በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የተግሣጽን ዓላማ መረዳት

የተግሣጽን ዓላማ መረዳት

የተግሣጽን ዓላማ መረዳት

“ተግሣጽ” የሚለውን ቃል ስትሰማ ወደ አእምሮህ የሚመጣው ምንድን ነው? አንድ መዝገበ ቃላት ተግሣጽ ለሚለው ቃል “ሰዎች የሥነ ምግባር ደንቦችንና መመሪያዎችን እንዲታዘዙ ማድረግ፣ እንቢ ሲሉ ደግሞ መቅጣት” የሚል ፍቺ ሰጥቶታል። ምንም እንኳ ለተግሣጽ የሚሰጠው ፍቺ ይህ ብቻ ባይሆንም በዛሬው ጊዜ ብዙ ሰዎች ለማንኛውም ዓይነት ተግሣጽ ተመሳሳይ የሆነ አሉታዊ አመለካከት አላቸው።

መጽሐፍ ቅዱስ ግን ተግሣጽን የሚገልጸው ለየት ባለ መንገድ ነው። ጠቢቡ ንጉሥ ሰሎሞን “ልጄ ሆይ፣ የእግዚአብሔርን ተግሣጽ አትናቅ” ሲል ጽፏል። (ምሳሌ 3:11) ይህ ጥቅስ የሚናገረው በደፈናው ስለ ማንኛውም ተግሣጽ ሳይሆን አምላክ ባወጣቸው የላቁ መሠረታዊ ሥርዓቶች ላይ ስለተመሠረተው ‘የይሖዋ ተግሣጽ’ ነው። መንፈሳዊ ጥቅሞች የሚያስገኘውና ተቀባይነትም የሚኖረው እንዲህ ያለው ተግሣጽ ብቻ ነው። ከዚህ በተቃራኒው ከፍ ካሉት የይሖዋ መሥፈርቶች ጋር በሚቃረን ሰብዓዊ አስተሳሰብ ላይ የተመሠረተ ተግሣጽ መጥፎና ጎጂ ነው። ከዚህም የተነሳ ብዙዎች ለተግሣጽ አሉታዊ አመለካከት ይይዛሉ።

የይሖዋን ተግሣጽ እንድንቀበል ማሳሰቢያ የሚሰጠን ለምንድን ነው? መለኮታዊ ተግሣጽ አምላክ ለሰብዓዊ ፍጡሮቹ ያለው ፍቅር መግለጫ እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል። በዚህም ምክንያት ሰሎሞን በመቀጠል እንዲህ ብሏል:- “እግዚአብሔር የወደደውን ይገሥጻልና፣ አባት የሚወድደውን ልጁን እንደሚገሥጽ።”​—⁠ምሳሌ 3:12

የተግሣጽና የቅጣት ልዩነት ምንድን ነው?

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በተገለጸው መሠረት ተግሣጽ የተለያዩ ገጽታዎች ያሉት ሲሆን በመመሪያ፣ በትምህርት፣ በሥልጠና፣ በወቀሳና በእርማት አልፎ ተርፎም በቅጣት መልክ ሊሰጥ ይችላል። ይሁን እንጂ በየትኛውም መልክ ቢሆን ይሖዋ ተግሣጽ የሚሠጠው በፍቅር ተገፋፍቶ ሲሆን ዓላማውም ግለሰቡን መጥቀም ነው። ይሖዋ ለማረም ብሎ ተግሣጽ የሚሰጠው ግለሰቡን ለመቅጣት ሲፈልግ ብቻ አይደለም።

በሌላ በኩል ደግሞ አምላክ የቅጣት እርምጃ የሚወስደው ግለሰቡን ለማረም ወይም ለማስተማር ብቻ ብሎ አይደለም። ለምሳሌ አዳምና ሔዋን ኃጢአት ከሠሩበት ዕለት ጀምሮ አለመታዘዛቸው የሚያስከትለውን መዘዝ ለመቀበል ተገድደዋል። ይሖዋ ከኤደን ገነት ያባረራቸው ሲሆን አለፍጽምና፣ በሽታ እንዲሁም እርጅና የሚያስከትሉት ሥቃይ ደርሶባቸዋል። ለበርካታ መቶ ዓመታት ፍዳቸውን ካዩ በኋላ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከሕልውና ውጪ ሆነዋል። ይህ መለኮታዊ ቅጣት እንጂ እነርሱን ለማረም ተብሎ የተሰጠ ተግሣጽ አይደለም። አዳምና ሔዋን ኃጢአት የሠሩት ሆን ብለው ስለሆነና ንስሐ ስላልገቡ መታረም የሚችሉ አልነበሩም።

ይሖዋ የቅጣት እርምጃ እንደወሰደ ከሚገልጹት ሌሎች ዘገባዎች መካከል በኖህ ዘመን የደረሰው የጥፋት ውኃ፣ የሰዶምና የገሞራ መደምሰስ እንዲሁም የግብጽ ሠራዊት በቀይ ባሕር መጥፋት ይገኙበታል። ይሖዋ እነዚህን እርምጃዎች የወሰደው ለሰዎቹ መመሪያ፣ ትምህርት ወይም ሥልጠና ለመስጠት አልነበረም። አምላክ የወሰዳቸውን እነዚህን የቅጣት እርምጃዎች በተመለከተ ሐዋርያው ጴጥሮስ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “ለቀደመውም ዓለም ሳይራራ ከሌሎች ሰባት ጋር ጽድቅን የሚሰብከውን ኖኅን አድኖ በኃጢአተኞች ዓለም ላይ የጥፋትን ውኃ [አውርዶባቸዋል]፣ ኃጢአትንም ያደርጉ ዘንድ ላሉት ምሳሌ አድርጎ ከተማዎችን ሰዶምንና ገሞራን አመድ እስኪሆኑ ድረስ አቃጥሎና ገልብጦ [ፈርዶባቸዋል]።”​—⁠2 ጴጥሮስ 2:5, 6

እነዚህ የቅጣት እርምጃዎች “ኃጢአትንም ያደርጉ ዘንድ ላሉት ምሳሌ” የሆኑት እንዴት ነው? ጳውሎስ ለተሰሎንቄ ሰዎች በጻፈው ደብዳቤ ላይ አምላክ በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ አማካኝነት “እግዚአብሔርን የማያውቁትን፣ ለጌታችንም ለኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል የማይታዘዙትን ይበቀላል” በማለት በእኛ ዘመን የቅጣት እርምጃ እንደሚወስድ ተናግሯል። አክሎም “በዘላለም ጥፋት ይቀጣሉ” ብሏል። (2 ተሰሎንቄ 1:8, 9) በግልጽ ለመረዳት እንደሚቻለው እንዲህ ያለው ቅጣት ዓላማ ሰዎቹን ማስተማር ወይም ማስተካከል አይደለም። ይሁን እንጂ ይሖዋ አምላኪዎቹ ተግሣጹን እንዲቀበሉ ሲናገር ንስሐ በማይገቡ ኃጢአተኞች ላይ የሚወስደውን ቅጣት ማመልከቱ አይደለም።

መጽሐፍ ቅዱስ ይሖዋን በዋነኝነት የሚገልጸው ለመቅጣት እንደተዘጋጀ አድርጎ አለመሆኑ ትልቅ ትርጉም ያዘለ ነው። ከዚህ ይልቅ አብዛኛውን ጊዜ የተገለጸው አፍቃሪ አስተማሪና ታጋሽ አሰልጣኝ እንደሆነ ነው። (ኢዮብ 36:22፤ መዝሙር 71:17፤ ኢሳይያስ 54:13) አዎን፣ አንድን ሰው ለማስተካከል ተብሎ የሚሰጥ መለኮታዊ ተግሣጽ ምንጊዜም በፍቅርና በትዕግሥት የተደገፈ ነው። ክርስቲያኖች የተግሣጽን ዓላማ መረዳታቸው ተግሣጽ በመቀበልም ሆነ በመስጠት ረገድ ተገቢ አመለካከት እንዲኖራቸው ይረዳቸዋል።

አፍቃሪ ወላጆች የሚሰጡት ተግሣጽ

በቤተሰብ ክልል ውስጥም ሆነ በክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ የሚገኝ ማንኛውም ሰው ተግሣጽ የሚሰጥበትን ዓላማ መረዳት ያስፈልገዋል። ይህ በተለይ በኃላፊነት ቦታ ላይ ያሉትን ይመለከታል። ለምሳሌ ያህል ወላጆች እንዲህ ዓይነት ኃላፊነት አላቸው። ምሳሌ 13:24 እንዲህ ይላል:- “በበትር ከመምታት የሚራራ ሰው ልጁን ይጠላል፤ ልጁን የሚወድድ ግን ተግቶ ይገሥጸዋል።”

ወላጆች ተግሣጽ መስጠት ያለባቸው እንዴት ነው? መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል:- “እናንተም አባቶች ሆይ፣ ልጆቻችሁን በጌታ ምክርና በተግሣጽ አሳድጉአቸው እንጂ አታስቈጡአቸው።” (ኤፌሶን 6:4) ይኸው ምክር በሚከተለው ጥቅስ ላይም በድጋሚ ተገልጿል:- “አባቶች ሆይ፣ ልባቸው እንዳይዝል ልጆቻችሁን አታበሳጩአቸው።”​—⁠ቆላስይስ 3:21

የተግሣጽን ዓላማ የተገነዘቡ ክርስቲያን ወላጆች በጣም ጥብቅ አይሆኑም። በ2 ጢሞቴዎስ 2:​24 ላይ ያለው መሠረታዊ ሥርዓት ወላጆች ተግሣጽ የሚሰጡበትን መንገድ በተመለከተም ሊሠራ ይችላል። ጳውሎስ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “የጌታም ባሪያ ለሰው ሁሉ ገር ለማስተማርም የሚበቃ . . . ሊሆን እንጂ ሊጣላ አይገባውም።” በቁጣ መገንፈል፣ በልጆች ላይ መጮኽ እንዲሁም መሳደብ ወይም ማንቋሸሽ ፍቅራዊ የሆነ ተግሣጽ ካለመሆኑም በላይ በአንድ ክርስቲያን ሕይወት ውስጥ ቦታ የለውም።​—⁠ኤፌሶን 4:31፤ ቆላስይስ 3:8

ወላጆች የሚሰጡት እርማት ልጁ እንዳጠፋ ጠበቅ ያለ ቅጣት በመስጠት ብቻ አያበቃም። አብዛኞቹ ልጆች አመለካከታቸውን እንዲያስተካክሉ ተደጋጋሚ ምክር ያስፈልጋቸዋል። ለዚህም ወላጆች ጊዜ መስጠት፣ ትዕግሥት ማሳየትና ተግሣጽ ስለሚሰጡበት መንገድ በጥሞና ማሰብ ያስፈልጋቸዋል። ልጆቻቸውን “በጌታ ምክርና በተግሣጽ” ማሳደግ እንዳለባቸው መዘንጋት አይኖርባቸውም። ይህም ለዓመታት የሚዘልቅ ሥልጠና መስጠት አለባቸው ማለት ነው።

ክርስቲያን እረኞች በየዋህነት ገሥጹ

እነዚህ መሠረታዊ ሥርዓቶች ለክርስቲያን ሽማግሌዎችም ይሠራሉ። አፍቃሪ እረኞች እንደመሆናቸው መጠን ትምህርት፣ መመሪያና አስፈላጊ ሲሆንም ወቀሳ በመስጠት መንጋውን ለመገንባት ይጥራሉ። እንደዚህ በሚያደርጉበት ጊዜ የተግሣጽን ዋነኛ ዓላማ በአእምሯቸው ይይዛሉ። (ኤፌሶን 4:11, 12) ትኩረታቸው ያረፈው ቅጣት በመስጠት ላይ ብቻ ከሆነ በደለኛውን ከቀጡ በኋላ ምንም እርዳታ ሳይሰጡት ሊቀሩ ይችላሉ። መለኮታዊ ተግሣጽ ግን ከዚህ የበለጠ ነገር ይጨምራል። ሽማግሌዎች በፍቅር ተነሳስተው በደለኛውን ተከታትለው ለመርዳት የሚያደርጉትን ጥረት ይቀጥሉበታል። ለግለሰቡ ከልብ ስለሚያስቡለት እርሱን ለማበረታታትና ለማሰልጠን ፕሮግራም ይዘው በተደጋጋሚ ሊጠይቁት ይችላሉ።

በ2 ጢሞቴዎስ 2:​25, 26 ላይ በሚገኘው ምክር መሠረት ሽማግሌዎች በቀላሉ ተግሣጽ የማይቀበሉ ሰዎችን በሚያነጋግሩበት ጊዜም “በየዋህነት” ማስተማር አለባቸው። ጥቅሱ የተግሣጽን ዓላማ ሲገልጽ “ምናልባት እግዚአብሔር እውነትን ያውቁ ዘንድ ንስሐን ይሰጣቸዋልና . . . በዲያብሎስ ሕያዋን ሆነው ከተያዙበት ወጥመድ ወጥተው፣ ወደ አእምሮ ይመለሳሉ” ይላል።

ንስሐ የማይገቡ ኃጢአተኞችን ከጉባኤ ማስወገድ አስፈላጊ የሚሆንበት ጊዜ አለ። (1 ጢሞቴዎስ 1:18-20) እንደዚህ ያለው ከባድ እርምጃም ቢሆን እንደ ተግሣጽ እንጂ ቅጣት ብቻ ተደርጎ መታየት የለበትም። አልፎ አልፎ፣ ሽማግሌዎች ኃጢአት መሥራታቸውን ያቆሙ የተወገዱ ግለሰቦችን ለማነጋገር ጥረት ያደርጋሉ። በዚህ ወቅት ሽማግሌዎች አንድ ሰው ወደ ክርስቲያን ጉባኤ ለመመለስ ሊወስዳቸው የሚገቡትን እርምጃዎች በመንገር ተግሣጽ ከሚሰጥበት ትክክለኛ ዓላማ ጋር የሚስማማ ነገር ያደርጋሉ።

ይሖዋ ፍጹም ፈራጅ ነው

ተግሣጽ የመስጠት ቅዱስ ጽሑፋዊ ሥልጣን ያላቸው ወላጆች፣ ክርስቲያን እረኞችና ሌሎችም ይህንን ኃላፊነት በቁም ነገር ሊያዩት ይገባል። ተግሣጽ የሚሰጣቸው ግለሰቦች ፈጽሞ ሊስተካከሉ አይችሉም ብለው መፍረድ አይኖርባቸውም። በዚህም ምክንያት ተግሣጽ የሚሰጡት በብቀላ ወይም በጥላቻ መንፈስ መሆን የለበትም።

እርግጥ ነው፣ ይሖዋ ከባድና የማያዳግም የቅጣት እርምጃ እንደሚወስድ መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል። እንዲያውም መጽሐፍ ቅዱስ “በሕያው እግዚአብሔር እጅ መውደቅ የሚያስፈራ ነው” ይላል። (ዕብራውያን 10:31) ሆኖም ማንም ሰው በዚህም ሆነ በሌላ በማንኛውም መልኩ ራሱን ከይሖዋ ጋር ለማወዳደር ፈጽሞ መሞከር አይኖርበትም። እንዲሁም ማንም ሰው በወላጆቹ ወይም በአንድ የጉባኤ ሽማግሌ እጅ መውደቅ የሚያስፈራ ነው ብሎ እንዲያስብ የሚያደርገው ምክንያት መኖር የለበትም።

ይሖዋ ተግሣጽ በሚሰጥበት ጊዜ ፍጹም ሚዛናዊ የሆነ እርምጃ መውሰድ ይችላል። ሰዎች ግን እንዲህ ዓይነት ችሎታ የላቸውም። አምላክ የአንድን ሰው ልብ ማንበብና ግለሰቡ የማይታረም በመሆኑ ወሳኝና የማያዳግም ቅጣት የሚገባው መሆን አለመሆኑን ማወቅ ይችላል። በአንጻሩ ግን ሰዎች እንዲህ ዓይነት ፍርድ የመስጠት ችሎታ የላቸውም። ከዚህም የተነሳ የኃላፊነት ቦታ ያላቸው ሰዎች ተግሣጽ በሚሰጡበት ጊዜ ዓላማቸው ምንጊዜም ግለሰቡን ለማስተካከል መሆን አለበት።

የይሖዋን ተግሣጽ መቀበል

ሁላችንም የይሖዋ ተግሣጽ ያስፈልገናል። (ምሳሌ 8:33 NW ) እንዲያውም በአምላክ ቃል ላይ የተመሠረተ ተግሣጽ ለማግኘት ጉጉት ሊኖረን ይገባል። የአምላክን ቃል ስናጠና በቃሉ አማካኝነት በቀጥታ ከይሖዋ የሚመጣውን ተግሣጽ መቀበል እንችላለን። (2 ጢሞቴዎስ 3:16, 17) አንዳንድ ጊዜ ግን ክርስቲያን ባልንጀሮቻችንም ተግሣጽ ሊሰጡን ይችላሉ። እንደዚህ ያለው ተግሣጽ የተሰጠበትን ዓላማ መገንዘባችን ተግሣጹን ያለማንገራገር እንድንቀበል ያስችለናል።

ሐዋርያው ጳውሎስ “ቅጣት ሁሉ ለጊዜው የሚያሳዝን እንጂ ደስ የሚያሰኝ አይመስልም” በማለት ሳይሸሽግ ተናግሯል። አክሎም “ዳሩ ግን በኋላ ለለመዱት የሰላምን ፍሬ እርሱም ጽድቅን ያፈራላቸዋል” ብሏል። (ዕብራውያን 12:11) ይሖዋ ተግሣጽ የሚሰጠን ለእኛ ጥልቅ ፍቅር ስላለው ነው። ተግሣጽ ሲሰጠንም ሆነ ሌሎችን ስንገሥጽ የመለኮታዊ ተግሣጽን ዓላማ አንዘንጋ፤ እንዲሁም “ተግሣጽን ያዝ፣ አትተውም፤ ጠብቀው፣ እርሱ ሕይወትህ ነውና” የሚለውን ጥበብ ያዘለ የመጽሐፍ ቅዱስ ምክር እንከተል።​—⁠ምሳሌ 4:13

[በገጽ 21 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

አምላክ ንስሐ የማይገቡ ኃጢአተኞችን የቅጣት ፍርድ ይበይንባቸዋል እንጂ እንዲታረሙ ተግሣጽ አይሰጣቸውም

[በገጽ 22 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ሽማግሌዎች በፍቅር በመነሳሳት ምርምር ለማድረግና የተሳሳቱ ሰዎችን ለመርዳት ጊዜያቸውን ይሠዋሉ

[በገጽ 23 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ወላጆች ‘የይሖዋን ምክርና ተግሣጽ’ በትዕግሥትና በፍቅር ይሰጣሉ