በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

“ሰብዓ ሰገል” እነማን ነበሩ?

“ሰብዓ ሰገል” እነማን ነበሩ?

“ሰብዓ ሰገል” እነማን ነበሩ?

የኢየሱስን ልደት ለማመልከት ተብለው በሚዘጋጁ ስዕሎች ላይ ባብዛኛው ካባ የለበሱ ሦስት ሰዎች በግመሎቻቸው ላይ ተቀምጠው ሕፃኑ ኢየሱስ በግርግም ውስጥ ወደ ተኛበት ጋጣ ሲመጡ ይታያል። ግሩም አለባበስ ያላቸው እነዚህ ጎብኚዎች “ሰብዓ ሰገል” ወይም በተለምዶ ሦስቱ ጠቢባን ተብለው ይጠራሉ። መጽሐፍ ቅዱስ ስለ እነዚህ ሰዎች ምን ይላል?

መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው ጠቢባን ተብለው የሚጠሩት እነዚህ ሰዎች የመጡት “ከምሥራቅ” ሲሆን ስለ ኢየሱስ መወለድ ያወቁትም እዚያው እያሉ ነበር። (ማቴዎስ 2:1, 2, 9) በመሆኑም እነዚህ ሰዎች ይሁዳ ለመድረስ ረዘም ያለ ጊዜ ወስዶባቸው መሆን አለበት። ኢየሱስን ያገኙት ገና አራስ ልጅ ሆኖ በከብቶች ጋጣ ውስጥ እንደተኛ አልነበረም። ከዚህ ይልቅ ሰዎቹ ማርያምንና “ሕፃኑን [“ትንሹን ልጅ፣ NW ]” ያገኟቸው በቤት ውስጥ ነበር።​—⁠ማቴዎስ 2:11

መጽሐፍ ቅዱስ እነዚህን ሰዎች “ሰብአ ሰገል” ወይም ኮከብ ቆጣሪዎች በማለት የሚጠራቸው ሲሆን ቁጥራቸው ምን ያህል እንደሆነ ምንም የሚገልጸው ነገር የለም። ዚ ኦክስፎርድ ኮምፓንየን ቱ ዘ ባይብል “ጎብኚዎቹ ወደ ቤተ ልሔም የመጡት በኮኮብ ተመርተው መሆኑ አስማትና ኮኮብ ቆጠራ ዝምድና ያላቸው ነገሮች መሆናቸውን ያሳያል” ብሏል። መጽሐፍ ቅዱስ ማንኛውንም ዓይነት የአስማት ድርጊቶችና በባቢሎናውያን ዘንድ የተለመደ የነበረውን ከከዋክብት መረጃ ለማግኘት የሚደረግ ጥረት በግልጽ ያወግዛል።​—⁠ዘዳግም 18:10-12፤ ኢሳይያስ 47:13

እነዚህ ሰዎች ያገኙት መረጃ ምንም መልካም ነገር አላስገኘም። እንዲያውም ክፉ የነበረው ንጉሥ ሄሮድስ በቅንዓት እንዲነሳሳ አድርጎታል። ይህ ደግሞ ዮሴፍ፣ ማርያምና ኢየሱስ ወደ ግብጽ እንዲሸሹ ከማድረጉም በላይ በቤተ ልሔም የነበሩ ‘ሁለት ዓመት የሆናቸውና ከዚያም የሚያንሱት’ ሕፃናት በሙሉ እንዲገደሉ ምክንያት ሆኗል። ሄሮድስ ከኮኮብ ቆጣሪዎቹ ያገኘውን መረጃ መሠረት በማድረግ ኢየሱስ የተወለደበትን ጊዜ በጥንቃቄ አስልቶ ነበር። (ማቴዎስ 2:16) እነዚህ ኮኮብ ቆጣሪዎች ያደረጉት ጉብኝት ካስከተለው መዘዝ አንጻር የተመለከቱት ኮኮብና ስለ “ተወለደው የአይሁድ ንጉሥ” ያገኙት መረጃ የአምላክ ጠላት ከሆነውና ኢየሱስ እንዲሞት ይፈልግ ከነበረው ከሰይጣን ዲያብሎስ የመጣ ነው ብሎ መደምደሙ ምክንያታዊ ይሆናል።​—⁠ማቴዎስ 2:1, 2