በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

“በማይመች አካሄድ አትጠመዱ”

“በማይመች አካሄድ አትጠመዱ”

“በማይመች አካሄድ አትጠመዱ”

ከሥዕሉ ማየት እንደምትችለው በማረስ ላይ ያሉት ግመልና በሬ በጣም የተጎሳቆሉ ይመስላል። ተመሳሳይ መጠንና ጉልበት ያላቸውን እንስሳት አንድ ላይ ለማጥመድ ታስቦ የተሠራው ቀንበር ሁለቱንም እንስሳት ለሥቃይ ዳርጓቸዋል። አምላክ እነዚህን የመሳሰሉ የቤት እንስሳትን ደህንነት በሚመለከት ለእስራኤላውያን “በበሬና በአህያ በአንድነት አትረስ” ብሏቸው ነበር። (ዘዳግም 22:10) ይህ መመሪያ ለበሬና ለግመልም ይሠራል።

አንድ ገበሬ ብዙውን ጊዜ ከብቶቹን እንዲህ ላለ ሥቃይ ሊዳርጋቸው አይፈልግም። ሆኖም ሁለት በሬዎች ከሌሉት ያሉትን ሁለት እንስሳት በአንድነት ይጠምዳቸው ይሆናል። በሥዕሉ ላይ የሚታየው የ19ኛው መቶ ዘመን ገበሬ እንዲህ ለማድረግ የተገደደው በዚህ ምክንያት ሳይሆን አይቀርም። ሁለቱ እንስሳት መጠናቸውና ክብደታቸው ስለሚለያይ ደካማው እኩል ለመጎተት መጣጣር ሲያስፈልገው ብርቱው ደግሞ ጫናው ይበዛበታል።

ሐዋርያው ጳውሎስ እኛን ጠቃሚ ትምህርት ለማስተማር እንዲህ ዓይነቱን ተገቢ ያልሆነ ጥምረት ምሳሌ አድርጎ በመጠቀም እንዲህ ሲል ጽፏል:- “ከማያምኑ ጋር በማይመች አካሄድ አትጠመዱ፤ ጽድቅ ከዓመፅ ጋር ምን ተካፋይነት አለውና? ብርሃንም ከጨለማ ጋር ምን ኅብረት አለው?” (2 ቆሮንቶስ 6:14) አንድ ክርስቲያን በማይመች አካሄድ ሊጠመድ የሚችለው እንዴት ነው?

አንደኛው መንገድ አንድ ክርስቲያን ከእምነቱ ውጪ የትዳር ጓደኛ የሚመርጥ ከሆነ ነው። እንዲህ ባለው ጥምረት ባልና ሚስቱ መሠረታዊ በሆኑ ጉዳዮች ላይ ስለሚጋጩ ለሁለቱም የሚመች አይሆንም።

ይሖዋ ጋብቻን ሲያቋቁም ሚስት ለባሏ “ረዳት” ወይም ማሟያ እንደምትሆን ተናግሯል። (ዘፍጥረት 2:18) በተመሳሳይም አምላክ በነቢዩ ሚልክያስ አማካኝነት ሚስት ‘አጋር’ እንደሆነች ገልጿል። (ሚልክያስ 2:14 አ.መ.ት) ፈጣሪያችን ይሖዋ ባልና ሚስት በመንፈሳዊ ጉዳዮች ረገድ እጅና ጓንት ሆነው በመሥራት ሸክሙን እንዲጋሩና ከበረከቱ እኩል እንዲቋደሱ ይፈልጋል።

አንድ ክርስቲያን “በጌታ” ብቻ በማግባት በሰማይ የሚኖረው አባታችን ለሰጠው ምክር አክብሮት እንዳለው ማሳየት ይችላል። (1 ቆሮንቶስ 7:39) ይህም አንድነት ላለው ትዳር ጠንካራ መሠረት ይሆናል። እንዲህ ያለው ትዳር ደግሞ ባልና ሚስት በተገቢው ሁኔታ ‘ተጣምደው’ አምላክን እንዲያገለግሉት ስለሚያስችል ክብርና ውዳሴ ያመጣለታል።—ፊልጵስዩስ 4:3

[በገጽ 32 ላይ የሚገኝ የሥዕል ምንጭ]

ግመልና በሬ:- From the book La Tierra Santa, Volume 1, 1830