በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

“አምላክን ማገልገል እፈልግ ነበር”

“አምላክን ማገልገል እፈልግ ነበር”

የመንግሥቱ አዋጅ ነጋሪዎች ሪፖርት

“አምላክን ማገልገል እፈልግ ነበር”

“ሕዝቤ ሆይ . . . ከእርስዋ ዘንድ ውጡ።” ይህ ሐዋርያው ዮሐንስ በመጀመሪያው መቶ ዘመን እዘአ የሰማው መላእክታዊ ጥሪ ነው። በዘመናችን በሚልዮን የሚቆጠሩ ቅን ልብ ያላቸው ሰዎች ለጥሪው ምላሽ በመስጠት የዓለም የሐሰት ሃይማኖት ግዛት ከሆነችው ከ“ታላቂቱ ባቢሎን” ሸሽተው ወጥተዋል። (ራእይ 18:1-4) ከእነዚህ ሰዎች መካከል በሄይቲ የሚኖረው ቪልኔር ይገኝበታል። እንዲህ ሲል ተሞክሮውን ይናገራል:-

“የተወለድኩት በ1956 በሄይቲ፣ ሳን ማርክ በምትባል ትንሽ ከተማ አጥባቂ ካቶሊክ በሆኑ ቤተሰቦች ውስጥ ነበር። ከምንኖርበት ከተማ እኔና ሌሎች ሁለት ሰዎች በሳን ሚሼል ዳ ሌቴሌይ፣ ሄይቲ በሚገኝ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት እንድንማር ስንመረጥ ቤተሰቦቼ ምን ያህል እንደተደሰቱ ልትገምቱ ትችላላችሁ። ከዚያም በ1980 ተጨማሪ ስልጠና ለመውሰድ ወደ ስቴቭሎ፣ ቤልጅየም ተላክን። እዚያው እያለን በካቶሊክ ዩኒቨርሲቲ ገብተን ተምረናል።

“መጀመሪያ ላይ ቄስ ለመሆን በጣም ጓጉቼ ነበር። አንድ ቀን በምሳ ክፍሉ ውስጥ እያለሁ የቡድናችን ኃላፊ የሆኑት አንድ ቄስ የሚነግሩኝ ነገር ስላላቸው ለጥቂት ደቂቃዎች እንድቆይ ጠየቁኝ። አፍ አውጥተው ለጾታ ግንኙነት እንደሚፈልጉኝ ሲነግሩኝ ምን ያህል እንደ ደነገጥኩ አስቡት! ጥያቄውን አልተቀበልኩትም፤ ሆኖም ያልጠበቅሁት በመሆኑ ጨርሶ ግራ ተጋባሁ። ለቤተሰቦቼ ስለሁኔታው ጻፍኩላቸውና በውሳኔዬ ቅር ቢሰኙም ከጥቂት ወራት በኋላ ትምህርት ቤቱን ለቅቄ ወጣሁ። በመንደሩ ውስጥ መጠለያ አገኘሁና ሌላ ሙያ መማር ጀመርኩ።

“ወደ ሳን ማርክ ስመለስ በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ላይ የነበረኝ እምነት ሙሉ በሙሉ ጠፍቶ ነበር። ምን ማድረግ እንዳለብኝ ባላውቅም አምላክን ማገልገል እፈልግ ነበር። ወደ አድቬንቲስት፣ ኤቤኔዜር እና ሞርሞን ቤተ ክርስቲያኖች ሄድኩ። በመንፈሳዊ ሁኔታ ግራ ተጋብቼ ነበር።

“ከዚያም ቤልጂየም በሚገኘው መንፈሳዊ ትምህርት ቤት እያለሁ አነብበው የነበረውን በክራምፖን የተዘጋጀውን መጽሐፍ ቅዱስ አስታወስኩ። ከዚህ መጽሐፍ ቅዱስ አምላክ ስም እንዳለው መረዳት ችዬ ነበር። ስለዚህ አምላክ እውነተኛውን ሃይማኖት ማወቅ እንድችል እንዲረዳኝ ስሙን እየጠራሁ አጥብቄ ጸለይኩ።

“ብዙም ሳይቆይ ሁለት የይሖዋ ምሥክሮች እኔ ወዳለሁበት አካባቢ ተዛወሩ። ረጋ ያሉ፣ ሰው አክባሪዎችና ሥርዓታማ ናቸው። አኗኗራቸው በጣም አስደነቀኝ። አንድ ቀን አንደኛዋ ምሥክር በዓመታዊው የክርስቶስ ሞት መታሰቢያ በዓል ላይ እንድገኝ ጋበዘችኝ። በስብሰባው በጣም ከመደሰቴ የተነሳ ከምሥክሮቹ ጋር ቋሚ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ለማድረግ ተስማማሁ። በስድስት ወር ጊዜ ውስጥ አምላክን ለማገልገል የሚያስችለኝን ትክክለኛ መንገድ እንዳገኘሁ እርግጠኛ ሆንኩ። ሕይወቴን ለይሖዋ ወሰንኩና ኅዳር 20, 1988 ተጠመቅሁ።”

ከጊዜ በኋላ ቪልኔር የሙሉ ጊዜ አገልግሎት ጀመረ። ዛሬ ቪልኔር የጉባኤ ሽማግሌ ሲሆን እሱና ሚስቱ ከሁለት ልጆቻቸው ጋር በጉባኤው ውስጥ በደስታ ያገለግላሉ።

[በገጽ 9 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ቪልኔር መጽሐፍ ቅዱስን በማንበብ የአምላክ ስም ይሖዋ መሆኑን ተገንዝቧል