በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ገለልተኝነት ክርስቲያናዊ ፍቅር እንዳናሳይ ያግደናል?

ገለልተኝነት ክርስቲያናዊ ፍቅር እንዳናሳይ ያግደናል?

ገለልተኝነት ክርስቲያናዊ ፍቅር እንዳናሳይ ያግደናል?

ክርስቲያን መሆን መጽሐፍ ቅዱስን ከማንበብ፣ ከመጸለይ እንዲሁም እሁድ እሁድ ቤተ ክርስቲያን ከመሳለም የበለጠ ነገርን ይጨምራል። አምላክን የሚያስደስቱና ሰዎችን የሚጠቅሙ ነገሮችን ማድረግን ያካትታል። መጽሐፍ ቅዱስ “ልጆች ሆይ፤ በተግባርና በእውነት እንጂ በቃልና በአንደበት ብቻ አንዋደድ” ይላል። (1 ዮሐንስ 3:18) ኢየሱስ ለሌሎች ከልቡ ያስብ የነበረ ሲሆን ክርስቲያኖችም የእርሱን አርአያ መኮረጅ ይፈልጋሉ። ሐዋርያው ጳውሎስ የእምነት ባልንጀሮቹን “ለጌታ ሥራ ዘወትር የምትተጉ ሁኑ” ሲል አሳስቧቸዋል። (1 ቆሮንቶስ 15:58) ይሁን እንጂ የጌታ ሥራ ምንድን ነው? ድሆችንና የተጨቆኑትን ለመርዳት ሲባል የመንግሥታትን ፖሊሲ ለመቀየር ጥረት ማድረግን ያካትታል? ኢየሱስ ያደረገው እንደዚህ ነበር?

ኢየሱስ በፖለቲካዊ ጉዳዮች ውስጥ እንዲገባ ወይም አንዱን ወገን እንዲደግፍ ግፊት ቢደረግበትም እንዲህ ከማድረግ ተቆጥቧል። ሰይጣን በዓለም መንግሥታት ሁሉ ላይ ሥልጣን ሊሰጠው ያቀረበለትን ግብዣ አልተቀበለም፤ ግብር መክፈልን በተመለከተ በተነሳው ውዝግብ ውስጥ ለመግባትም አልፈለገም። እንዲሁም ሰዎች አንድ ላይ ተሰባስበው ሊያነግሱት ሲሞክሩ ከአካባቢው ገለል ብሏል። (ማቴዎስ 4:8-10፤ 22:17-21፤ ዮሐንስ 6:15) ይሁን እንጂ ገለልተኛ መሆኑ ሌሎችን የሚጠቅም ነገር እንዳያከናውን አላገደውም።

ኢየሱስ ትኩረት ያደረገው ለሰዎች ዘላቂ ጥቅም በሚያስገኘው ነገር ላይ ነበር። አምስት ሺህ ሰዎችን መመገቡና የታመሙትን መፈወሱ የተወሰኑ ሰዎችን ለጊዜው ከችግራቸው ቢገላግላቸውም ትምህርቶቹ መላው የሰው ዘር ዘላለማዊ በረከት የሚያገኝበትን መንገድ ከፍተዋል። ኢየሱስ የሚታወቀው የእርዳታ ዘመቻዎችን በማቀናጀት ሳይሆን “መምህር” በመሆኑ ነበር። (ማቴዎስ 26:18፤ ማርቆስ 5:35፤ ዮሐንስ 11:28) “የተወለድሁት፣ ወደዚህም ዓለም የመጣሁት ስለ እውነት ለመመስከር ነው” ሲል ተናግሯል።—ዮሐንስ 18:37

ከፖለቲካ የተሻለ መልዕክት ማወጅ

ኢየሱስ ያስተማረው እውነት ፖለቲካዊ ፍልስፍና አልነበረም። ከዚህ ይልቅ እርሱ ራሱ ንጉሥ በሚሆንለት መንግሥት ላይ ያተኮረ እውነት ነበር። (ሉቃስ 4:43) ይህ መንግሥት መቀመጫው በሰማይ ሲሆን ሰብዓዊ መንግሥታትን በሙሉ አስወግዶ ለሰው ልጆች ዘላቂ ሰላም ያሰፍናል። (ኢሳይያስ 9:6, 7፤ 11:9፤ ዳንኤል 2:44) በመሆኑም ለሰው ዘር እውነተኛ ተስፋ የሚሆነው ይህ መንግሥት ብቻ ነው። ሰዎች አስተማማኝ የወደፊት ጊዜ ለማየት በሰብዓዊ ኃይሎች እንዲታመኑ ከማበረታታት ይልቅ እንደዚህ ያለውን እርግጠኛ ተስፋ ማወጁ የበለጠ ፍቅር እንዳለን የሚያሳይ አይሆንም? መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል:- “በገዦች አትታመኑ፤ ማዳን በማይችሉ ሥጋ ለባሾችም አትመኩ። መንፈሳቸው ትወጣለች፤ ወደ መሬታቸውም ይመለሳሉ፤ ያን ጊዜም ዕቅዳቸው እንዳልነበር ይሆናል። ረዳቱ የያዕቆብ አምላክ የሆነ፣ ተስፋውንም በአምላኩ በእግዚአብሔር ላይ የጣለ ሰው ምስጉን ነው።” (መዝሙር 146:3-5) በዚህም የተነሳ ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን የላካቸው ‘የመንግሥቱን ወንጌል’ እንዲያውጁ እንጂ መንግሥታትን በተሻለ መንገድ ማዋቀር ስለሚቻልበት መንገድ እንዲሰብኩ አይደለም።—ማቴዎስ 10:6, 7፤ 24:14

ክርስቲያን ሰባኪዎች እንዲያከናውኑት የተሰጣቸው ‘የጌታ ሥራ’ ይህ ነው። የአምላክ መንግሥት ዜጎች እርስ በርሳቸው እንዲዋደዱ ስለሚጠበቅባቸው ይህ መንግሥት የምድርን ሃብት ለሰው ዘር በተመጣጠነ መንገድ በማከፋፈል ድህነትን ማስወገድ ይችላል። (መዝሙር 72:8, 12, 13) ይህ በእርግጥም ሊሰበክ የሚገባው የምስራች ነው።

በዛሬው ጊዜ የይሖዋ ምሥክሮች ይህንን ‘የጌታ ሥራ’ በ235 አገሮች ውስጥ ያከናውናሉ። ኢየሱስ ከሰጠው ትዕዛዝ ጋር በሚስማማ መልኩ ሁሉንም መንግሥታት ያከብራሉ። (ማቴዎስ 22:21) ሆኖም ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ “ከዓለም ለይቼ ስለ መረጥኋችሁ የዓለም አይደላችሁም” በማለት የሰጣቸውን መመሪያም ያስታውሳሉ።—ዮሐንስ 15:19

ፖለቲካ ይሰብኩ የነበሩ አንዳንድ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን በደንብ ካጠኑ በኋላ ለውጥ አድርገዋል። ካቶሊክ አክሽን የተባለ በቤተ ክርስቲያን የሚተዳደር ድርጅት አባል የነበረ አንደ ጣልያናዊ የፖለቲካ ሰው እንዲህ ብሏል:- “በፖለቲካ ውስጥ መሳተፍ የጀመርኩት እያንዳንዱ ሰው ለኅብረተሰቡ ፖለቲካዊና ማኅበራዊ መሻሻል የጎላ አስተዋጽኦ ማድረግ እንዳለበት ስለተሰማኝ ነበር።” ከይሖዋ ምሥክሮች እንደ አንዱ በመሆን የአምላክን መንግሥት ለመስበክ ሲል የአንድ ከተማ ከንቲባ ሆኖ መሥራቱን አቆመ። በፖለቲካ ውስጥ ያሉ ሰዎች በበጎ ተነሳሽነት የሚያደርጓቸው ጥረቶች ፍሬ ቢስ የሚሆኑበትን ምክንያት እንዲህ በማለት ገልጿል:- “ዓለም አሁን ባለበት ሁኔታ ውስጥ የሚገኘው ጥሩ ሰዎች የማኅበረሰቡን ሁኔታ ለማሻሻል ጥረት ስላላደረጉ ሳይሆን ጥቂቶች የሚያደርጉት መልካም ጥረት በብዙኃኑ ክፋት ስለሚዋጥ ነው።”

እውነተኛ ክርስቲያኖች የሰው ዘር ብቸኛ ተስፋ ስለሆነው መንግሥት ለመስበክ ሲሉ ከፖለቲካ ጉዳዮች ገለልተኛ መሆናቸው ሌሎችን የሚጠቅም ነገር እንዳያከናውኑ አያግዳቸውም። የአምላክ መንግሥት ዜጎች እንዲሆኑ እነርሱ የረዷቸው ሰዎች ጎጂ የሆኑ ዝንባሌዎችን ማስወገድን፣ ለሥልጣን አክብሮት ማሳየትን፣ የቤተሰብ ሕይወታቸውን ማሻሻልንና ለቁሳዊ ሃብት ሚዛናዊ አመለካከት መያዝን ተምረዋል። ከሁሉ በላይ ደግሞ የይሖዋ ምሥክሮች ሰዎች ከአምላክ ጋር የቅርብ ዝምድና መመሥረት እንዲችሉ ይረዷቸዋል።

የአምላክ መንግሥት ሰባኪዎች በሚኖሩበት ኅብረተሰብ ውስጥ ጠቃሚ አስተዋጽኦ ያበረክታሉ። ከዚህም በላይ ሰዎች እውን በሆነውና አምላክን ለሚወድዱ ሁሉ ዘላቂ ሰላም በሚያስገኘው መንግሥት ላይ ትምክህታቸውን እንዲጥሉ ይረዳሉ። እነዚህ ክርስቲያኖች ገለልተኛ አቋም በመያዛቸው በዛሬው ጊዜ ዘላቂና ጠቃሚ የሆነ እርዳታ ማበርከት ችለዋል።

[በገጽ 7 ላይ የሚገኝ ሣጥን/ሥዕል]

ከፖለቲካ ወጥቼ የአምላክን መንግሥት መስበክ ጀመርኩ

አቲላ ልጅ እያለ በበሌም፣ ብራዚል የሚገኙ ቀሳውስት ነጻነት ለማምጣት ስለሚደረግ እንቅስቃሴ የሚሰጡትን ትምህርት ተከታትሎ ነበር። የሰው ዘር ከጊዜ በኋላ ከጭቆና እንደሚላቀቅ መስማት ያስደስተው ነበር፤ ስለዚህ የአንድ ንቅናቄ ቡድን አባል ሆነና የተቃውሞ ሰልፎችንና አድማዎችን ማስተባበር ተማረ።

ያም ሆኖ አቲላ በቡድኑ ውስጥ ያሉትን ልጆች ታላቁን አስተማሪ ማዳመጥ በተባለው መጽሐፍ በመጠቀም ማስተማር ያስደስተው ነበር። a መጽሐፉ ስለ መልካም ሥነ ምግባርና ለባለሥልጣናት ስለ መገዛት ይናገራል። ይህም የነጻነት ፍልስፍናውን የሚደግፉ ሰዎች ኢየሱስ ያስተማረውን ከፍ ያለ የሥነ ምግባር ደረጃ የማይከተሉትና አንዳንዶች ሥልጣን ሲይዙ የተጨቆነውን ሕዝብ ችላ የሚሉት ለምን እንደሆነ እንዲያስብ አደረገው። ከዚያም ከቡድኑ ወጣ። ቆየት ብሎም የይሖዋ ምሥክሮች ወደ ቤቱ መጡና ስለ አምላክ መንግሥት ነገሩት። ብዙም ሳይቆይ መጽሐፍ ቅዱስ ማጥናት የጀመረ ሲሆን በሰው ዘር ላይ ለሚደርሰው ጭቆና ትክክለኛው መፍትሔ ምን እንደሆነ አወቀ።

ዚሁ ጊዜ አቲላ ሃይማኖትንና ፖለቲካን አስመልክቶ የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ባዘጋጀችው ሴሚናር ላይ ተገኘ። መምህራኑ “[ፖለቲካና ሃይማኖት] የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ናቸው” በማለት ይናገሩ ነበር። በይሖዋ ምሥክሮች ስብሰባ ላይም ተገኘ። በሁለቱ ስብሰባዎች መካከል ከፍተኛ ልዩነት መኖሩን ተገነዘበ። በይሖዋ ምሥክሮች ስብሰባ ላይ ሲጋራ የሚያጨስ፣ የሚጠጣ ወይም አስጸያፊ ቀልዶችን የሚናገር ሰው አልነበረም። ከምሥክሮቹ ጋር በስብከቱ ሥራ ለመካፈል ወሰነና ብዙም ሳይቆይ ተጠመቀ። የድሆችን ችግር ለማስወገድ ትክክለኛው መፍትሔ የነጻነት ፍልስፍና የማይሆንበትን ምክንያት አሁን ተገንዝቧል።

[የግርጌ ማስታወሻዎች]

a በይሖዋ ምሥክሮች የተዘጋጀ።

[በገጽ 6 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ክርስቲያን አገልጋዮች ገለልተኛ አቋም መያዛቸው ሌሎችን ከመርዳት አያግዳቸውም