በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የአንባብያን ጥያቄዎች

የአንባብያን ጥያቄዎች

የአንባብያን ጥያቄዎች

አቤል የአምላክን ሞገስ ለማግኘት የእንስሳ መሥዋዕት መቅረብ እንዳለበት ያውቅ ነበርን?

ቃየንና አቤል መሥዋዕት እንዳቀረቡ የሚገልጸው የመጽሐፍ ቅዱስ ዘገባ ዝርዝር መረጃዎችን አልያዘም። ዘፍጥረት 4:​3-5 ላይ እንዲህ እናነባለን:- “ከብዙ ቀን በኋላም ቃየን ከምድር ፍሬ ለእግዚአብሔር መሥዋዕትን አቀረበ፤ አቤልም ደግሞ ከበጎቹ በኩራትና ከስቡ አቀረበ። እግዚአብሔርም ወደ አቤልና ወደ መሥዋዕቱ ተመለከተ፤ ወደ ቃየንና ወደ መሥዋዕቱ ግን አልተመለከተም።”

ቃየንና አቤል መሥዋዕት ከማቅረባቸው በፊት መሥዋዕት ስለማቅረብም ሆነ ይሖዋ ምን ዓይነት መሥዋዕት እንደሚቀበል የሚገልጽ ሐሳብ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አናገኝም። በመሆኑም ቃየንና አቤል መሥዋዕታቸውን ያቀረቡት በራሳቸው ተነሳስተው መሆን አለበት። የወላጆቻቸው የመጀመሪያ መኖሪያ ወደ ነበረችው ገነት እንዳይገቡ ተከልክለዋል። ኃጢአት የሚያስከትላቸውን ውጤቶች መመልከት የጀመሩ ሲሆን ከአምላክም ርቀው ነበር። በኃጢአት መውደቃቸው ጉስቁልና ያስከተለባቸው ሲሆን ይህም እርዳታ ለማግኘት ወደ አምላክ ዞር እንዲሉ ሳይገፋፋቸው አልቀረም። ያቀረቡት መሥዋዕት የአምላክን ሞገስ ለማግኘት በፈቃዳቸው ያቀረቡት ስጦታ ሊሆን ይችላል።

በውጤቱም አምላክ አቤል ያቀረበውን መሥዋዕት ሲቀበል የቃየንን ግን ሳይቀበል ቀረ። ለምን? አቤል ትክክለኛውን ዓይነት መሥዋዕት ሲያቀርብ ቃየን ግን እንደዚህ ስላላደረገ ነውን? ምን ዓይነት መሥዋዕት ተቀባይነት እንዳለውና ምን ዓይነት መሥዋዕት ተቀባይነት እንደሌለው ለሁለቱም ስላልተነገራቸው የመሥዋዕቱ ዓይነት ለውጥ አያመጣም ብሎ በእርግጠኝነት መናገር አይቻልም። ሆኖም ሁለቱም ዓይነት መሥዋዕት ተቀባይነት ያለው ይመስላል። ከጊዜ በኋላ ይሖዋ ለእስራኤል ብሔር በሰጠው ሕግ ውስጥ የእንስሳትና የእንስሳት አካላትን ብቻ ሳይሆን የተጠበሰ እሸት፣ የገብስ ነዶ፣ የላመ ዱቄት፣ የበሰሉ ምግቦችና ወይን መሥዋዕት ሆነው ቢቀርቡ እንደሚቀበል ተናግሯል። (ዘሌዋውያን 6:19-23፤ 7:11-13፤ 23:10-13) በግልጽ ለመረዳት እንደሚቻለው አምላክ የአንዳቸውን መሥዋዕት ሲቀበል የሌላኛቸውን ግን እንዳይቀበል ያደረገው ቃየንና አቤል ያቀረቡት የመሥዋዕት ዓይነት ብቻ አልነበረም።​—⁠ከኢሳይያስ 1:11 እና አሞጽ 5:22 ጋር አወዳድር።

ከበርካታ መቶ ዓመታት በኋላ ሐዋርያው ጳውሎስ “አቤል ከቃየል ይልቅ የሚበልጥን መሥዋዕት ለእግዚአብሔር በእምነት አቀረበ፣ በዚህም፣ እግዚአብሔር ስለ ስጦታው ሲመሰክር፣ እርሱ ጻድቅ እንደ ሆነ ተመሰከረለት” በማለት ተናግሯል። (ዕብራውያን 11:4) ስለዚህ አቤል በአምላክ ዘንድ እንደ ጻድቅ የተቆጠረው በእምነቱ ምክንያት ነው። ይሁን እንጂ ያመነው ምንድን ነው? ‘የእባቡን ራስ በመቀጥቀጥ’ የሰው ልጅ ያጣውን ሰላምና ፍጽምና መልሶ እንዲያገኝ በሚያደርገው ይሖዋ ቃል በገባው ዘር ላይ እምነት እንዳለው አሳይቷል። አቤል ዘሩ ‘ሰኰናው እንደሚቀጠቀጥ’ ከሚናገረው ሐሳብ በመነሳት የሚያቀርበው መሥዋዕት ደም ማፍሰስን የሚጨምር መሆን እንዳለበት አስቦ ሊሆን ይችላል። (ዘፍጥረት 3:15) ያም ሆነ ይህ የአቤል መሥዋዕት ‘ከቃየን ይልቅ እንዲበልጥ’ ያደረገው አቤል ያሳየው እምነት ነው።

በተመሳሳይም ቃየን ተቀባይነት ያጣው ትክክል ያልሆነ መሥዋዕት ስላቀረበ ሳይሆን ከድርጊቱ እንደታየው እምነት ስለጎደለው ነው። ይሖዋ ለቃየን “መልካም ብታደርግ ፊትህ የሚበራ አይደለምን?” በማለት በግልጽ ነግሮታል። (ዘፍጥረት 4:7) አምላክ ቃየንን ሳይቀበል የቀረው በመሥዋዕቱ ስላልተደሰተ አልነበረም። ከዚያ ይልቅ በቅናትና በጥላቻ ተነሳስቶ በፈጸመው ግድያ እንደታየው “የገዛ ሥራው ክፉ” ስለነበረ ነው።​—⁠1 ዮሐንስ 3:12