በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ጥበብ ያለበት ውሳኔ ማድረግ የምትችለው እንዴት ነው?

ጥበብ ያለበት ውሳኔ ማድረግ የምትችለው እንዴት ነው?

ጥበብ ያለበት ውሳኔ ማድረግ የምትችለው እንዴት ነው?

ነፃ ምርጫ ከአምላክ የተገኘ ስጦታ ነው። ነፃ ምርጫ ባይኖረን ኖሮ በምናደርጋቸው ነገሮች ላይ ምንም ሥልጣን የሌለን ከሮቦት ያልተሻልን ፍጥረታት እንሆን ነበር። ሆኖም የመምረጥ ነፃነት ፈታኝ ሁኔታዎችን ያስከትላል። የመምረጥ ነፃነት ያለን እንደመሆናችን መጠን በሕይወታችን ውስጥ ውሳኔዎች ማድረግ ይኖርብናል።

እርግጥ ብዙዎቹ ውሳኔዎች ቀላል ናቸው። ሆኖም የምንሠማራበትን የሥራ መስክ መምረጥን ወይም ትዳር መመሥረት አለመመሥረትን የመሳሰሉ ውሳኔዎች የወደፊቱን ሕይወታችንን በጥልቅ ሊነኩት ይችላሉ። ሌሎች ውሳኔዎች ደግሞ ሌሎችን ይነካሉ። ወላጆች የሚያደርጓቸው አንዳንድ ውሳኔዎች በልጆቻቸው ላይ ከፍተኛ ለውጥ ያስከትላሉ። ከዚህም በተጨማሪ ለምናደርጋቸው ብዙ ውሳኔዎች ለአምላክ መልስ እንሰጣለን።​—⁠ሮሜ 14:​12

እርዳታ ማግኘት የሚያስፈልግበት ምክንያት

ውሳኔ በማድረግ ረገድ የሰው ልጆች ያስመዘገቡት ታሪክ ጥሩ አይደለም። የሰው ልጅ ካደረጋቸው ውሳኔዎች ውስጥ ተመዝግቦ የሚገኘው የመጀመሪያው ውሳኔ አስከፊ ውጤት አስከትሏል። ሔዋን፣ አምላክ እንዳትበሉ ብሎ በጥብቅ የከለከለውን ፍሬ ለመብላት ወሰነች። በራስ ወዳድነት ምኞት ላይ ተመስርታ ያደረገችው ውሳኔ ባሏም ከእርሷ ጋር አብሮ አምላክን እንዳይታዘዝ የገፋፋው ሲሆን ድርጊቱ በሰው ዘር ላይ ታላቅ መከራ አስከትሏል። በብዙ ሁኔታዎች እንደታየው አሁንም ሰዎች ውሳኔ የሚያደርጉት በትክክለኛ መሠረታዊ ሥርዓት ላይ ሳይሆን በራስ ወዳድነት ምኞት ላይ ተመርኩዘው ነው። (ዘፍጥረት 3:​6-19፤ ኤርምያስ 17:​9) ብዙውን ጊዜ ከባድ ውሳኔ የሚጠይቅ ሁኔታ ሲያጋጥመን የአቅማችንን ውስንነት እንገነዘባለን።

ብዙዎች ከበድ ያለ ውሳኔ የሚጠይቅ ሁኔታ ሲያጋጥማቸው ከሰው በላይ የሆነ አካል እርዳታ ለማግኘት መፈለጋቸው አያስደንቅም። መጽሐፍ ቅዱስ ናቡከደነፆር በጦርነት ላይ እያለ ውሳኔ ማድረግ አስፈልጎት የነበረበትን አንድ አጋጣሚ ይዘግባል። ንጉሥ የነበረ ቢሆንም ‘ምዋርት ማሟረትና’ መናፍስት ጠሪዎችን መጠየቅ እንዳለበት ተሰምቶት ነበር። ዘገባው እንዲህ ይላል:- “ፍላጾችን ወዘወዘ፣ ከተራፊምም ጠየቀ፣ ጉበትም ተመለከተ።” (ሕዝቅኤል 21:​21) ዛሬም በተመሳሳይ ብዙዎች ጠንቋዮችንና ኮኮብ ቆጣሪዎችን ያማክራሉ ወይም በሌሎች መንገዶች ከመናፍስት እርዳታ ለማግኘት ይጥራሉ። ሆኖም እነዚህ የመረጃ ምንጮች አታላይና አሳሳች ናቸው።​—⁠ዘሌዋውያን 19:​31

ሆኖም ሙሉ በሙሉ አስተማማኝ የሆነና በታሪክ ዘመን ሁሉ የሰው ልጆች ጥበብ ያለበት ውሳኔ እንዲያደርጉ የረዳ አንድ አካል አለ። ይህ አካል ከይሖዋ አምላክ በቀር ሌላ ማንም ሊሆን አይችልም። ለምሳሌ ያህል በጥንት ጊዜ አምላክ ለሕዝቡ ለእስራኤል ኡሪምና ቱሚም የተባሉ ቅዱስ ጠጠሮች ሰጥቷቸው ነበር። ሕዝቡ ከባድ ውሳኔ ማድረግ የሚጠይቅ ሁኔታ ሲያጋጥመው ጠጠሮቹ ይጣላሉ። ይሖዋም በኡሪምና በቱሚም በኩል ለጥያቄዎቻቸው ቀጥተኛ መልስ ይሰጥ እንዲሁም የእስራኤል ሽማግሌዎች ያደረጉት ውሳኔ ከእርሱ ፈቃድ ጋር ይስማማ እንደሆነና እንዳልሆነ እንዲያረጋግጡ ይረዳቸው ነበር።​—⁠ዘጸአት 28:​30፤ ዘሌዋውያን 8:​8፤ ዘኁልቊ 27:​21

ሌላ ምሳሌ ደግሞ ተመልከት። ጌዴዎን እስራኤላውያን ከምድያማውያን ጋር በሚያደርጉት ጦርነት ሠራዊቱን እንዲመራ ተጠይቆ ነበር። በዚህ ጊዜ ይህንን ከፍተኛ መብት ለመቀበል ወይም ላለመቀበል ውሳኔ ማድረግ አስፈልጎት ነበር። ጌዴዎን የይሖዋን ድጋፍ እንደሚያገኝ እርግጠኛ ለመሆን ይሖዋ ተአምራዊ ምልክት እንዲያሳየው ጠየቀ። በሌሊት አውድማው ላይ የተወው የተባዘተ የበግ ጠጉር በጠል ሲረሰርስ ጠጉሩ ካረፈበት ዙሪያ ያለው መሬት ግን ደረቅ እንዲሆን ጠየቀ። በሚቀጥለው ምሽት ደግሞ ጠጉሩ ደረቅ እንዲሆንና የቀረው መሬት ግን በጠል እንዲረሰርስ ጠየቀ። ይሖዋም ጌዴዎን የጠየቀውን ምልክት በደግነት አሳየው። በዚህም ምክንያት ጌዴዎን ትክክለኛ ውሳኔ ማድረግ የቻለ ሲሆን በመለኮታዊ ድጋፍ የእስራኤልን ጠላቶች ሙሉ በሙሉ ደምስሷል።​—⁠መሳፍንት 6:​33-40፤ 7:21, 22

ዛሬስ ምን ለማለት ይቻላል?

ዛሬም ቢሆን ይሖዋ አገልጋዮቹ ከበድ ያለ ውሳኔ ማድረግን የሚጠይቁ ሁኔታዎች ሲያጋጥሟቸው የእርዳታ እጁን ይዘረጋላቸዋል። እንዴት? እኛ እንደ ጌዴዎን ‘በተባዘተ የበግ ጠጉር’ አማካኝነት ትክክለኛው ውሳኔ የቱ እንደሆነ የሚያሳይ ምልክት ከይሖዋ መጠየቅ ይኖርብናልን? አንድ ባልና ሚስት የመንግሥቱ ሰባኪዎች ይበልጥ ወደሚያስፈልጉበት ቦታ መሄድ ይኖርባቸው እንደሆነና እንዳልሆነ ለማወቅ ስለፈለጉ ለውሳኔ እንዲረዳቸው አንድ ፈተና አዘጋጁ። ቤታቸውን በተወሰነ ገንዘብ ለመሸጥ አሰቡ። ከዚያ ቤቱ በተወሰነው ቀን ውስጥ ባሰቡት ገንዘብ ወይም ከዚህ በሚበልጥ ዋጋ ከተሸጠ አምላክ እንዲሄዱ ፈልጓል ማለት ነው። ቤቱ ካልተሸጠ ግን አምላክ እንዲሄዱ አልፈለገም ማለት ነው ብለው ሊደመድሙ ነው።

ቤቱ ግን ሳይሸጥ ቀረ። ይህ ማለት ይሖዋ እነዚህ ባልና ሚስት ሰባኪዎች ይበልጥ በሚያስፈልጉበት ቦታ ሄደው እንዲያገለግሉ አልፈለገም ማለት ነውን? እርግጥ ይሖዋ ለአገልጋዮቹ እንዲህ ያደርጋል ወይም አያደርግም ብሎ መደምደሙ መዳፈር ይሆናል። በዛሬው ጊዜ ይሖዋ ለእኛ ያለውን ፈቃድ ለመግለጽ ፈጽሞ እጁን ጣልቃ አያስገባም ማለት አንችልም። (ኢሳይያስ 59:​1) ሆኖም በምናደርጋቸው ከባድ ውሳኔዎች ረገድ አምላክ እጁን ያስገባል ብለን የመጠበቅ ወይም በሌላ አባባል ውሳኔውን ለእርሱ የመተው መብት የለንም። ጌዴዎንም ቢሆን በአብዛኛው የሕይወት ዘመኑ ከይሖዋ ምንም ዓይነት ተዓምራዊ ምልክት ሳያይ ውሳኔዎች ማድረግ አስፈልጎታል!

ያም ሆነ ይህ መጽሐፍ ቅዱስ መለኮታዊ መመሪያ ማግኘት እንደሚቻል ይገልጻል። ስለጊዜያችን አስቀድሞ ሲናገር:- “ወደ ቀኝም ወደ ግራም ፈቀቅ ብትል ጆሮችህ በኋላህ:- መንገዱ ይህች ናት በእርስዋም ሂድ የሚለውን ቃል ይሰማሉ” ብሏል። (ኢሳይያስ 30:​21) ከበድ ያሉ ውሳኔዎች በምናደርግበት ጊዜ ውሳኔዎቻችን ከአምላክ ፈቃድ ጋር የሚስማሙና የእርሱን የላቀ ጥበብ የሚያንጸባርቁ መሆናቸውን ለማረጋገጥ መጣራችን ፍጹም ተገቢ ነው። እንዴት? ቃሉን በመመርመርና ‘ለእግራችን መብራት ለመንገዳችን ብርሃን’ እንዲሆን በመፍቀድ ነው። (መዝሙር 119:​105፤ ምሳሌ 2:​1-6) ይህንን ለማድረግ ከመጽሐፍ ቅዱስ ትክክለኛ እውቀት የመሰብሰብን ልማድ ማዳበር ይኖርብናል። (ቆላስይስ 1:​9, 10) እንዲሁም ውሳኔ የሚጠይቁ ነገሮች ሲያጋጥሙን ከጉዳዩ ጋር ዝምድና ያላቸውን ሁሉንም የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች መመርመር ይኖርብናል። እንዲህ ያለው ምርምር ‘ከሁሉ ይበልጥ አስፈላጊ የሆኑትን ነገሮች’ ለይተን እንድናውቅ ይረዳናል።​—⁠ፊልጵስዩስ 1:​9, 10 NW 

ይሖዋ እንደሚሰማን እርግጠኛ በመሆን በጸሎት ወደ እርሱ መቅረብም ይኖርብናል። ማድረግ ስላለብን ውሳኔና ስላሉን አማራጮች ለአፍቃሪው አምላካችን መግለጹ ምንኛ ያጽናናል! ከዚያም ትክክለኛውን ውሳኔ እንድናደርግ እንደሚረዳን በመተማመን መመሪያ እንዲሰጠን መጠየቅ እንችላለን። በአብዛኛው መንፈስ ቅዱስ ተግባራዊ ሊሆኑ የሚችሉ የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶችን እንድናስታውስ ይረዳናል። ወይም ደግሞ ከሁኔታችን ጋር ተዛማጅነት ያለውን ጥቅስ ይበልጥ በተሻለ መንገድ እንድንረዳው ሊያደርገን ይችላል።​—⁠ያዕቆብ 1:​5, 6

በተጨማሪም ይሖዋ ስለ ውሳኔዎቻችን ልናዋያቸው የምንችል የጎለመሱ ሰዎች በጉባኤው ውስጥ አዘጋጅቶልናል። (ኤፌሶን 4:​11, 12) ሆኖም ሌሎችን በምናነጋግርበት ወቅት ለመስማት የሚፈልጉትን ነገር የሚነግራቸው ሰው እስኪያገኙ ድረስ የተለያየ ሰው የሚያነጋግሩትን ዓይነት ሰዎች መሆን አይኖርብንም። በመጨረሻም የዚያን ሰው ምክር ይከተላሉ። የሮብዓምንም የማስጠንቀቂያ ምሳሌ ማስታወስ ይኖርብናል። ከበድ ያለ ውሳኔ ማድረግ ባስፈለገው ጊዜ በአባቱ ግዛት ወቅት ካገለገሉት ሽማግሌዎች ድንቅ ምክር አገኘ። ሆኖም ሮብዓም የእነርሱን ምክር ከመከተል ይልቅ ከእርሱ ጋር ያደጉትን እኩዮቹን አማከረ። የእነርሱን ምክር ተከትሎ በጣም መጥፎ ውሳኔ በማድረጉ የመንግሥቱን ሰፊ ግዛት አጣ።​—⁠1 ነገሥት 12:1-17

ምክር በምትጠይቅበት ወቅት የሕይወት ተሞክሮና ጥሩ የቅዱሳን ጽሑፎች እውቀት እንዲሁም ለትክክለኛ መሠረታዊ ሥርዓቶች አምላካዊ አክብሮት ያላቸውን ሰዎች አማክር። (ምሳሌ 1:5፤ 11:14፤ 13:20) የሚቻል ከሆነ ከጉዳዩ ጋር ተዛማጅነት ባላቸው መሠረታዊ ሥርዓቶችና ባሰባሰብካቸው መረጃዎች ላይ ለማሰላሰል ጊዜ መድብ። ነገሮችን በይሖዋ ቃል ብርሃን መመልከት ስትጀምር ትክክለኛው ውሳኔ ይበልጥ ግልጽ ሆኖ መታየቱ አይቀርም።​—⁠ፊልጵስዩስ 4:6, 7

የምናደርጋቸው ውሳኔዎች

አንዳንድ ውሳኔዎች ቀላል ናቸው። ሐዋርያት መመሥከራቸውን እንዲያቆሙ ሲታዘዙ ስለ ኢየሱስ መስበካቸውን መቀጠል እንዳለባቸው ያውቁ ስለነበር ወዲያው ከሰው ይልቅ አምላክን ለመታዘዝ መወሰናቸውን ለሳንሄድሪን አሳወቁ። (ሥራ 5:​28, 29) ሌሎች ውሳኔዎች ግን ይበልጥ ማሰብን የሚጠይቁ ሊሆኑ ይችላሉ። ምክንያቱም መጽሐፍ ቅዱስ ስለጉዳዩ በቀጥታ ላይናገር ይችላል። ያም ሆኖ የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች በአብዛኛው የተሻለ ውሳኔ ለማድረግ የሚያስችል መመሪያ ይሰጡናል። ለምሳሌ ያህል በዛሬው ጊዜ ያሉት አብዛኞቹ መዝናኛዎች በኢየሱስ ዘመን የሚታወቁ ባይሆኑም ይሖዋ ምን እንደሚያስደስተውና ምን ደግሞ እንደሚያሳዝነው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በግልጽ ሰፍሯል። ስለዚህ ክፋትን፣ የሥነ ምግባር ብልግናን ወይም ደግሞ ዓመፅን በሚያበረታታ መዝናኛ የሚካፈል ማንኛውም ክርስቲያን መጥፎ ውሳኔ አድርጓል።​—⁠መዝሙር 97:10፤ ዮሐንስ 3:19-21፤ ገላትያ 5:19-23፤ ኤፌሶን 5:3-5

አንዳንዴ ደግሞ ሁለቱም ውሳኔዎች ትክክል የሚሆኑበት ጊዜ አለ። የመንግሥቱ አስፋፊዎች በሚያስፈልጉበት ቦታ ሄዶ ማገልገል አስደናቂ መብት ሲሆን ታላላቅ በረከቶችንም ሊያስገኝ ይችላል። ሆኖም አንድ ሰው በተለያዩ ምክንያቶች የተነሣ እንዲህ ላለማድረግ ቢወስን በጉባኤው ውስጥም ሆኖ ጥሩ ሥራ ሊያከናውን ይችላል። አንዳንድ ጊዜ የሚገጥመን ውሳኔ የሚጠይቅ ሁኔታ ለይሖዋ ያለንን ጥልቅ አምልኮታዊ ፍቅር ወይም በሕይወታችን ውስጥ የምናስቀድመውን ነገር የሚመዝን አጋጣሚ ሊሆን ይችላል። በዚህ ጊዜ ይሖዋ የመምረጥ ነፃነታችንን ተጠቅመን የልባችንን እውነተኛ ፍላጎት እንድናሳይ ይፈቅድልናል።

የምናደርጋቸው ውሳኔዎች በአብዛኛው ሌሎችን ይነካሉ። ለምሳሌ ያህል የመጀመሪያው መቶ ዘመን ክርስቲያኖች ሕጉ ከሚጥላቸው ብዙ እገዳዎች ነጻ በመሆናቸው ተደስተው ነበር። ይህ ማለት በሕጉ ሥር ንጹህ ያልሆነውን ምግብ መብላትም ሆነ አለመብላት ይችሉ ነበር ማለት ነው። ያም ሆኖ ይህንን ነፃነታቸውን ለመጠቀም ሲወስኑ የሌሎችን ሕሊና ግምት ውስጥ እንዲያስገቡም ተበረታትተው ነበር። ጳውሎስ “ማሰናከያ አትሁኑ” በማለት በጉዳዩ ላይ የሰጠው ምክር ዛሬ ለምናደርጋቸው ብዙ ውሳኔዎችም ይሠራል። (1 ቆሮንቶስ 10:​32) ሌሎችን ላለማሰናከል ያለን ፍላጎት በምናደርጋቸው ብዙ ውሳኔዎች ላይ ለውጥ ሊያመጣ ይችላል። ደግሞም ባልንጀራን መውደድ ከሁሉ የሚበልጠው ሁለተኛ ትእዛዝ ነው።​—⁠ማቴዎስ 22:​36, 39

ውሳኔዎቻችን የሚያስከትሉት ውጤት

በጥሩ ሕሊና በመመራትና በመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች ላይ በመመርኮዝ የተደረጉ ውሳኔዎች የኋላ ኋላ ጥቅም ማስገኘታቸው አይቀርም። በወቅቱ ግን አንዳንድ መሥዋዕትነት ያስከፍሉን ይሆናል። ሐዋርያት ስለ ኢየሱስ መስበካቸውን እንደማያቆሙ ለሳንሄድሪን ሲገልጹ ከመፈታታቸው በፊት ተገርፈው ነበር። (ሥራ 5:​40) ሲድራቅ፣ ሚሳቅና አብድናጎ የተባሉት ሦስት ዕብራውያን ናቡከደነፆር ላሠራው የወርቅ ምስል ላለመስገድ ሲወስኑ ሕይወታቸው አደጋ ላይ ወድቆ ነበር። ውሳኔያቸው ሊያስከትልባቸው የሚችለውን ሞት እንኳ ለመጋፈጥ ተዘጋጅተው ነበር። ሆኖም የአምላክን በረከትና በእርሱ ዘንድ ተቀባይነትን እንደሚያገኙ ያውቁ ነበር።​—⁠ዳንኤል 3:​16-19

በማስተዋል ላይ የተመሠረተ ውሳኔ ካደረግን በኋላ አንዳንድ ችግሮች ቢያጋጥሙን ውሳኔው ስህተት ነበር ብለን መደምደም አይኖርብንም። “ጊዜና አጋጣሚ” በጥሩ የልብ ግፊት የተደረጉ ውሳኔዎችን ውጤት ሳይቀር በመጥፎ ሊነካ ይችላል። (መክብብ 9:​11 NW ) ከዚህም በላይ ይሖዋ አንዳንድ ጊዜ ቁርጠኝነታችንን ለመመዘን ፈተናዎች እንዲደርሱብን ሊፈቅድ ይችላል። ያዕቆብ ምርቃት ለማግኘት ሌሊቱን ሙሉ ከመልአኩ ጋር መታገል አስፈልጎት ነበር። (ዘፍጥረት 32:24-26) እኛም ብንሆን ትክክለኛውን ነገር እያደረግንም ከፈተና ጋር መታገል ይኖርብን ይሆናል። ቢሆንም ውሳኔያችን ከአምላክ ፈቃድ ጋር የሚስማማ ከሆነ አምላክ እንድንጸና እንደሚረዳንና በመጨረሻም እንደሚባርከን እርግጠኞች መሆን እንችላለን።​—⁠2 ቆሮንቶስ 4:7

ስለዚህ ከበድ ያለ ውሳኔ በምታደርግበት ወቅት በገዛ ራስህ ጥበብ አትታመን። ተግባራዊ ሊሆኑ የሚችሉ የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶችን መርምር። ስለ ጉዳዩ ይሖዋን አነጋግረው። የሚቻል ከሆነ የጎለመሱ ክርስቲያን ባልንጀሮችህን አማክር። ከዚያም ደፋር በመሆን አምላክ የሰጠህን የመምረጥ ነፃነት ኃላፊነት ባለው መንገድ ተጠቀምበት። ጥበብ ያለበት ውሳኔ በማድረግ ልባችሁ በይሖዋ ፊት ቅን እንደሆነ አሳዩ።

[በገጽ 28 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ከባድ ውሳኔዎች ከማድረጋችሁ በፊት የአምላክን ቃል መርምሩ

[በገጽ 29 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ማድረግ ስላለባችሁ ውሳኔ ለይሖዋ ንገሩት

[በገጽ 30 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ከባድ ውሳኔዎቻችሁን በተመለከተ ከጎለመሱ ክርስቲያኖች ጋር መወያየት ትችላላችሁ