በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

በማናውቀው አምላክ ማመን

በማናውቀው አምላክ ማመን

በማናውቀው አምላክ ማመን

ከሦስት ጀርመናውያን መካከል ሁለቱ በአምላክ ያምናሉ። ሆኖም ከአንድ ሺህ የሚበልጡት ስለሚያምኑበት አምላክ እንዲገልጹ ሲጠየቁ ሁሉም ማለት ይቻላል የሰጡት መልስ የተለያየ ነበር። ፎከስ የተሰኘው ጋዜጣ “ጀርመናውያን ስለ አምላክ ያላቸው አመለካከት እንደመልካቸው የተለያየ ነው” ብሏል። በአምላክ ማመን ጥሩ ነገር ቢሆንም የምናምንበትን አምላክ ማንነት አለማወቃችን የሚያሳዝን አይሆንም?

ስለ አምላክ ማንነት በቂ እውቀት የሌላቸው ጀርመናውያን ብቻ አይደሉም፤ በሌሎች የአውሮፓ አገሮችም ተመሳሳይ አመለካከት ተስፋፍቶ ይገኛል። በኦስትሪያ፣ በብሪታንያና በኔዘርላንድ የተደረገ አንድ ጥናት እንዳመለከተው በብዙዎች ዘንድ አምላክ “ታላቅ ኃይል ወይም ሊገለጽ የማይቻል ምስጢር” እንደሆነ ተደርጎ ይታሰባል። በተለይ ወጣቶች (በአምላክ የሚያምኑትም ጭምር) አምላክ ከሰው ልጅ የመረዳት ችሎታ በላይ እንደሆነ ይሰማቸዋል።

አምላክን በደንብ ታውቀዋለህን?

አንድን ሰው እንዲሁ በሩቅ በማወቅና ያንኑ ሰው በቅርብ በማወቅ መካከል ሰፊ ልዩነት አለ። አንድን ሰው በሩቅ ብቻ ማወቅ የሰውየውን ሕልውና ከመገንዘብ አልፎ አይሄድም። ለምሳሌ ያህል ስለ አንድ ንጉሠ ነገሥት፣ ታዋቂ አትሌት ወይም የፊልም ተዋናይ የተወሰነ እውቀት ይኖረን ይሆናል። አንድን ሰው በቅርበት ማወቅ ግን ከዚህ የበለጠ ነገር ማለትም የዚያን ሰው ባህርይ፣ ምግባር፣ ስሜት፣ የሚወዳቸውንና የሚጠላቸውን ነገሮች እንዲሁም ለወደፊቱ ጊዜ ያለውን እቅድ ማወቅን ይጨምራል። አንድን ሰው በቅርበት ማወቅ ከዚያ ሰው ጋር የጠበቀ ወዳጅነት ለመመሥረት መንገድ ይከፍታል።

ሌሎች በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች ስለ አምላክ ውስን የሆነ እውቀት መያዝ ወይም አምላክ መኖሩን ማወቅ ብቻ በቂ እንዳልሆነ ተገንዝበዋል። ይልቁንም አምላክን በቅርበት ለማወቅ ከዚያ ያለፈ እርምጃ ወስደዋል። ጥረታቸው ዋጋ አስገኝቶላቸው ይሆን? በአምላክ መኖር ብቻ ያምን የነበረ በሰሜን ጀርመን የሚኖር ፖል የተባለ አንድ ሰው ስለ አምላክ የበለጠ ለማወቅ ይወስናል። ፖል እንዲህ ይላል:- “አምላክን በቅርበት ለማወቅ ጊዜና ጥረት ይጠይቃል፤ ሆኖም እንደዚህ ማድረጋችን የሚያስገኘው ጥቅም ከፍተኛ ነው። ከአምላክ ጋር የቀረበ ዝምድና መመሥረት የዕለት ተዕለት ሕይወታችን የተሻለ እንዲሆን ያደርግልናል።”

አምላክን በቅርበት ለማወቅ ጊዜ መመደብና ጥረት ማድረግ አስፈላጊ ነውን? እባክህ የሚቀጥለውን ርዕስ አንብብ።

[በገጽ 3 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

አንድን ሰው እንዲሁ በሩቅ በማወቅና ያንኑ ሰው በቅርብ በማወቅ መካከል ሰፊ ልዩነት አለ