በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ንጹሕ ሕሊና

ንጹሕ ሕሊና

ንጹሕ ሕሊና

ኬንያ ውስጥ በአንድ ዩኒቨርሲቲ የሚሠራው ቻርለዝ አንድ ቀን ከሥራ ወደ ቤቱ ሲሄድ ሞባይል ስልኩ ጠፋበት። በኬንያ ሞባይል ስልክ ውድ የቅንጦት ዕቃ ተደርጎ ይታያል።

ቻርለዝ “ያገኘው ሰው ይመልስልኛል የሚል ተስፋ አልነበረኝም” ብሏል። ይሁን እንጂ ከጥቂት ቀናት በኋላ ኬንያ ከሚገኘው የይሖዋ ምሥክሮች ቅርንጫፍ ቢሮ ስልክ ሲደወልለት በጣም ተገረመ። ወደ ቅርንጫፍ ቢሮው መጥቶ ሞባይል ስልኩን እንዲወስድ ሲነገረው ጆሮውን ማመን አቃተው! የሙሉ ጊዜ አገልጋይ የሆነ አንድ የይሖዋ ምሥክር መኪና ውስጥ አብሮት ይጓዝ እንደነበረና ስልኩን ያገኘው እርሱ እንደሆነ ነገሩት። የይሖዋ ምሥክሩ ባለቤቱ እንዲታወቅ ስልኩን ወደ ቅርንጫፍ ቢሮው ይዞ የመጣ ሲሆን በዚያ የሚያገለግሉ ፈቃደኛ ሠራተኞች የሞባይሉን ቁጥር በማግኘት በመጨረሻ ቻርለዝን መጥራት ቻሉ።

ቻርለዝ ለቅርንጫፍ ቢሮው እንዲህ ሲል ደብዳቤ ጻፈ:- “አስቸጋሪ ቢሆንባችሁም እኔን ለማግኘት ያደረጋችሁትን ጥረት በጣም አደንቃለሁ። ስልኩን ያገኘውን እንዲሁም የእኔ መሆኑን አውቀው የመለሱልኝን የድርጅታችሁን አባላት ከልብ አመሰግናቸዋለሁ። በዛሬው ጊዜ ሐቀኛ ሰው ማግኘት በጣም አስቸጋሪ ነው። ሆኖም ይሖዋ አምላክን በትክክል የሚወክሉ ጥቂት የእርሱ ምሥክሮች በመካከላችን የሚገኙ መሆናቸው በጣም ያስደስታል።”

በምድር ዙሪያ ያሉ የይሖዋ ምሥክሮች በሐቀኝነታቸው ይታወቃሉ። “በነገር ሁሉ በመልካም እንድንኖር ወደን፣ መልካም ሕሊና እንዳለን ተረድተናልና” ብሎ የተናገረው የሐዋርያው ጳውሎስ ዓይነት አቋም አላቸው። (ዕብራውያን 13:18፤ 1 ቆሮንቶስ 11:1) ኢየሱስ “መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ” ብሎ እንደተናገረው መልካም ባሕርያቸው ለይሖዋ አምላክ ክብር እንደሚያመጣ ይገነዘባሉ።—ማቴዎስ 5:16