በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የአንባብያን ጥያቄዎች

የአንባብያን ጥያቄዎች

የአንባብያን ጥያቄዎች

አንደኛው ወላጅ የይሖዋ ምሥክር ሆኖ ሌላኛው ወላጅ ግን ምሥክር በማይሆንበት ጊዜ ልጆችን በማሰልጠን ረገድ ቅዱሳን ጽሑፎች ምን መመሪያ ይሰጣሉ?

የይሖዋ ምሥክር ያልሆነ የትዳር ጓደኛ ያላቸው ምሥክር ወላጆች ልጆችን በማሰልጠን ረገድ መመሪያ ለማግኘት ሁለት መሠረታዊ የሆኑ ቅዱስ ጽሑፋዊ ሥርዓቶችን መመልከት ይገባቸዋል። አንደኛው “ከሰው ይልቅ ለእግዚአብሔር ልንታዘዝ ይገባል” የሚለው ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ “ክርስቶስ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ራስ እንደ ሆነ . . . ባል የሚስት ራስ ነውና” ይላል። (ሥራ 5:29፤ ኤፌሶን 5:23) ሁለተኛው ሥርዓት ባሎቻቸው የይሖዋ ምሥክር ለሆኑ ሚስቶች ብቻ ሳይሆን ምሥክር ያልሆኑ ባሎች ላሏቸው ሚስቶችም ይሠራል። (1 ጴጥሮስ 3:1) የይሖዋ ምሥክር የሆነ ወላጅ (ባልም ሆነ ሚስት) ልጆቹን በሚያሠለጥንበት ጊዜ እነዚህን ሁለት ሥርዓቶች ተግባራዊ ማድረግ የሚችለው እንዴት ነው?

ባልየው የይሖዋ ምሥክር ከሆነ የቤተሰቡን መንፈሳዊም ሆነ ቁሳዊ ፍላጎት የማሟላት ኃላፊነት አለበት። (1 ጢሞቴዎስ 5:8) አማኝ ያልሆነችው እናት ከልጆቻቸው ጋር የበለጠ ጊዜ ልታሳልፍ ብትችልም የይሖዋ ምሥክር የሆነው አባት ቤት ውስጥ መንፈሳዊ ሥልጠና በመስጠትና ሥነ ምግባራዊ ትምህርትና ጤናማ ጓደኝነት ወደሚገኝባቸው ክርስቲያናዊ ስብሰባዎች ይዟቸው በመሄድ ልጆቹን ሊያስተምራቸው ይገባል።

አማኝ ያልሆነችው ሚስቱ ልጆቻቸውን ወደ ራስዋ የአምልኮ ቦታ መውሰድ ወይም የራሷን እምነት ማስተማር ብትፈልግስ? የአገሪቱ ሕግ እንደዚህ እንድታደርግ ይፈቅድ ይሆናል። ልጆቹ እዚያ በሚደረገው የአምልኮ ሥርዓት ለመካፈል መፈተን አለመፈተናቸው ከአባታቸው በሚያገኙት መንፈሳዊ ሥልጠና ላይ የተመካ ይሆናል። ልጆቹ እያደጉ ሲሄዱ አባታቸው የሚሰጣቸው ቅዱስ ጽሑፋዊ ትምህርት የአምላክን ቃል እውነት እንዲከተሉ ሊረዳቸው ይገባል። ልጆቹ ከእውነት ጎን ለመቆም ቢወስኑ አማኝ የሆነው አባት ምንኛ ይደሰታል!

እናትየው የይሖዋ ምሥክር ከሆነች የራስነትን መሠረታዊ ሥርዓት ሳትጥስ ለልጆችዋ ዘላለማዊ ደህንነት ማሰብ ይኖርባታል። (1 ቆሮንቶስ 11:3) አብዛኛውን ጊዜ አማኝ ያልሆነው ባል የይሖዋ ምሥክር የሆነችው ሚስቱ ለልጆቻቸው ሥነ ምግባራዊና መንፈሳዊ ሥልጠና እንዳትሰጣቸውና እንደዚህ ያለውንም ሥልጠና እንዳያገኙ ወደ የይሖዋ ሕዝቦች ስብሰባዎች ይዛቸው እንዳትሄድ አይከለክልም። እናትየው የማያምነው ባልዋ ልጆቻቸው በይሖዋ ድርጅት አማካኝነት የሚያገኙት ገንቢ ሥልጠና ያለውን ጠቀሜታ እንዲገነዘብ ልትረዳው ትችላለች። በሥነ ምግባር እያሽቆለቆለ በመሄድ ላይ በሚገኘው ዓለም ውስጥ ልጆቻቸው የመጽሐፍ ቅዱስን የሥነ ምግባር መሥፈርቶች መማራቸው የሚያስገኛቸውን ጥቅሞች በጥበብ ልትነግረው ትችላለች።

ያም ሆኖ የማያምነው ባል ልጆቹ የእሱን ሃይማኖት እንዲከተሉ በማሰብ ወደ ራሱ የአምልኮ ቦታ ሊወስዳቸው እንዲሁም ከራሱ እምነት ጋር የሚስማማ ሃይማኖታዊ ትምህርት ሊሰጣቸው ይፈልግ ይሆናል። ወይም ደግሞ ሁሉንም ዓይነት ሃይማኖት በመቃወም ልጆቹ ምንም ዓይነት ሃይማኖታዊ ትምህርት እንዳይሰጣቸው ሊከለክል ይችላል። የቤተሰቡ ራስ እንደመሆኑ መጠን ውሳኔ የማድረጉ ኃላፊነት በዋነኛነት የተጣለው በእሱ ላይ ነው። a

አማኝ የሆነችው ሚስት ራስዋን የወሰነች ክርስቲያን እንደመሆንዋ መጠን የባልዋን የራስነት ሥልጣን ብታከብርም ሐዋርያው ጴጥሮስና ሐዋርያው ዮሐንስ የነበራቸውን አመለካከት አትዘነጋም። “እኛስ ያየነውንና የሰማነውን ከመናገር ዝም ማለት አንችልም” ሲሉ ተናግረዋል። (ሥራ 4:​19, 20) የይሖዋ ምሥክር የሆነች እናት ለልጆቹ መንፈሳዊ ደህንነት ካላት አሳቢነት በመነሳት በተለያዩ አጋጣሚዎች ተጠቅማ ሥነ ምግባራዊ መመሪያ ትሰጣቸዋለች። ይሖዋ እውነት እንደሆነ የምታውቀውን ነገር ለሌሎች የማስተማር ኃላፊነት ጥሎባታል፤ ይህ ደግሞ ልጆችዋንም ይጨምራል። (ምሳሌ 1:8፤ ማቴዎስ 28:19, 20) የይሖዋ ምሥክር የሆነችው እናት ይህንን ችግር መፍታት የምትችለው እንዴት ነው?

በአምላክ ማመንን እንደ ምሳሌ እንውሰድ። የይሖዋ ምሥክር የሆነችው እናት ባልዋ ስለሚከለክላት ከልጆችዋ ጋር መደበኛ የሆነ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ማድረግ አትችል ይሆናል። ይህ ማለት ታዲያ ለልጆችዋ ስለ ይሖዋ ምንም አትነግራቸውም ማለት ነውን? በፍጹም አይደለም። የምትናገራቸው ቃላትና ተግባርዋ በፈጣሪ እንደምታምን ያሳያሉ። ልጆችዋም በዚህ ጉዳይ ላይ ጥያቄ ማንሳታቸው አይቀርም። ሃይማኖታዊ ነፃነትዋን በመጠቀም ለልጆችዋም ጭምር በፈጣሪ ላይ ያላትን እምነት መግለጽ ትችላለች። ከልጆቹ ጋር መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት ወይም አዘውትራ ወደ ስብሰባዎች ይዛቸው መሄድ ባትችልም ስለ ይሖዋ አምላክ እንዲያውቁ ልትረዳቸው ትችላለች።​—⁠ዘዳግም 6:7

ሐዋርያው ጳውሎስ የይሖዋ ምሥክር የሆኑ ወላጆች ከማያምን የትዳር ጓደኛቸው ጋር ስለሚኖራቸው ግንኙነት ሲጽፍ እንዲህ ብሏል:- “ያላመነ ባል በሚስቱ ተቀድሶአልና፣ ያላመነችም ሚስት በባልዋ ተቀድሳለች፤ አለዚያ ልጆቻችሁ ርኵሳን ናቸው፤ አሁን ግን የተቀደሱ ናቸው።” (1 ቆሮንቶስ 7:14) ይሖዋ አማኝ በሆነው የትዳር ጓደኛ ምክንያት ትዳሩን እንደ ቅዱስ አድርጎ ይመለከተዋል፤ ልጆቹም በይሖዋ ዓይን ቅዱሳን እንደሆኑ ተደርገው ይቆጠራሉ። ምሥክር የሆነችው ሚስት የመጨረሻ ውጤቱን ለይሖዋ በመተው ልጆችዋ እውነትን እንዲረዱ ለማድረግ የምትችለውን ሁሉ ልታደርግ ይገባል።

ልጆቹ እያደጉ ሲሄዱ ከወላጆቻቸው ባገኙት ትምህርት ላይ በመመሥረት ምን ዓይነት አቋም እንደሚወስዱ መወሰን ይኖርባቸዋል። ከሚከተሉት የኢየሱስ ቃላት ጋር የሚስማማ እርምጃ ይወስዱ ይሆናል:- “ከእኔ ይልቅ አባቱን ወይም እናቱን የሚወድ ለእኔ ሊሆን አይገባውም።” (ማቴዎስ 10:37) ከዚህም በላይ “ልጆች ሆይ፣ ለወላጆቻችሁ በጌታ ታዘዙ” ተብለው ታዝዘዋል። (ኤፌሶን 6:1) ብዙ ወጣቶች የማያምነው ወላጅ ብዙ ስደት ቢያደርስባቸውም ከእሱ ይልቅ ‘አምላክን ለመታዘዝ’ መርጠዋል። ተቃውሞ ቢኖርባቸውም ልጆቹ ይሖዋን ለማገልገል ሲመርጡ ማየት የይሖዋ ምሥክር ለሆነው ወላጅ ምንኛ የሚክስ ነው!

[የግርጌ ማስታወሻ]

a ሚስትየው የፈለገችውን ሃይማኖት ለመከተል ያላት ሕጋዊ መብት በክርስቲያናዊ ስብሰባዎች ላይ የመገኘት ነፃነትንም ይጨምራል። አንዳንድ ጊዜ ሚስት ወደ ስብሰባ ስትሄድ ባልየው ትናንሾቹን ልጆች ለመንከባከብ ፈቃደኛ ስለማይሆን አፍቃሪ የሆነችው እናት ልጆቹን ይዛ ወደ ስብሰባዎች ለመሄድ ትገደዳለች።