በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

‘ጥበብ ረጅም ዘመን ታኖረናለች’

‘ጥበብ ረጅም ዘመን ታኖረናለች’

‘ጥበብ ረጅም ዘመን ታኖረናለች’

በሕይወት ውስጥ የሚያጋጥሙ ችግሮችን በመፍታት ረገድ ጥበብ ወሳኝ ሚና ይጫወታል ቢባል የማይስማማ ማን ይኖራል? እውነተኛ ጥበብ እውቀትንና ማስተዋልን ተገቢ በሆነ መንገድ የመጠቀም ችሎታ ነው። ጥበብ የሞኝነት፣ የቂልነትና የጅልነት ተቃራኒ ነው። በዚህም ምክንያት ቅዱሳን ጽሑፎች ጥበብ እንድናገኝ በጥብቅ ያሳስቡናል። (ምሳሌ 4:​7) እንዲያውም የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሆነው የምሳሌ መጽሐፍ በዋነኛነት የተጻፈው ጥበብንና ተግሣጽን ለማስተማር ነው። ገና ከመክፈቻው “የእስራኤል ንጉሥ የዳዊት ልጅ የሰሎሞን ምሳሌዎች፤ ጥበብንና ተግሣጽን ለማወቅ” በማለት ይጀምራል።​—⁠ምሳሌ 1:​1, 2

እስቲ ከምሳሌ መጽሐፍ ውስጥ የመጀመሪያዎቹ ጥቂት ምዕራፎች የሚያስተላልፉትን ጠንካራ ትምህርት እንመልከት። ሰሎሞን ለገዛ ልጁ ማሳሰቢያ እንደሚሰጥ አፍቃሪ አባት አንባቢዎቹ ተግሣጽን እንዲሰሙና ጥበብን በትኩረት እንዲከታተሉ ይማጸናል። (ምዕራፍ 1 እና 2) ከይሖዋ ጋር የጠበቀ ወዳጅነት እንዴት መመሥረት እንደምንችልና ልባችንን እንዴት መጠበቅ እንደምንችል ይገልጽልናል። (ምሳሌ 3 እና 4) በሥነ ምግባር ንጹሕ ሆነን እንድንመላለስ በጥብቅ ይመክረናል። (ምዕራፍ 5 እና 6) አዎን፣ ሥነ ምግባር የጎደለው አንድ ሰው የሚጠቀምበትን ዘዴ በማጋለጥ ከፍተኛ ጥቅም ይሰጠናል። (ምዕራፍ 7) እንዲሁም ስብዕና እንዳላት ተደርጋ የተገለጸችው ጥበብ የምታቀርበው ግብዣ ለእያንዳንዱ ሰው ምንኛ ማራኪ ነው! (ምዕራፍ 8) ንጉሥ ሰሎሞን በቀጣዮቹ ምዕራፎች ውስጥ የሚገኙትን ምሳሌዎች ከማስፈሩ በፊት የቀደሙትን ምዕራፎች ጠቅለል ባለ መንገድ ይከልሳል።​—⁠ምዕራፍ 9

‘ኑ፣ እንጀራዬን ብሉ፣ የወይን ጠጄንም ጠጡ’

የምሳሌ መጽሐፍ የመጀመሪያ ክፍል ቀደም ሲል የተሰጠውን ምክር በድጋሚ የሚጠቅስ ድርቅ ያለ ክለሳ አይደለም። ከዚህ ይልቅ አንባቢው ጥበብን እንዲፈልግ በማነሳሳት አስደሳችና ቀስቃሽ ማብራሪያ ይሰጣል።

የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሆነው የምሳሌ መጽሐፍ 9ኛ ምዕራፍ “ጥበብ ቤትዋን ሠራች፣ ሰባቱንም ምሰሶችዋን አቆመች ” በማለት ይጀምራል። (ምሳሌ 9:​1) አንድ የቋንቋ ምሁር እንደገለጹት “ሰባት ምሰሶዎች” የሚለው ሐረግ “በሁለት ጎኑ ሦስት ሦስት ቋሚና ከመግቢያው ፊት ለፊት፣ መካከል ላይ አንድ ምሰሶ እንዲኖሩት ተደርጎ በቅጥር ግቢ ውስጥ የተሠራን አንድ ትልቅ ቤት ያመለክታል” ብለዋል። ያም ሆነ ይህ እውነተኛ ጥበብ ብዙ እንግዶችን ማስተናገድ የሚያስችል ጠንካራ ቤት ሠርታለች።

በቤቱ ውስጥ ድግሱ ተዘጋጅቷል። እንደ ወይን ጠጁ ሁሉ ሥጋውም ተዘጋጅቷል። ጥበብ ምግብ ለማዘጋጀቱና ገበታ ለማቅረቡ ጉዳይ ልዩ ትኩረት ሰጥታለች። “ፍሪዳዋን አረደች፣ የወይን ጠጅዋን ደባለቀች፣ ማዕድዋን አዘጋጀች።” (ምሳሌ 9:​2) በዚህ ምሳሌያዊ ገበታ ላይ የቀረበው ምግብ ጥንቃቄ የተሞላበት ምርምር ሊደረግበት የሚገባ መንፈሳዊ ምግብ እንደሆነ ግልጽ ነው።​—⁠ኢሳይያስ 55:​1, 2

እውነተኛ ጥበብ ወዳዘጋጀችው ድግስ የተጠሩት እነማን ናቸው? “ባሪያዎችዋን ልካ በከተማይቱ ከፍተኛ ስፍራ ላይ ጠራች:- አላዋቂ የሆነ [“ተሞክሮ የጎደለው፣” NW ] ወደዚህ ፈቀቅ ይበል፤ አእምሮ [“ልብ፣” NW ] የጐደላቸውንም እንዲህ አለች:- ኑ፣ እንጀራዬን ብሉ፣ የደባለቅሁትንም የወይን ጠጅ ጠጡ። አላዋቂነትን ትታችሁ በሕይወት ኑሩ፣ በማስተዋልም መንገድ ሂዱ።”​—ምሳሌ 9:​3-6

ጥበብ እድምተኞቿን እንዲጠሩ አገልጋዮችዋን ልካለች። እነርሱም በጣም ብዙ ሰዎችን መጥራት ይችሉ ዘንድ ሕዝብ ወደሚበዛባቸው ቦታዎች ሄደዋል። “ልብ የጎደላቸው” ወይም ማስተዋል የጎደላቸው እንዲሁም ተሞክሮ የጎደላቸው ሁሉ ተጋብዘዋል። (ምሳሌ 9:​4) እንዲሁም የሕይወት ተስፋ ተዘርግቶላቸዋል። በምሳሌ መጽሐፍ ውስጥ የሚገኘውን ጨምሮ በአምላክ ቃል ውስጥ የሰፈረውን ጥበብ ማንም ሰው በቀላሉ ሊያነበው እንደሚችል ግልጽ ነው። በዛሬው ጊዜ የይሖዋ ምሥክሮች የእውነተኛ ጥበብ መልእክተኞች በመሆን በማንኛውም ቦታ የሚያገኟቸው ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን እንዲያጠኑ በትጋት ይጋብዛሉ። በእርግጥም ይህንን እውቀት መቅሰም የዘላለም ሕይወት ያስገኛል።​—⁠ዮሐንስ 17:​3

ክርስቲያኖች ጥበብ የምትሰጠውን ተግሣጽ በትህትና መቀበል አለባቸው። በተለይ ደግሞ ወጣቶችና በቅርቡ ስለ ይሖዋ መማር የጀመሩ ሰዎች እንዲህ ማድረግ ይኖርባቸዋል። በአምላክ መንገዶች ያካበቱት ተሞክሮ ውስን ስለሆነ ‘ልብ ጎድሏቸው’ ሊሆኑ ይችላሉ። ዝንባሌያቸው ሙሉ በሙሉ መጥፎ ነው ማለት አይደለም። ከዚያ ይልቅ ልባቸው ይሖዋ አምላክን ደስ ማሰኘት ወደሚችልበት ደረጃ ላይ እንዲደርስ ለማድረግ ጊዜና ጥረት ይጠይቃል። ይህ ደግሞ ሐሳብን፣ ምኞትን፣ ፍላጎትንና ግብን አምላክ ከሚቀበላቸው ነገሮች ጋር እንዲስማማ ማድረግን ይጠይቃል። “አሁን እንደ ተወለዱ ሕፃናት ተንኰል የሌለበትን የቃልን ወተት” መመኘታቸው ምንኛ ጠቃሚ ነው።​—⁠1 ጴጥሮስ 2:​2

ሁላችንስ ብንሆን ‘መሠረታዊ ከሆኑ ትምህርቶች’ አልፈን መሄድ አይኖርብንምን? በእርግጥም ‘የአምላክን ጥልቅ ነገሮች’ የማወቅና የጎለመሱ ሰዎች እንደሚመገቡት ያለ ጠንካራ ምግብ የመመገብ ፍላጎታችንን ማሳደግ ይኖርብናል። (ዕብራውያን 5:​12–6:​1፤ 1 ቆሮንቶስ 2:​10) በኢየሱስ ክርስቶስ አመራር ሥር የሚገኘው “ታማኝና ልባም ባሪያ” ለሁሉም ወቅታዊ የሆነ መንፈሳዊ ምግብ በትጋት ያቀርባል። (ማቴዎስ 24:​45-47) የአምላክን ቃልና የባሪያው ክፍል የሚያዘጋጃቸውን በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረቱ ጽሑፎችን በትጋት በማጥናት ከጥበብ ገበታ ላይ መመገባችንን እንቀጥል።

“ፌዘኛን አትገሥጽ”

የጥበብ ትምህርት እርማትንና ተግሣጽ መስጠትን የሚጨምር ነው። ይህ የጥበብ ገጽታ ተቀባይነት ያለው በሁሉም ዘንድ አይደለም። በዚህም የተነሳ የምሳሌ መጽሐፍ የመጀመሪያ ክፍል መደምደሚያ እንዲህ በማለት ያስጠነቅቃል:- “ፌዘኛን የሚገሥጽ ለራሱ ስድብን ይቀበላል፣ ኀጥእንም የሚዘልፍ ነውርን ያገኛል። ፌዘኛን አትገሥጽ እንዳይጠላህ።”​—⁠ምሳሌ 9:​7, 8ሀ

ፌዘኛ አካሄዱን እንዲያቀና በሚረዳው ሰው ላይ ቂም ይይዛል እንዲሁም ጥላቻ ያዳብራል። ክፉ ሰው ተግሣጽ ከፍተኛ ጥቅም እንዳለው አይገነዘብም። እውነትን ለሚጠላ ሰው ወይም ሲነግሩት ለሚያፌዝ ሰው ማራኪ የሆነውን የአምላክ ቃል እውነት ለማስተማር መሞከር ምንኛ ሞኝነት ነው! ሐዋርያው ጳውሎስ በአንጾኪያ በሰበከበት ወቅት ለእውነት ፍቅር የሌለው አንድ የአይሁድ ቡድን አጋጥሞት ነበር። ንግግሩን በስድብ እየተቃወሙ አምባጓሮ ለመፍጠር ሙከራ ባደረጉ ጊዜ ጳውሎስ “የእግዚአብሔር[ን] ቃል . . . ከገፋችሁትና የዘላለም ሕይወት እንዳይገባችሁ በራሳችሁ ከፈረዳችሁ . . . እነሆ፣ ወደ አሕዛብ ዘወር እንላለን” አላቸው።​—⁠ሥራ 13:​45, 46

የመንግሥቱን ምሥራች ልበ ቅን ለሆኑ ሰዎች ለማድረስ በምናደርገው ጥረት ከፌዘኞች ጋር የጦፈ ክርክርና ጭቅጭቅ ውስጥ እንዳንገባ መጠንቀቅ ይኖርብናል። ክርስቶስ ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን እንዲህ በማለት አዟቸዋል:- “ወደ ቤትም ስትገቡ ሰላምታ ስጡ፤ ቤቱም የሚገባው ቢሆን ሰላማችሁ ይድረስለት፤ ባይገባው ግን ሰላማችሁ ይመለስላችሁ። ከማይቀበላችሁም ቃላችሁንም ከማይሰሙ ሁሉ፣ ከዚያ ቤት ወይም ከዚያች ከተማ ስትወጡ የእግራችሁን ትቢያ አራግፉ።”​—⁠ማቴዎስ 10:​12-14

ጥበበኛ ሰው ለእርማት የሚሰጠው ምላሽ ፌዘኛ ሰው ከሚሰጠው ምላሽ ፈጽሞ የተለየ ነው። ሰሎሞን “ጠቢብን ገሥጽ ይወድድህማል። ለጠቢብ ሰው ትምህርትን ስጠው፣ ጥበብንም ያበዛል” በማለት ተናግሯል። (ምሳሌ 9:​8ለ, 9ሀ) ጠቢብ ሰው ‘ቅጣት ሁሉ ለጊዜው የሚያሳዝን እንጂ ደስ የሚያሰኝ እንዳልሆነ፣ ዳሩ ግን በኋላ ለለመዱት የሰላምን ፍሬ እርሱም ጽድቅን እንደሚያፈራላቸው’ ያውቃል። (ዕብራውያን 12:​11) ምክር የማያስደስት ቢሆንም እንኳ እሺ ብለን እስከ ተቀበልን ድረስ ይበልጥ ጠቢብ የሚያደርገን ከሆነ የአጸፋ እርምጃ የምንወስድበት ወይም ምክሩን ላለመቀበል የምንከላከልበት ምን ምክንያት አለ?

ሰሎሞን “ጽድቅንም አስተምረው፣ እውቀትንም ያበዛል” በማለት ይቀጥላል። (ምሳሌ 9:​9ለ) በጣም ጠቢብ ወይም በዕድሜ የገፋ በመሆኑ ትምህርት የማያስፈልገው ሰው የለም። በዕድሜ በጣም የገፉ ሰዎች እንኳ ሳይቀሩ እውነትን ተቀብለው ራሳቸውን ለይሖዋ ሲወስኑ ማየቱ ምንኛ የሚያስደስት ነው! እኛም ብንሆን ትምህርት የመቅሰምና አእምሯችንን የማሠራት ፍላጎት እንዲኖረን የምንጥር እንሁን።

“የሕይወትህ ዕድሜ ይጨምርልሃል”

ሰሎሞን ማስተላለፍ ለፈለገው ዋና ነጥብ አጽንኦት ለመስጠት ለጥበብ መሠረት የሚሆነውን ነገር አክሎ ተናግሯል። “የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው፤ ቅዱሱንም ማወቅ ማስተዋል ነው” በማለት ጽፏል። (ምሳሌ 9:​10) ለእውነተኛው አምላክ የጠለቀ አክብሮታዊ ፍርሃት ሳያዳብሩ አምላካዊ ጥበብ እንዲኖር ማድረግ አይቻልም። አንድ ሰው ጥሩ እውቀት ሊኖረው ይችላል ሆኖም ይሖዋን የማይፈራ ከሆነ እውቀቱን ፈጣሪን በሚያስከብር መንገድ ሳይጠቀም ይቀራል። እንዲያውም ከሚያውቃቸው ነገሮች ብቻ በመነሳት ወደ ተሳሳተ መደምደሚያ ሊደርስና እንደሞኝ ሊቆጠር ይችላል። ከዚህ በተጨማሪ የቅዱሱ የይሖዋ እውቀት ለጥበብ ዓይነተኛ መለያ የሆነውን ማስተዋልን ለማግኘት በጣም አስፈላጊ ነው።

ጥበብ ምን ዓይነት ፍሬ ታፈራለች? (ምሳሌ 8:​12-21, 35) የእስራኤል ንጉሥ “ዘመንህ በእኔ ይበዛልና፣ የሕይወትህም ዕድሜ ይጨመርልሃልና” በማለት ይናገራል። (ምሳሌ 9:​11) የዘመን ርዝማኔ እና ረጅም ዕድሜ ከጥበብ ጋር በመወዳጀት የሚገኝ ውጤት ነው። አዎን፣ ‘ጥበብን ገንዘብ ላደረጋት ሕይወትን ትሰጠዋለች።’​—⁠መክብብ 7:​12

ጥበብን ለማግኘት ከፍተኛ ጥረት ማድረግ የእያንዳንዱ ግለሰብ ኃላፊነት ነው። ሰሎሞን ይህን ሃቅ ጎላ አድርጎ ሲናገር “ጠቢብ ብትሆን ለራስህ ጠቢብ ትሆናለህ፣ ፌዘኛም ብትሆን ፌዘኛነትህን ለብቻህ ትሸከማለህ” ብሏል። (ምሳሌ 9:​12) ጠቢብ ሰው ጠቢብ በመሆኑ የሚጠቀመው ራሱ ነው፤ ፌዘኛም ለሚደርስበት ሥቃይ ኃላፊነቱን የሚሸከመው ራሱ ነው። በእርግጥም የምንዘራውን ያንኑ እናጭዳለን። እንግዲያው ‘ጥበብ ስትናገር በጥሞና እናዳምጥ።’​—⁠ምሳሌ 2:​2

“ሰነፍ ሴት ሁከተኛ ናት”

ሰሎሞን በማነጻጸር ቀጥሎ እንዲህ ይላል:- “ሰነፍ ሴት ሁከተኛ ናት፤ አሳብ የላትም፣ አንዳችም አታውቅም። በቤትዋ ደጅ በከተማይቱ ከፍተኛ ስፍራ በወንበር ላይ ትቀመጣለች፣ በመንገድ የሚያልፉትን አካሄዳቸውንም ያቀኑትን ለመጥራት:- አላዋቂ የሆነ ወደዚህ ፈቀቅ ይበል።”​—⁠ምሳሌ 9:​13-16ሀ

ስንፍና ለፍላፊ፣ ስድና አላዋቂ በሆነች ሴት ተመስላለች። እሷም በበኩሏ ቤት ሠርታለች። ተሞክሮ የጎደለውን ማንኛውንም ሰው መጣራቱን ሥራዬ ብላ ተያይዛዋለች። ስለዚህ አላፊ አግዳሚው የራሱን ምርጫ ማድረግ ይችላል። የማንን ግብዣ ይቀበላሉ? የጥበብን ወይስ የስንፍናን?

“የስርቆት ውኃ ይጣፍጣል”

ጥበብም ሆነች ስንፍና “ወደዚህ ፈቀቅ” በሉ እያሉ አድማጮቻቸውን ይጋብዛሉ። ይሁን እንጂ ግብዣቸው ለየቅል ነው። ጥበብ ወይን ጠጅ፣ ሥጋና እንጀራ ወደሞላበት ድግስ ሰዎችን ትጋብዛለች። ስንፍና ሰውን ለመሳብ የምትጠቀምበት መንገድ ስድ የሆነች ሴት የምትጠቀምበትን ዘዴ ያስታውሰናል። ሰሎሞን “አእምሮ የጐደለውንም እንዲህ አለች:- የስርቆት ውኃ ይጣፍጣል፣ የተሸሸገም እንጀራ ደስ ያሰኛል” በማለት ተናግሯል።​—⁠ምሳሌ 9:​16ለ, 17

“ሰነፍ ሴት” ወይን ጠጅ ከመጋበዝ ይልቅ የተሰረቀ ውኃ ታቀርባለች። (ምሳሌ 9:​13) በቅዱሳን ጽሑፎች ውስጥ፣ ከምትወደድ ሚስት ጋር በጾታ ስሜት መርካት ጥም የሚቆርጥ ቀዝቃዛ ውኃ ከመጠጣት ጋር ተመሳስሏል። (ምሳሌ 5:​15-17) እንግዲያው የስርቆት ውኃ በድብቅ የሚፈጸመውን የጾታ ብልግናን ያመለክታል። እንዲህ ያለው ውኃ ከወይን ጠጅ ይልቅ ጣፋጭ መስሎ የሚታየው ሌሎች ሳይነቁ በስርቆት የሚገኝ በመሆኑ ነው። በስርቆት የተገኘ እንጀራም ሃቀኝነት በጎደለው መንገድ ስለተገኘ ጥበብ ከምታቀርበው እንጀራና ሥጋ ይበልጥ የሚጥም ይመስላል። የተከለከለንና የተሰረቀን ነገር ማራኪ እንደሆነ አድርጎ መመልከት የስንፍና ምልክት ነው።

ጥበብ የምታቀርበው ግብዣ ሕይወት መስጠትንም የሚጨምር ሲሆን ሰነፍ ሴት ግን እሷን መከተል ስለሚያስከትለው ውጤት ምንም የምትለው ነገር የለም። ሆኖም ሰሎሞን “ነገር ግን እርሱ ሙታን ከዚያ እንዳሉ፣ እድመኞችዋም በሲኦል ጥልቀት እንዳሉ አያውቅም” በማለት አስጠንቅቋል። (ምሳሌ 9:​18) አንድ ምሁር “የሰነፍ ሴት መኖሪያ ቤት ሳይሆን መቃብር ነው። አንዴ ከገባህ መውጫ የለህም” በማለት ጽፈዋል። ሥነ ምግባር የጎደለው አኗኗር መከተል ሞት ያስከትላል።

ኢየሱስ ክርስቶስ “በጠበበው ደጅ ግቡ፤ ወደ ጥፋት የሚወስደው ደጅ ሰፊ፣ መንገዱም ትልቅ ነውና፣ ወደ እርሱም የሚገቡ ብዙዎች ናቸው፤ ወደ ሕይወት የሚወስደው ደጅ የጠበበ፣ መንገዱም የቀጠነ ነውና፣ የሚያገኙትም ጥቂቶች ናቸው” በማለት ተናግሯል። (ማቴዎስ 7:​13, 14) ሁላችንም ሁልጊዜ ከጥበብ ገበታ የምንመገብና ወደ ሕይወት በሚወስደው ጎዳና ላይ ከሚጓዙት ሰዎች መካከል የምንገኝ እንሁን።

[በገጽ 31 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ጠቢብ ሰው የሚሰጠውን ተግሣጽ በደስታ ይቀበላል

[በገጽ 31 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ጥበብን ማግኘት የእያንዳንዱ ግለሰብ ኃላፊነት ነው