በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

“ወደ ቄሣር ይግባኝ ብዬአለሁ!”

“ወደ ቄሣር ይግባኝ ብዬአለሁ!”

“ወደ ቄሣር ይግባኝ ብዬአለሁ!”

በቁጣ ገንፍሎ የወጣው ሕዝብ ራሱን መከላከል የሚችልበት መንገድ የሌለውን አንድ ሰው መደብደብ ጀመረ። የሕዝቡ አቋም ሰውዬው ሞት ይገባዋል የሚል ነው። አለቀለት፣ አይተርፍም በሚባልበት ሰዓት ላይ ወታደሮች ደርሰው ሰውዬውን እንደምንም ብለው በቁጣ ካበደው ሕዝብ አስጣሉት። ሰውዬው ሐዋርያው ጳውሎስ ሲሆን ደብዳቢዎቹ የጳውሎስን ስብከት አምርረው የሚቃወሙና ቤተ መቅደስ አርክሷል ብለው የሚከሱት አይሁዳውያን ናቸው። ከሞት ያዳኑት ሰዎች ደግሞ ቀላውዴዎስ ሉስዮስ በሚባል አዛዥ የሚመሩ ሮማውያን ናቸው። ጳውሎስ በግርግሩ መካከል በወንጀለኝነት ተጠርጥሮ ተያዘ።

የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ የመጨረሻዎቹ ሰባት ምዕራፎች ጳውሎስ ከተያዘበት ጊዜ አንስቶ ስለተከሰቱት ሁኔታዎች ይተርካሉ። ጳውሎስ ሕግ ፊት ቀርቦ ስላሳለፈው ታሪክ፣ በእርሱ ላይ ስለተመሠረተው ክስ፣ እሱ ስላቀረበው የመከላከያ ሐሳብ እንዲሁም ስለ ሮማውያን የፍርድ አሰጣጥ ሂደት የተወሰነ እውቀት ማግኘታችን እነዚህን ምዕራፎች ጥሩ አድርገን መረዳት እንችል ዘንድ ተጨማሪ ብርሃን ይፈነጥቅልናል።

በቀላውዴዎስ ሉስዮስ ጥበቃ ሥር

የቀላውዴዎስ ሉስዮስ ኃላፊነት በኢየሩሳሌም ውስጥ ጸጥታ ማስጠበቅንም ይጨምራል። የእርሱ የበላይ የነበረው ሮማዊው የይሁዳ አገረ ገዥ በቂሣርያ ይኖር ነበር። ሉስዮስ በጳውሎስ ላይ የወሰደው እርምጃ አንድ ግለሰብ ሊደርስበት ከሚችለው አደጋ ለመጠበቅ ወይም ሁከት ፈጣሪውን በቁጥጥር ሥር ለማዋል የተደረገ እርምጃ እንደሆነ ተደርጎ ሊቆጠር ይችላል። የአይሁዳውያን ሁከት እየተባባሰ በሄደ ጊዜ ሉስዮስ እስረኛውን በአንቶኒያ ግንብ ወደሚገኘው ጦር ሠፈር እንዲወስደው አስገደደው።​—⁠ሥራ 21:​27–22:​24

ሉስዮስ፣ ጳውሎስ ምን እንዳጠፋ ለማወቅ ፈልጓል። ከፍተኛ ሁካታ ስለነበረ ምንም ማወቅ አልቻለም። ስለዚህ ጊዜ ሳያጠፋ ‘ሕዝቡ በጳውሎስ ላይ እንዲህ የሚጮኽበትን ምክንያት ለማወቅ ጳውሎስ እየተገረፈ እንዲመረመር’ ትእዛዝ አስተላለፈ። (ሥራ 22:​24) ግርፊያ ከወንጀለኞች፣ ከባሪያዎችና ከተራ ሰዎች መረጃ ለማውጣጣት የሚሠራበት የተለመደ ዘዴ ነበር። ለዚህ ዓላማ የሚጠቀሙበት አለንጋ (ፍሌግሩም ) ውጤታማ ሊሆን ቢችልም በጣም አሰቃቂ መሣሪያ ነበር። ከአለንጋዎቹ መካከል አንዳንዶቹ ድቡልቡል ብረቶች የተንጠለጠለባቸው ሰንሰለቶች ናቸው። ሌሎቹ ደግሞ ሹል የአጥንት ስብርባሪዎችና ቁርጥራጭ ብረቶች የታሠሩባቸው የተገመዱ የቆዳ ጠፍሮች ናቸው። አለንጋዎቹ ሰውነትን በመተልተል ክፉኛ ያቆስላሉ።

በዚህ ጊዜ ጳውሎስ ሮማዊ ዜግነት ያለው መሆኑን ተናገረ። አንድን ሮማዊ ሳይፈረድበት መግረፍ ስለማይቻል ጳውሎስ ዜግነቱን መናገሩ ፈጣን ለውጥ አስገኝቶለታል። ሮማዊ ዜግነት ያለውን አንድ ሰው ማንገላታት ወይም መደብደብ አንድን ሮማዊ ባለ ሥልጣን ቦታውን ሊያሳጣው ይችላል። ይህም ጳውሎስ ልዩ አስተያየት ተደርጎለት ጠያቂዎችን ተቀብሎ የማነጋገር ልዩ መብት አስገኝቶለታል።​—⁠ሥራ 22:​25-29፤ 23:​16, 17

ሉስዮስ ስለ ክሱ ምንም የተጨበጠ ነገር ስላላገኘ ሁከቱ የተፈጠረበትን ምክንያት ለማወቅ ጳውሎስን በሳንሄድሪን ሸንጎ ፊት አቆመው። ሆኖም ጳውሎስ በትንሣኤ ተስፋ በማድረጉ ምክንያት መከሰሱን ሲናገር በመካከላቸው ጠብ ተፈጠረ። ጠቡ በጣም ከመባባሱ የተነሳ ሉስዮስ በንዴት የበገኑት አይሁዳውያን ጳውሎስን እንዳይገነጣጥሉት በመስጋት ለሁለተኛ ጊዜ ከግርግሩ መሃል ነጥቆ አወጣው።​—⁠ሥራ 22:​30–23:​10

ሉስዮስ አንድ ሮማዊ በእርሱ እጅ እያለ እንዲሞት አልፈለገም። ጳውሎስን ለመግደል ሴራ መጠንሰሱን ሲሰማ በአፋጣኝ ወደ ቂሣርያ እንዲወሰድ አደረገ። እስረኞች ወደ ከፍተኛ የሕግ ባለ ሥልጣናት በሚላኩበት ጊዜ ጉዳዩን የሚያስረዳ አባሪ ደብዳቤ አብሮ እንዲላክ ሕጉ ያዝዝ ነበር። እንዲህ ያለው ሪፖርት የመጀመሪያውን የምርመራ ውጤት፣ እርምጃው የተወሰደበትን ምክንያት እንዲሁም መርማሪው ስለ ጉዳዩ ያለውን አመለካከት የሚያካትት መሆን ይኖርበታል። ሉስዮስ በደብዳቤው ላይ ጳውሎስ ‘የአይሁድን ሕግ በሚመለከት መከሰሱንና ይህም ለሞት ወይም ለእስራት የሚያበቃው አለመሆኑን’ እንዲሁም የጳውሎስ ከሳሾች አቤቱታቸውን በአውራጃው ሹም በፊልክስ ፊት እንዲያሰሙ መንገሩን ጠቅሷል።​—⁠ሥራ 23:​29, 30

አገረ ገዥው ፊልክስ ፍርድ መስጠት ተሳነው

የአውራጃው ፍርድ አሰጣጥ ሂደት በፊልክስ እጅ ነበር። ከፈለገ የአካባቢውን ደንብ አሊያም በማኅበረሰቡ ውስጥ ከፍተኛ ቦታ ያላቸው ሰዎችንና የመንግሥት ባለ ሥልጣናትን ለመዳኘት የወጣውን የወንጀለኛ መቅጫ ሕግ መከተል ይችላል። ይህ ኦርዶ ወይም ሕጋዊ መዝገብ ይባላል። እንዲሁም ማንኛውንም ዓይነት ወንጀል ለመዳኘት የሚያስችል ሕግ ማውጣት ይችላል። ይህ ደግሞ ኤክስትራ ኦርዲነም ይባላል። አንድ የአውራጃ አስተዳዳሪ አንድን ጉዳይ ማየት የሚኖርበት ‘ሮም ላይ ከሚሠራበት አንጻር ሳይሆን በአጠቃላይ መደረግ ከሚኖርበት አንጻር ’ ነበር። ስለሆነም ፍርዱ በአብዛኛው ለእርሱ የተተወ ነበር።

በጥንቷ ሮም ይሠራበት የነበረውን ሕግ በዝርዝር ማወቅ አስቸጋሪ ቢሆንም የጳውሎስ ጉዳይ ኤክስትራ ኦርዲነም ለሚባለው የአውራጃ ፍርድ አሰጣጥ ሂደት ግሩም ምሳሌ ሆኖ” ሊጠቀስ የሚችል ነው። አስተዳዳሪው በአማካሪዎቹ እየተረዳ ግለሰቦች የሚያቀርቡትን ክስ ያደምጣል። ከዚያም ተከሳሹ ይጠራና በከሳሹ ፊት ቆሞ የመከላከያ ሐሳብ ያቀርባል። ሆኖም ማስረጃ የማቅረቡ ኃላፊነት ለከሳሹ የተተወ ነው። በፍርድ ወንበሩ ላይ የተቀመጠው ባለሥልጣን ተገቢ የመሰለውን ቅጣት ይበይናል። ከፈለገ ወዲያውኑ ፍርድ መስጠት ይችላል፤ ካልሆነም ላልተወሰነ ጊዜ ማስተላለፍ ይችላል። እስከዚያው ድረስ ግን ተከሳሹ እስር ቤት ይቆያል። ሔንሪ ካድበሪ የተባሉ አንድ ምሁር “እንዲህ ያለው ገደብ የለሽ ሥልጣን ሹሙ ‘ተገቢ ላልሆነ ስሜት እንዲሸነፍና’ ተከሳሹን በነጻ ለማሰናበት፣ ጥፋተኛ ነህ ብሎ ለመፍረድ ወይም ጉዳዩን ለማጓተት በጉቦ ለመደለል መንገድ እንደሚከፍት ምንም ጥርጥር የለውም” ብለዋል።

ሊቀ ካህናቱ ሐናንያ፣ የአይሁድ ሽማግሌዎችና ጠርጠሉስ ጳውሎስን ‘በአይሁዳውያን መካከል ሁከት የሚያስነሳ በሽታ’ ሆኗል በማለት በፊልክስ ፊት ከሰውታል። በተጨማሪም “የናዝራውያን ወገን” ቀንደኛ መሪ ነው እንዲሁም ቤተ መቅደሱን ለማርከስ ሞክሯል በማለት ከሰሱት።​—⁠ሥራ 24:​1-6

መጀመሪያ ላይ ጳውሎስን የደበደቡት ሰዎች ጥሮፊሞስ የተባለውን አሕዛብ ለአይሁዳውያን ብቻ ወደተፈቀደው አደባባይ ያስገባው መስሏቸው ነበር። a (ሥራ 21:​28, 29) እንደ እውነቱ ከሆነ ሕግ ተላልፏል መባል የነበረበት ጥሮፊሞስ ነው። ሆኖም አይሁዳውያኑ ጳውሎስ አድርጎታል ብለው ያሰቡትን ነገር ሕግ ተላላፊውን እንደ መርዳት ወይም እንደ ማደፋፈር አድርገው ቆጥረውት ከሆነ እሱም ቢሆን ሞት የሚገባው ጥፋት ተገኝቶበታል ሊባል ይችል ነበር። ይህ ጥፋት ለሞት የሚያበቃ ወንጀል ነው የሚለውን ጉዳይ ሮምም እውቅና ሰጥታው የነበረ ይመስላል። ስለሆነም ጳውሎስ በሉስዮስ ሳይሆን በአይሁድ ቤተ መቅደስ ጠባቂዎች ተይዞ ቢሆን ኖሮ ሳንሄድሪን ያለ ምንም ችግር ጉዳዩን አይቶ ብይን ሊሰጠው ይችል ነበር።

አይሁዳውያን ጳውሎስ የሚያስተምረው የአይሁድን እምነት ወይም ሕጋዊ እውቅና ያገኘን ሃይማኖት (ሪሊጂዮ ሊኪታ) አይደለም የሚል አመለካከት ነበራቸው። ይልቁንም ሕገ ወጥ እንዲያውም ዓመፅን የሚያነሳሳ ትምህርት ተደርጎ መታየት አለበት ይላሉ።

በተጨማሪም ጳውሎስ “በሽታ ሆኖ በዓለም ባሉት አይሁድ ሁሉ ሁከት” አስነስቷል ብለውታል። (ሥራ 24:​5) ንጉሥ ቀላውዴዎስ በዚያው ወቅት አካባቢ በእስክንድርያ የሚኖሩ አይሁዳውያንን “በመላው ዓለም ወረርሽኝ አስፋፍተዋል” በማለት አውግዟቸው ነበር። የወቀሳው መመሳሰል የሚያስደንቅ ነው። አድሪያን ኤን ሼርዊን ዊት የተባሉ አንድ ታሪክ ጸሐፊ እንዲህ ብለዋል:- “ይህ ክስ በንጉሥ ቀላውዴዎስ ዘመነ መንግሥት ወይም በኔሮ አስተዳደር የመጀመሪያዎቹ ዓመታት ውስጥ በአንድ አይሁዳዊ ላይ ተቃውሞ ለማነሳሳት የተሰነዘረ ነበር። አይሁዳውያን አገረ ገዥው የጳውሎስ ስብከት በሮም ግዛት ሥር በሚገኙ የአይሁድ ማኅበረሰቦች ውስጥ ብጥብጥ የሚፈጥር ነው ብለው ለማሳመን እየሞከሩ ነበር። አገረ ገዥዎቹ ሃይማኖታዊ በሆነ ጉዳይ ውስጥ እጃቸውን እንደማያስገቡ ስለገባቸው ጉዳዩን ወደ ፖለቲካ ለመጠምዘዝ እየሞከሩ ነበር።”

ጳውሎስ የመከላከያ መልሱን አንድ በአንድ አቀረበ። ‘ምንም ዓይነት ሁከት አልፈጠርኩም። እርግጥ ነው እነርሱ “ኑፋቄ” ብለው ከሚጠሩት ወገን ነኝ። ሆኖም ይህ ራሱ የሚያሳየው የአይሁድን ሕግ የምከተል መሆኔን ነው። ረብሻውን የቀሰቀሱት አንዳንድ የእስያ አይሁዶች ናቸው። ክስ ካላቸው እዚህ መጥተው አቤቱታቸውን ማቅረብ ነበረባቸው።’ ጳውሎስ ጉዳዩ በአይሁዳውያን መካከል የተፈጠረ ሃይማኖታዊ አለመግባባት እንደሆነ አድርጎ አቅርቦታል። ሮማውያን ደግሞ ይህን ዓይነቱን ጉዳይ ለመዳኘት እምብዛም ብቃት አልነበራቸውም። ፊልክስ በቋፍ ላይ የሚገኙትን አይሁዳውያንን ይበልጥ እንዳያበሳጫቸው በመስጋት ጉዳዩን በእንጥልጥል ተወው። ጳውሎስ ጉዳዩን ማየት ያለብን እኛ ነን ለሚሉት አይሁዳውያን አልፎ አልተሰጠም ወይም በሮማውያን ሕግ መሠረት አልተዳኘም ወይም ደግሞ በነጻ አልተሰናበተም። ፊልክስ ያኔውኑ ውሳኔ እንዲሰጥ የሚያስገድደው ምክንያት ያልነበረ ከመሆኑ ሌላ አይሁዳውያኑን ደስ ለማሰኘት ሲልና ጳውሎስ ጉቦ እንዲሰጠው ተስፋ በማድረግ ጉዳዩን ለሌላ ጊዜ አስተላልፎታል።​—⁠ሥራ 24:​10-19, 26 b

በጶርቅዮስ ፊስጦስ ዘመን የተከሰተው ለውጥ

ከሁለት ዓመት በኋላ ጶርቅዮስ ፊስጦስ የተባለ አዲስ አገረ ገዥ በኢየሩሳሌም ሥልጣን ሲይዝ አይሁዳውያን ክሳቸውን እንደገና በማንሳት ጳውሎስን አሳልፎ እንዲሰጣቸው ጥያቄ አቀረቡ። ሆኖም ፊስጦስ “ተከሳሹ በከሳሾቹ ፊት ለፊት ሳይቆም ለተከሰሰበትም መልስ ይሰጥ ዘንድ ፈንታ ሳያገኝ፣ ማንንም ቢሆን አሳልፎ መስጠት የሮማውያን ሥርዓት አይደለም” የሚል ቁርጥ ያለ መልስ ሰጣቸው። ታሪክ ጸሐፊው ሃሪ ደብሊው ታሽራ “ፊስጦስ፣ ሕግን በመንተራስ አንድን ሮማዊ ለመግደል ሴራ እንደተጠነሰሰ ገብቶት ነበር” በማለት ጽፈዋል። ስለሆነም አይሁዳውያን ቂሣርያ ሄደው ክሳቸውን እንዲያቀርቡ ተነገራቸው።​—⁠ሥራ 25:​1-6, 16

እዚያም አይሁዳውያን ‘በሕይወት ይኖር ዘንድ አይገባውም’ በማለት ስለ ጳውሎስ ቢናገሩም ያቀረቡት አንድም ማስረጃ አልነበረም። ጳውሎስ ለሞት የሚያበቃ ምንም ወንጀል እንዳልሠራ ፊስጦስ ተገንዝቦ ነበር። ፊስጦስ “ስለ ገዛ ሃይማኖታቸውና ጳውሎስ:- ሕያው ነው ስለሚለው ስለ ሞተው ኢየሱስ ስለ ተባለው ከእርሱ ጋር ይከራከሩ ነበር” በማለት ለአንድ ለሌላ ባለ ሥልጣን ስለ ሁኔታው ተናግሮ ነበር።​—⁠ሥራ 25:​7, 18, 19, 24, 25

ጳውሎስ ከቀረበበት ከማንኛውም ዓይነት ፖለቲካዊ ክስ ነጻ መሆኑ ተረጋገጠ። ሆኖም አይሁዳውያን ሃይማኖታዊ ውዝግቦችን ለመዳኘት ብቃት ያለው የእነርሱ ፍርድ ቤት ብቻ እንደሆነ ሳይከራከሩ አልቀረም። ታዲያ ጳውሎስ በዚህ ጉዳይ ላይ ፍርድ ለማግኘት ወደ ኢየሩሳሌም ይሄድ ይሆን? ፊስጦስ ወደ ኢየሩሳሌም መሄድ ይፈልግ እንደሆነ ጳውሎስን ጠይቆት ነበር። ሆኖም ይህ ፈጽሞ የማይታሰብ ነበር። ጳውሎስን ከሳሾቹ ራሳቸው ዳኛ ሆነው በተቀመጡበት በኢየሩሳሌም እንዲዳኝ መላክ ለአይሁዳውያን አሳልፎ እንደመስጠት ይቆጠራል። ጳውሎስ “እፋረድበት ዘንድ በሚገባኝ በቄሣር ፍርድ ወንበር ፊት ቆሜአለሁ። አይሁድን ምንም አልበደልሁም። . . . ለእነርሱ አሳልፎ ይሰጠኝ ዘንድ ማንም አይችልም፤ ወደ ቄሣር ይግባኝ ብዬአለሁ” አለ።​—⁠ሥራ 25:​10, 11, 20

አንድ ሮማዊ እነዚህን ቃላት ከተናገረ በአውራጃ ደረጃ ፍርድ የመስጠት ሂደቱ ሙሉ በሙሉ ይቋረጣል። ይግባኝ የመጠየቅ መብቱ (ፕሮቮካትዮ ) “ትክክለኛ፣ ሁኔታዎችን ያገናዘበና ውጤታማ” ነበር። ስለዚህ ፊስጦስ ከአማካሪዎቹ ጋር ከመከረ በኋላ “ወደ ቄሣር ይግባኝ ብለሃል፤ ወደ ቄሣር ትሄዳለህ” አለው።​—⁠ሥራ 25:​12

ፊስጦስ የጳውሎስ ጉዳይ ከእጁ በመውጣቱ ተደስቶ ነበር። ከጥቂት ቀናት በኋላ ለዳግማዊ ሄሮድስ አግሪጳ እንደተናገረው ጉዳዩ ግራ አጋብቶት ነበር። ፊስጦስ ለንጉሠ ነገሥቱ ጉዳዩን የሚያብራራ ደብዳቤ መጻፍ ነበረበት። ሆኖም ጉዳዩ ከአይሁድ ሕግ ጋር የተያያዘ በመሆኑ ፈጽሞ የማይገባና ውስብስብ ሆኖበታል። ይሁን እንጂ አግሪጳ እንዲህ ላለው ጉዳይ መፍትሔ አያጣም። ስለዚህ አግሪጳ ጉዳዩን ማየት እንደሚፈልግ ሲናገር ደብዳቤውን በማርቀቅ ረገድ እንዲረዳ ተጠየቀ። ከዚያ በኋላ ጳውሎስ ለአግሪጳ የተናገረው ሁሉ አልጨበጥልህ ስላለው ፊስጦስ “ጳውሎስ ሆይ፣ አብደሃል እኮ፤ ብዙ ትምህርትህ ወደ እብደት ያዞርሃል” አለው። ሆኖም አግሪጳ ሁሉም ነገር በትክክል ገብቶታል። “በጥቂት ክርስቲያን ልታደርገኝ ትወዳለህ” አለው። ፊስጦስና አግሪጳ ጳውሎስ ስላቀረበው የመከላከያ ሐሳብ ምንም ይሰማቸው ምን ጥፋት እንደሌለበትና ወደ ቄሣር ይግባኝ ባይል ኖሮ ሊፈታ ይችል እንደነበር ተሰምቷቸዋል።​—⁠ሥራ 25:​13-27፤ 26:​24-32

የተጓተተው ፍርድ መቋጫ

ጳውሎስ ሮም ከደረሰ በኋላ ሊሰብክላቸው ፈልጎ ብቻ ሳይሆን ስለ እርሱ የሚያውቁት ነገር ይኖር እንደሆነ ለማወቅ ታላላቅ የአይሁድ ሰዎችን ወደ እርሱ አስጠራ። ይህን ማድረጉ ከከሳሾቹ ወገን የሆኑትን ሰዎች ስሜት ለመረዳት ሳያስችለው አልቀረም። በኢየሩሳሌም የሚኖሩ ባለ ሥልጣናት አንድን ክስ እንዲከታተሉላቸው በሮም የሚኖሩ አይሁዳውያንን እርዳታ መጠየቃቸው ያልተለመደ አልነበረም። ሆኖም ጳውሎስ ስለ እርሱ ምንም መረጃ እንዳልደረሳቸው ነገሩት። ጳውሎስ ፍርዱን እየተጠባበቀ እያለ ቤት ተከራይቶ በነጻነት እንዲሰብክ ተፈቀደለት። እንዲህ ያለው ለዘብተኛ አያያዝ ጳውሎስ በሮማውያን ዘንድ ጥፋተኛ እንደሆነ ተደርጎ እንዳልታየ የሚያሳይ ሊሆን ይችላል።​—⁠ሥራ 28:​17-31

ጳውሎስ ለሁለት ተጨማሪ ዓመታት ማረፊያ ቤት ቆይቷል። ለምን? መጽሐፍ ቅዱስ በዝርዝር አይገልጽም። ከሳሽ ቀርቦ ክሱን እስኪያንቀሳቅስ ድረስ ይግባኝ ባዩ እንደታሰረ መቆየቱ ያለ ነገር ቢሆንም በኢየሩሳሌም የሚኖሩ አይሁዳውያን ክሱ እንደማያዋጣቸው በመገንዘብ ሳይሆን አይቀርም የውኃ ሽታ ሆነው ቀሩ። ጳውሎስን በተቻለ መጠን ረዘም ላለ ጊዜ ጸጥ ማሰኘት የሚቻልበት የተሻለው ዘዴ ፍርድ ቤት አለመቅረብ እንደሆነ ተሰምቷቸው ሊሆን ይችላል። ያም ሆነ ይህ ጳውሎስ በኔሮ ፊት ቀርቦ ጥፋተኛ አለመሆኑ ተፈርዶለት ከተያዘ ከአምስት ዓመት ገደማ በኋላ ተለቅቆ ሚስዮናዊ አገልግሎቱን የቀጠለ ይመስላል።​—⁠ሥራ 27:​24

ከረጅም ጊዜ በፊት አንስቶ የእውነት ጠላቶች ክርስቲያኖች የሚያከናውኑትን የስብከት ሥራ ለማስተጓጎል ‘ሕግን በመንተራስ ዓመፅ ሲሠሩ’ ኖረዋል። ይህ ሊያስደንቀን አይገባም። ኢየሱስ “እኔን አሳደውኝ እንደ ሆኑ እናንተን ደግሞ ያሳድዱአችኋል” በማለት ተናግሯል። (መዝሙር 94:​20፤ ዮሐንስ 15:​20) ያም ሆኖ ኢየሱስ ለመላው ዓለም ወንጌሉን እንድንሰብክ ነጻነት እንደሚሰጠን ቃል ገብቶልናል። (ማቴዎስ 24:​14) ስለሆነም ሐዋርያው ጳውሎስ የደረሰበትን ስደትና ተቃውሞ እንደተቋቋመ ሁሉ ዛሬም የይሖዋ ምሥክሮች ‘ምሥራቹን ለመከላከልና በሕግ ለማስከበር’ ይጥራሉ።​—⁠ፊልጵስዩስ 1:​7 NW

[የግርጌ ማስታወሻ]

a የአሕዛብን አደባባይ ከውስጠኛ አደባባይ የሚለይ ሦስት ክንድ ከፍታ ያለው አንድ የግንብ አጥር ይገኛል። በዚህ ግድግዳ ላይ አንዳንዱ በግሪክኛ ሌላው ደግሞ በላቲንኛ የሚከተለው ማስጠንቀቂያ ተጽፎበታል:- “ማንኛውም የባዕድ አገር ሰው ይህን ግድግዳ ወይም በቤተ መቅደሱ ዙሪያ ያለውን አጥር አልፎ መግባት አይኖርበትም። ገብቶ የተገኘ ማንኛውም ሰው ለሚከተለው የሞት ቅጣት ተጠያቂው ራሱ ነው።”

b እንዲህ ማድረግ በእውነቱ ሕገ ወጥ ነበር። አንድ ምንጭ እንደሚከተለው ይላል:- “እጅ መንሻን አስመልክቶ በወጣው ሕግ ማለትም በሌክስ ሬፒቱነደሩም ላይ እንደተገለጸው አንድ ባለ ሥልጣን ወይም አስተዳዳሪ አንድን ሰው ለማሰርም ሆነ ለመፍታት፣ ብይን ለመስጠትም ሆነ ላለመስጠት ወይም አንድን እስረኛ በነጻ ለማሰናበት ጉቦ መጠየቅም ሆነ መቀበል ፈጽሞ የተከለከለ ነው።”