በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ሕይወትህ የላቀ ትርጉም ሊኖረው ይችላልን?

ሕይወትህ የላቀ ትርጉም ሊኖረው ይችላልን?

ሕይወትህ የላቀ ትርጉም ሊኖረው ይችላልን?

የአንድ ነገር እውነተኛ ዋጋ ሁልጊዜ ከላይ በሚታየው የሚወሰን አይደለም። በዩናይትድ ስቴትስ የታተመው ትልቁ የባንክ ኖት 10, 000 የአሜሪካ ዶላር የተጻፈበት ኖት ነው። ሆኖም ይህ መጠን የሰፈረበት ወረቀት በዋጋ ረገድ የሚያወጣው ጥቂት ሳንቲሞች ብቻ ነው።

አነስተኛ ዋጋ ያላቸው ነጠላ ወረቀቶች ለሕይወትህ እውነተኛ ትርጉም ሊያስገኙልህ ይችሉ እንደሆነ አስበህ ታውቃለህ? ብዙዎች እውነተኛ ትርጉም ያስገኛሉ የሚል አስተሳሰብ አላቸው። በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች የቻሉትን ያህል ብዙ ገንዘብ ለማግኘት ሌት ተቀን ይሠራሉ። አንዳንድ ጊዜ ገንዘብ ለማግኘት የሚያደርጉት ጥረት ጤንነታቸውን፣ ከጓደኞቻቸውና አልፎ ተርፎም ከቤተሰባቸው ጋር ያላቸውን ግንኙነት መሥዋዕት እንዲያደርጉ ጠይቆባቸዋል። ታዲያ ምን ጥቅም አስገኘላቸው? ገንዘብ ወይም በገንዘብ የምንገዛው ነገር እውነተኛና ዘላቂ የሆነ እርካታ ሊያስገኝልን ይችላልን?

በቁሳዊ ንብረቶች እርካታን ለማግኘት በጣርን መጠን እርካታ የማግኘታችን አጋጣሚ እየተመናመነ እንደሚሄድ በመስኩ የተሰማሩ ተመራማሪዎች ይናገራሉ። ጋዜጠኛው አልፊ ኮን እንዲህ ሲሉ ደምድመዋል:- “እርካታ እንዲሁ በግዢ የሚገኝ ነገር አይደለም። . . . በሕይወታቸው ውስጥ ለሀብት ቅድሚያ የሚሰጡ ሰዎች ከወትሮው የከፋ ውጥረትና የመንፈስ ጭንቀት የሚያጋጥማቸው ከመሆኑም በላይ አጠቃላይ የደህንነት ስሜታቸው በጣም ዝቅተኛ ነው።”​—⁠ኢንተርናሽናል ሄራልድ ትሪቢዩን

ምንም እንኳ ተመራማሪዎች ትርጉም ያለው ሕይወት ለመምራት ከገንዘብ የተለየ ነገር እንደሚያስፈ​ልግ የተገነዘቡ ቢሆንም የብዙዎች አስተሳሰብ ግን ከዚህ ተቃራኒ ነው። በቀን እስከ 3, 000 የሚደርሱ የንግድ ማስታወቂያዎች ውርጅብኝ የሚወርድባቸው በምዕራባውያኑ ዓለም የሚኖሩ ሰዎች እንዲህ ያለ አስተሳሰብ ማዳበራቸው ሊያስገርመን አይ​ገባም። ማስታወቂያዎቹ የሚያስተዋውቁት መኪናም ሆነ ከረሜላ ከበስተጀርባ ያለው መልእክት ‘ይህን ዕቃ ከገዛህ ይበልጥ ደስተኛ ትሆናለህ’ የሚል ነው።

ነጋ ጠባ ቁሳዊ ነገሮችን በንግድ ማስታወቂያዎች ማቅረብ የሚያስከትለው ውጤት ምንድን ነው? በአብዛኛው መንፈሳዊ ቁም ነገሮች ችላ እንዲባሉ ያደርጋል! ኒውስዊክ መጽሔት ላይ የወጣ አንድ ሪፖርት በቅርቡ በጀርመን የኮሎኝ ሊቀ ጳጳስ “በኅብረተሰባችን ውስጥ አምላክ የመነጋገሪያ ርዕስ መሆኑ አክትሟል” ብለው መናገራቸውን ገል​ጿል።

ምናልባት አንተም ያለ የሌለ ኃይልህን ያዋልከው መተዳደሪያ ለማግኘቱ ተግባር ይሆናል። ሌላ ማንኛውንም ነገር ለመሥራት የሚያስችል ጊዜ እንደሌለህ ሆኖ ይሰማህ ይሆናል። ይሁን እንጂ ጤንነትህ ወይም ዕድሜህ የምታደርጋቸውን እንቅስቃሴዎች እስኪገድብብህ ድረስ ሁልጊዜ ተመሳሳይ ሥራ ከማከናወን ይልቅ በሕይወት ውስጥ የተሻለ ነገር መኖር አለበት ብለህ አልፎ አልፎ ታስብ ይሆናል።

ለመንፈሳዊ ጉዳዮች የበለጠ ትኩረት መስጠት የላቀ እርካታ ሊያስገኝልህ ይችል ይሆን? ለሕይወትህ የላቀ ትርጉም ሊያስገኝልህ የሚችለው ምንድን ነው?