በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የአንባብያን ጥያቄዎች

የአንባብያን ጥያቄዎች

የአንባብያን ጥያቄዎች

“በኢየሱስ ስም” እንደሚሉ ያሉ መግለጫዎችን ሳይጠቀሙ ወደ አምላክ በጸሎት መቅረብ ተገቢ ነውን?

መጽሐፍ ቅዱስ ወደ ይሖዋ በጸሎት መቅረብ የሚፈልጉ ክርስቲያኖች በኢየሱስ ስም መጠቀም እንዳለባቸው ይገልጻል። ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን “በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም” ብሏቸው ነበር። አክሎም “አብም ስለ ወልድ እንዲከበር በስሜ የምትለምኑትን ሁሉ አደርገዋለሁ። ማናቸውንም ነገር በስሜ ብትለምኑ እኔ አደርገዋለሁ” በማለት ተናግሯል።​—⁠ዮሐንስ 14:​6, 13, 14

ሳይክሎፒዲያ ኦቭ ቢብሊካል፣ ቲኦሎጂካል ኤንድ ኤክሊስያስቲካል ሊትረቸር የኢየሱስን የላቀ ቦታ አስመልክቶ የሚከተለውን ብሏል:- “ጸሎት የሚቀርበው በኢየሱስ በኩል ለአምላክ ብቻ ነው። በመሆኑም ለቅዱሳን ወይም ለመላእክት የሚቀርበው ልመና ሁሉ ፋይዳ ቢስ ከመሆኑም በላይ አምላክን እንደ መስደብ ይቆጠራል። ፍጥረቱ የቱንም ያህል ክብር ቢኖረው ለፍጥረት የሚሰጠው ማንኛውም ዓይነት አምልኮ የጣዖት አምልኮ ሲሆን ይህም በአምላክ ቅዱስ ሕግ ውስጥ በጥብቅ ተወግዟል።”

ታዲያ አንድ ሰው በጣም አስደሳች ነገር ቢገጥመውና “በኢየሱስ ስም” የሚለውን መግለጫ ሳይጠቀም “አመሰግንሃለሁ ይሖዋ” ብቻ ቢልስ? ይህ ስህተት ነውን? ላይሆን ይችላል። ለምሳሌ ያህል አንድ ክርስቲያን ድንገተኛ አደጋ አጋጠመውና “ይሖዋ እርዳኝ!” ብሎ ጮኸ እንበል። ግለሰቡ “በኢየሱስ ስም” ስላላለ ብቻ አምላክ አገልጋዩን ከመርዳት ወደኋላ ይላል ማለት አይቻልም።

እንዲያውም ድምፅ አውጥቶ ለአምላክ መናገር በራሱ ጸሎት ማለት እንዳልሆነ ሊጤን ይገባዋል። ለምሳሌ ያህል ቃየን ወንድሙን በመግደሉ ምክንያት ፍርዱን ከይሖዋ ከተቀበለ በኋላ “ኃጢአቴ ልሸከማት የማልችላት ታላቅ ናት። እነሆ ዛሬ ከምድር ፊት አሳደድኸኝ፤ ከፊትህም እሰወራለሁ፤ በምድርም ላይ ኰብላይና ተቅበዝባዥ እሆናለሁ፤ የሚያገኘኝም ሁሉ ይገድለኛል” ብሎ ነበር። (ዘፍጥረት 4:​13, 14) ቃየን ይህንን የተናገረው ለይሖዋ ቢሆንም እንኳ ኃጢአት ያስከተለበትን መራራ ውጤት በስሜት ግንፋሎት መግለጹ ነበር።

መጽሐፍ ቅዱስ “እግዚአብሔር ትዕቢተኞችን ይቃወማል፣ ለትሑታን ግን ጸጋን ይሰጣል” በማለት ይነግረናል። ልዑሉን አምላክ እንደ አንድ ተራ ሰው ማነጋገር ትህትና እንደጎደለን የሚያሳይ ይሆናል። (ያዕቆብ 4:​6፤ መዝሙር 47:​2፤ ራእይ 14:​7) በተጨማሪም የአምላክ ቃል ስለ ኢየሱስ ምን እንደሚል እያወቁ ሆን ብሎ ለኢየሱስ ክርስቶስ እውቅና ሳይሰጡ መጸለዩም አክብሮት የጎደለው ድርጊት ነው።​—⁠ሉቃስ 1:​32, 33

ይህ ማለት ግን ይሖዋ በምንጸልይበት ወቅት አንድ ዓይነት ስልት ወይም ሥርዓት እንድንከተል ይጠብቅብናል ማለት አይደለም። ቁም ነገሩ ያለው በግለሰቡ የልብ ዝንባሌ ላይ ነው። (1 ሳሙኤል 16:​7) በመጀመሪያው መቶ ዘመን ቆርኔሌዎስ የተባለ አንድ የሮማ ሠራዊት አዛዥ ‘ሁልጊዜ ወደ እግዚአብሔር ይጸልይ’ ነበር። ያልተገረዘ አሕዛብ የሆነው ቆርኔሌዎስ ይሖዋን የሚያመልክ ሰው አልነበረም። ቆርኔሌዎስ ጸሎቱን በኢየሱስ ስም አቅርቧል ለማለት ባይቻልም ‘ጸሎቱ በእግዚአብሔር ፊት ለመታሰቢያ እንዲሆን አርጓል።’ ለምን? ምክንያቱም ‘ልብን የሚመረምረው’ አምላክ ቆርኔሌዎስ ‘ለአምላክ ያደረና እርሱን የሚፈራ’ መሆኑን ተመልክቶ ነበር። (ሥራ 10:​2, 4፤ ምሳሌ 17:​3) ቆርኔሌዎስ ‘ስለ ናዝሬቱ ኢየሱስ’ እውቀት ካገኘ በኋላ መንፈስ ቅዱስ ተቀብሎ የተጠመቀ የኢየሱስ ደቀ መዝሙር ሆኗል።​—⁠ሥራ 10:​30-48

ለማጠቃለል ያህል የሰው ልጆች አምላክ የሚሰማቸውን ጸሎቶች የመወሰን መብት የላቸውም። አንድ ክርስቲያን አልፎ አልፎ “በኢየሱስ ስም” እንደሚሉት ያሉትን መግለጫዎች ሳይጠቀም ወደ አምላክ ቢጸልይ የጥፋተኝነት ስሜት ሊሰማው አይገባም። ይሖዋ የአቅማችንን ውስንነት የሚያውቅ ከመሆኑም በላይ ሊረዳንም ይፈልጋል። (መዝሙር 103:​12-14) “በእግዚአብሔር ልጅ” የምናምን ከሆነ “እንደ ፈቃዱ አንዳች ብንለምን” እንደሚሰማን እርግጠኞች መሆን እንችላለን። (1 ዮሐንስ 5:​13, 14) ይሁን እንጂ እውነተኛ ክርስቲያኖች በተለይ ሌሎችን ወክለው በሚጸልዩበት ጊዜ ቅዱስ ጽሑፉ ውስጥ በተገለጸው መሠረት ኢየሱስ በይሖዋ ዓላማዎች ውስጥ የሚጫወተውን ሚና ይገነዘባሉ። እንዲሁም ጸሎታቸውን በኢየሱስ በኩል ለአምላክ በማቅረብ እርሱን በታዛዥነት ለማክበር ይጥራሉ።