በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ለፈተናዎች ሊኖረን የሚገባው አመለካከት ምንድን ነው?

ለፈተናዎች ሊኖረን የሚገባው አመለካከት ምንድን ነው?

ለፈተናዎች ሊኖረን የሚገባው አመለካከት ምንድን ነው?

ሁሉም ሰው ፈተናዎች ያጋጥሙታል። የባሕርይ አለ​መጣጣም፣ የኢኮኖሚ ችግሮች፣ ጤና ማጣት፣ መጥፎ ነገር እንድናደርግ የሚገፋፋ የእኩዮች ተጽዕኖ፣ ስደት፣ በገለልተኝነት አቋማችን ወይም ከጣዖት አምልኮ በመራቃችን ምክንያት የሚደርስብን ተፈታታኝ ሁኔታ እና ሌሎች ብዙ ነገሮች ፈተና ሊሆኑብን ይችላሉ። የትኛውም ዓይነት ፈተና ቢሆን ብዙውን ጊዜ ጭንቀት መፍጠሩ አይቀርም። ፈተናዎችን በጽናት መቋቋም የምንችለው እንዴት ነው? ከፈተናዎች ጥቅም ማግኘት የምንችልበት መንገድ ይኖር ይሆን?

ከሁሉ የላቀ እርዳታ

በጥንት ዘመን የኖረው ንጉሥ ዳዊት ሕይወቱ በመከራ የተሞላ ነበር፤ ያም ሆኖ እስከ ዕለተ ሞቱ ድረስ ታማኝነቱን ጠብቋል። እንዲጸና የረዳው ምን ነበር? ዳዊት ኃይል ከየት እንዳገኘ ሲናገር “እግዚአብሔር እረኛዬ ነው፣ የሚያሳጣኝም የለም” ብሏል። አክሎም “በሞት ጥላ መካከል እንኳ ብሄድ አንተ ከእኔ ጋር ነህና ክፉን አልፈራም፤ በትርህና ምርኩዝህ እነርሱ ያጸናኑኛል” ሲል ተናግሯል። (መዝሙር 23:1, 4) አዎን፣ ይሖዋ ወደር የማይገኝለት ብርታት ምንጭ ነው። ዳዊትን በጣም አስጨናቂ በሆኑ ወቅቶች እንደ እረኛ ሆኖ መርቶታል፤ አስፈላጊ በሚሆንበት ጊዜ ለእኛም ተመሳሳይ ነገር ለማድረግ ዝግጁ ነው።

የይሖዋን እርዳታ ማግኘት የምንችለው እንዴት ነው? መጽሐፍ ቅዱስ “እግዚአብሔር ቸር እንደ ሆነ ቅመሱ እዩም” በማለት እርዳታ ማግኘት የምንችልበትን መንገድ ያመለክተናል። (መዝሙር 34:8) ይህ ፍቅራዊ ግብዣ ነው፤ ግን ምን ማለት ነው? ይሖዋን እንድናገለግልና ሕይወታችንን ሙሉ በሙሉ ከእሱ ፈቃድ ጋር አስማምተን እንድንኖር የቀረበ ማበረታቻ ነው። እንደዚህ ዓይነቱ ሕይወት መሥዋዕትነት መክፈል ይጠይቃል። በአንዳንድ ሁኔታዎች ሥር ደግሞ ስደትና መከራ ስለሚያስከትል ፈታኝ ሊሆን ይችላል። ያም ሆኖ የይሖዋን ግብዣ በሙሉ ልባቸው የሚቀበሉ ሰዎች እንደዚያ በማድረጋቸው ፈጽሞ አይቆጩም። ይሖዋ ይክሳቸዋል። መንፈሳዊ አመራሩንና እንክብካቤውን ያገኛሉ። ፈተናዎች ሲያጋጥሟቸው በቃሉ፣ በመንፈስ ቅዱሱና በክርስቲያን ጉባኤ አማካኝነት ይደግፋቸዋል። ውሎ አድሮ ደግሞ የዘላለም ሕይወት በመስጠት ይባርካቸዋል።​—⁠መዝሙር 23:6፤ 25:9፤ ኢሳይያስ 30:21፤ ሮሜ 15:5

ይሖዋን ለማገልገል በመወሰን ሕይወታቸውን ለመለወጥ ፈቃደኞች የሆኑና ከዚህ ውሳኔያቸው ጋር ተስማምተው የሚኖሩ ሰዎች ይሖዋ የገባውን ቃል ሙሉ በሙሉ እንደሚጠብቅ ተመልክተዋል። ኢያሱን ተከትለው ወደ ተስፋይቱ ምድር የገቡት እስራኤላውያንም ያጋጠማቸው ሁኔታ ይኸው ነበር። ዮርዳኖስን ከተሻገሩ በኋላ ጽናት የሚጠይቁ ፈተናዎች፣ ጦርነቶችና ትምህርት ሰጥተዋቸው ያለፉ ችግሮች አጋጥመዋቸዋል። ይሁን እንጂ ያ ትውልድ ከግብጽ ወጥተው በምድረ በዳ ከሞቱት አባቶቹ ይልቅ ታማኝ ሆኗል። ይሖዋም ታማኝ የሆኑትን ደግፏቸዋል። መጽሐፍ ቅዱስ እነዚህ ታማኝ እስራኤላውያን ኢያሱ ሊሞት በተቃረበበት ወቅት ስለ ነበሩበት ሁኔታ ሲናገር እንዲህ ይላል:- “እግዚአብሔርም ለአባቶቻቸው እንደ ማለላቸው በዙሪያቸው ካሉት አሳረፋቸው፤ . . . እግዚአብሔር ለእስራኤል ቤት ከተናገረው መልካም ነገር ሁሉ ተፈጸመ እንጂ ምንም አልቀረም።” (ኢያሱ 21:44, 45) እኛም ፈተና ሲያጋጥመንም ሆነ በሌላ በማንኛውም ጊዜ በይሖዋ ላይ ሙሉ በሙሉ ከተማመንን ተመሳሳይ በረከት እናገኛለን።

በይሖዋ ላይ ያለንን ትምክህት ምን ሊያዳክምብን ይችላል? ኢየሱስ “ለሁለት ጌቶች መገዛት የሚቻለው ማንም የለም፤ . . . ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አትችሉም” ሲል የተናገረው ቃል ትምክህታችንን ሊያዳክሙ ከሚችሉ ነገሮች አንዱ ምን እንደሆነ ይጠቁመናል። (ማቴዎስ 6:24) በይሖዋ የምንታመን ከሆነ በዓለም ላይ ያሉ አብዛኞቹ ሰዎች እንደሚያደርጉት በቁሳዊ ነገሮች ለመታመን አንሞክርም። ኢየሱስ ተከታዮቹን እንዲህ ሲል መክሯቸዋል:- “ነገር ግን አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፣ [አስፈላጊ የሆኑ ቁሳዊ ነገሮች] ሁሉ ይጨ[መሩ]ላችኋል።” (ማቴዎስ 6:33) ለቁሳዊ ነገሮች ሚዛናዊ አመለካከት ያለውና በሕይወቱ ውስጥ ለአምላክ መንግሥት አንደኛ ቦታ የሚሰጥ ክርስቲያን ትክክለኛ ምርጫ አድርጓል። (መክብብ 7:12) እርግጥ ነው፣ እንዲህ ማድረጉ በቁሳዊ መንገድ የተወሰነ መሥዋዕትነት መክፈል ይጠይቅበት ይሆናል። ሆኖም የተትረፈረፈ በረከት ያገኛል። ይሖዋም ይደግፈዋል።​—⁠ኢሳይያስ 48:17, 18

ከፈተናዎች ምን እንማራለን?

እርግጥ ነው፣ “እግዚአብሔር ቸር እንደ ሆነ ቅመሱ እዩም” የሚለውን ምክር ተግባራዊ ማድረጋችን በሕይወት ውስጥ ከሚያጋጥሙን ያልተጠበቁ ክስተቶችም ሆነ ሰይጣንና ሰብዓዊ ወኪሎቹ ከሚሰነዝሩብን ጥቃት ሙሉ በሙሉ አይከላከልልንም። (መክብብ 9:11) በመሆኑም የአንድ ክርስቲያን የልብ ዝንባሌና የአቋም ጽናት ሊፈተን ይችላል። ይሖዋ አገልጋዮቹ እንደዚህ ዓይነት ፈተናዎች እንዲያጋጥሟቸው የሚፈቅደው ለምንድን ነው? ሐዋርያው ጴጥሮስ እንደሚከተለው ብሎ ሲጽፍ አንዱን ምክንያት ገልጿል:- “በእሳት ምንም ቢፈተን ከሚጠፋው ወርቅ ይልቅ አብልጦ የሚከብር የተፈተነ እምነታችሁ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ሲገለጥ፣ ለምስጋናና ለክብር ለውዳሴም ይገኝ ዘንድ አሁን ለጥቂት ጊዜ ቢያስፈልግ በልዩ ልዩ ፈተና አዝናችኋል።” (1 ጴጥሮስ 1:6, 7) አዎን፣ ፈተናዎች የእምነታችንን ጥንካሬና ለይሖዋ ያለን ፍቅር ምን ያህል ጥልቅ እንደሆነ የምናሳይበትን አጋጣሚ ይፈጥሩልናል። እንዲሁም ሰይጣን ዲያብሎስ ለሚሰነዝረው ስድብና ወቀሳ መልስ ለመስጠት ያስችላሉ።​—⁠ምሳሌ 27:11፤ ራእይ 12:10

ፈተናዎች ሌሎች ክርስቲያናዊ ባህርያትን ለማዳበርም ይረዱናል። ለምሳሌ ያህል የሚከተሉትን የመዝሙራዊው ቃላት ተመልከት:- “እግዚአብሔር . . . ወደ ችግረኞችም [“ትሑታን፣”የ1980 ትርጉም ] ይመለከታልና፤ ትዕቢተኞችንም ከሩቅ ያውቃል።” (መዝሙር 138:6) አብዛኞቻችን በተፈጥሯችን ትሑቶች ባንሆንም ፈተናዎች ይህንን አስፈላጊ ባሕርይ እንድናዳብር ሊረዱን ይችላሉ። በሙሴ ዘመን አንዳንድ እስራኤላውያን ከሳምንት እስከ ሳምንትና ከወር እስከ ወር መና መብላት አሰልቺ ሆኖባቸው እንደነበረ አስታውስ። ምንም እንኳን መናው ተአምራዊ ዝግጅት ቢሆንም ለእነርሱ ፈተና ሆኖባቸው ነበር። የፈተናው ዓላማ ምን ነበር? ሙሴ እንዲህ ብሏቸዋል:- “[ይሖዋ] አንተን ትሑት ለማድረግና ለመፈተን . . . መና በምድረ በዳ መገበህ።”​—⁠ዘዳግም 8:16 አ.መ.ት 

በተመሳሳይ የእኛም ትሕትና ሊፈተን ይችላል። እንዴት? ለምሳሌ ያህል፣ ድርጅታዊ ማስተካከያዎች ሲደረጉ ምን ይሰማናል? (ኢሳይያስ 60:17) የስብከቱንና የማስተማሩን ሥራ በሙሉ ልባችን እንደግፋለን? (ማቴዎስ 24:14፤ 28:19, 20) በ“ታማኝና ልባም ባሪያ” አማካኝነት መጽሐፍ ቅዱሳዊ እውነቶች ሲብራሩ በጉጉት እንቀበላቸዋለን? (ማቴዎስ 24:45-47፤ ምሳሌ 4:18) ዘመናዊ ዕቃዎችን፣ አዲስ የመጣውን የልብስ ፋሽን ወይም አዲሱን የመኪና ሞዴል እንድንገዛ የሚቀርብልንን ፈተና እንቋቋማለን? ትሑት የሆነ ሰው ለእነዚህ ጥያቄዎች አዎንታዊ መልስ ይሰጣል።​—⁠1 ጴጥሮስ 1:14-16፤ 2 ጴጥሮስ 3:11

ፈተናዎች ሌላም አስፈላጊ ባሕርይ ማለትም ጽናትን እንድናዳብር ይረዱናል። ደቀ መዝሙሩ ያዕቆብ እንዲህ ብሏል:- “ወንድሞቼ ሆይ፣ የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን [“ጽናትን፣” NW ] እንዲያደርግላችሁ አውቃችሁ፣ ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ እንደ ሙሉ ደስታ ቊጠሩት።” (ያዕቆብ 1:2, 3) በይሖዋ ላይ ሙሉ በሙሉ በመታመን የተለያዩ ፈተናዎችን መቋቋማችን ጽናትና ታማኝነት እንድናዳብር ይረዳናል። እንዲሁም እጅግ የተቆጣው የዚህ ዓለም አምላክ ሰይጣን ወደፊት የሚ​ሰነዝርብንን ጥቃቶች ለመቋቋም እንድንችል ያጠነክረናል።​—⁠1 ጴጥሮስ 5:8-10፤ 1 ዮሐንስ 5:19፤ ራእይ 12:12

ለፈተናዎች ተገቢ አመለካከት ይኑራችሁ

ፍጹም የሆነው የአምላክ ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ምድር በነበረበት ወቅት ያጋጠሙትን የተለያዩ ፈተናዎች በጽናት መቋቋሙ ብዙ በረከቶች አስገኝቶለታል። ጳውሎስ ይህን አስመልክቶ ሲጽፍ ኢየሱስ “ከተቀበለው መከራ መታዘዝን ተማረ” ብሏል። (ዕብራውያን 5:8) እስከ ሞት ድረስ ታማኝ መሆኑ የይሖዋን ስም ከማስከበሩም በላይ ፍጹም ሰብዓዊ ሕይወቱን ለሰው ልጆች ቤዛዊ መሥዋዕት አድርጎ ለመስጠት አስችሎታል። ይህም በኢየሱስ የሚያምኑ ሁሉ የዘላለም ሕይወት የማግኘት ተስፋ እንዲኖራቸው መንገድ ከፍቷል። (ዮሐንስ 3:16) ኢየሱስ ፈተና ቢደርስበትም ታማኝነቱን ሳያላላ በመጽናቱ በአሁኑ ወቅት ሊቀ ካህናችንና የተሾመ ንጉሣችን ሊሆን በቅቷል።​—⁠ዕብራውያን 7:26-28፤ 12:2

እኛስ? እኛም ፈተናዎች ሲያጋጥሙን በታማኝነት ከጸናን የተትረፈረፉ በረከቶች እናገኛለን። መጽሐፍ ቅዱስ ሰማያዊ ተስፋ ስላላቸው ሰዎች ሲናገር እንዲህ ይላል:- “በፈተና የሚጸና ሰው የተባረከ ነው፤ ከተፈተነ በኋላ [ይሖዋ] ለሚወዱት ተስፋ ስለ እርሱ የሰጣቸውን የሕይወትን አክሊል ይቀበላልና።” (ያዕቆብ 1:12) ምድራዊ ተስፋ ያላቸውም በታማኝነት ከጸኑ ገነት በሆነች ምድር ላይ ዘላለማዊ ሕይወት ያገኛሉ። (ራእይ 21:3-6) ከሁሉ በላይ ደግሞ በታማኝነት መጽናታቸው የይሖዋን ስም ያስከብራል።

የኢየሱስን ፈለግ ስንከተል በዚህ ሥርዓት ውስጥ የሚያጋጥሙንን ፈተናዎች ሁሉ በተሳካ ሁኔታ ልንቋቋማቸው እንደምንችል እርግጠኞች መሆን እንችላለን። (1 ቆሮንቶስ 10:13፤ 1 ጴጥሮስ 2:21) እንዴት? በእሱ ለሚታመኑት “እጅግ ታላቅ ኃይል” በሚሰጠው በይሖዋ ላይ በመመካት ነው። (2 ቆሮንቶስ 4:7 አ.መ.ት ) እንግዲያው አስቸጋሪ ፈተናዎች እየደረሱበትም እንኳን “ከፈተነኝም በኋላ እንደ ወርቅ እወጣለሁ” ብሎ እንደተናገረው እንደ ኢዮብ ዓይነት ጽኑ እምነት ይኑረን።​—⁠ኢዮብ 23:10

[በገጽ 31 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ኢየሱስ ፈተና ቢደርስበትም በታማኝነት በመጽናቱ የይሖዋን ስም አስከብሯል፤ እኛም ከጸናን እንዲሁ እናደርጋለን