በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ከምንም ነገር የላቀ ውርሻ

ከምንም ነገር የላቀ ውርሻ

ከምንም ነገር የላቀ ውርሻ

አረጋዊው ሐዋርያ ዮሐንስ በሕይወቱ ማገባደጃ አካባቢ “ልጆቼ በእውነት የሚመላለሱ መሆናቸውን ከመስማት የሚበልጥ ደስታ የለኝም” በማለት ጽፎ ነበር።—3 ዮሐንስ 4

ይህ ታማኝ ሐዋርያ “ልጆቼ” ሲል ስለ መንፈሳዊ ልጆቹ መናገሩ ነበር። በርካታ ወላጆች በእርሱ አባባል ይስማማሉ። ልጆቻቸውን “በጌታ ምክርና ተግሣጽ” ለማሳደግ በትጋት የጣሩ ሲሆን አሁን ልጆቻቸው አድገው ‘በእውነት ሲመላለሱ’ ሲመለከቱ በጣም ይደሰታሉ። (ኤፌሶን 6:4) ወላጆች ለልጆቻቸው ሊሰጧቸው ከሚችሉት ከምንም ነገር የላቀው ውርሻ የዘላለም ሕይወት የሚያስገኘውን መንገድ ማስተማር ነው። እንዲህ የምንለው ይሖዋ በሚፈልገው መንገድ ሕይወትን መምራትን የሚጨምረው ለአምላክ ያደሩ መሆን “ለአሁኑም ሆነ ለሚመጣው ሕይወት ተስፋ ስላለው” ነው።—1 ጢሞቴዎስ 4:8

ፍጹም አባት የሆነው ይሖዋ ልጆቻቸውን በመንፈሳዊ ለማሠልጠን ጠንክረው ለሚሠሩ ፈሪሃ አምላክ ያላቸው ወላጆች ትልቅ ግምት አለው። ልጆችም ለወላጆቻቸው ጥረት ምላሽ በመስጠት አብረዋቸው በእውነተኛው አምልኮ ሲካፈሉ ትልቅ ደስታ ያገኛሉ። እነዚህ ልጆች እያደጉ ሲሄዱ በልጅነታቸው ስላደረጓቸው መንፈሳዊ እንቅስቃሴዎች ብዙ ደስ የሚሉ ትዝታዎች ይኖሯቸዋል። አንዳንዶች በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ለመጀመሪያ ጊዜ ክፍል ያቀረቡበትን ዕለት ሲያስታውሱ ደስ ይላቸዋል። a ወይም ከወላጆቻቸው ጋር ከቤት ወደ ቤት ሄደው ለመጀመሪያ ጊዜ ለሰዎች የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ያነበቡበትን ዕለት ያስታውሳሉ። ወላጆቻቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች መማሪያ መጽሐፌ ወይም ታላቁን አስተማሪ ማዳመጥ b ከተባሉት መጽሐፍት ያነቡላቸው የነበረውን እንዴት ሊረሱት ይችላሉ? ጋብሪኤል ምን ደስ ይለው እንደነበር ሲናገር እንዲህ ይላል:- “ገና የአራት ዓመት ልጅ ሳለሁ እናቴ በየዕለቱ ምግብ ስታበስል ትዘምርልኝ ነበር። አንድ የመንግሥቱ መዝሙር አሁን ድረስ ጥልቅ ስሜት ያሳድርብኛል። ካደግሁ በኋላ ይህ መዝሙር ይሖዋን ማገልገል ያለውን አስፈላጊነት እንድገነዘብ ረድቶኛል።” ምናልባት እናንተም ጋብርኤል የጠቀሰውን ይህን ማራኪ መዝሙር ታስታውሱት ይሆናል። ለይሖዋ የውዳሴ መዝሙር ዘምሩ በተሰኘው የመዝሙር መጽሐፍ ላይ 157ኛው መዝሙር (በአማርኛው መዝሙር መጽሐፍ ተራ ቁጥር 68) ሲሆን “ይሖዋን በወጣትነት ማምለክ” የሚል ርዕስ አለው።

መዝሙሩ “ምስጋና አዘጋጀ ከ’ፃናት/ጮክ ብለው የ’ሱስን አወደሱት” በሚሉት ስንኞች ይጀምራል። አዎን፣ ከኢየሱስ ጋር ጊዜ ለማሳለፍ የታደሉ ልጆች የነበሩ ሲሆን ቅንነት የሚንጸባረቅበት ደስ የሚለው ባሕርያቸው ሳይማርከው አልቀረም። እንዲያውም ልጆች አዲስ ነገር ለመማር ያላቸውን ጉጉት ተከታዮቹ ሊኮርጁት እንደሚገባ ተናግሯል። (ማቴዎስ 18:3, 4) ስለዚህ ልጆች በይሖዋ አምልኮ ውስጥ የራሳቸው ቦታ አላቸው። መዝሙሩም በመቀጠል “አምላክን ያወድሳሉ ልጆች” ይላል።

በርካታ ወጣቶች በቤት፣ በትምህርት ቤትና በሌሎች ቦታዎች ምሳሌ የሚሆን ምግባር በማሳየት ለአምላክና ለቤተሰባቸው ክብር አምጥተዋል። ወላጆቻቸው “እውነት ወዳዶች በመሆናቸው” ምንኛ ተባርከዋል! (ዘዳግም 6:7) ፈሪሃ አምላክ ያላቸው ወላጆች እንደ አንድ አፍቃሪ አባት ሆኖ ፍጡራኑ የሚሄዱበትን መንገድ የሚያስተምራቸውን አምላክን ይኮርጃሉ። ይህም ትልቅ በረከት ያስገኝላቸዋል። እነርሱም በቤተሰባቸው ውስጥ ያሉትን ልጆች ሲያስተምሯቸውና ልጆቹም ሲታዘዟቸው “ደስ ይላቸዋል።” (ኢሳይያስ 48:17, 18) በሜክሲኮ በሚገኘው የይሖዋ ምሥክሮች ቅርንጫፍ ቢሮ ውስጥ የምታገለግለው አንሄሊካ እንዲህ ትላለች:- “ወላጆቼ ሁልጊዜ የመጽሐፍ ቅዱስን መሠረታዊ ሥርዓቶች በሥራ ላይ ለማዋል ጥረት ያደርጉ ነበር። ይህም የልጅነት ጊዜዬን ደስተኛ ሆኜ ለማሳለፍ አስችሎኛል።”

እንደ አንሄሊካ ያሉ ክርስቲያኖች መንፈሳዊ ውርሻን አጥብቆ መያዝ የሚክስ እንደሆነ ይስማማሉ። ምናልባት የእናንተም ወላጆች በትክክለኛው የክርስትና ጎዳና እንድትመላለሱ ኮትኩተው እያሳደጓችሁ ይሆናል። ከሆነ ይኸው መዝሙር “ወጣቶች መንገዳችሁን አጥሩ” በማለት በዚያው እንድትቀጥሉ ያበረታታችኋል። ወደፊት የራሳችሁን ውሳኔ የምታደርጉበት ጊዜ ይመጣል። ስለዚህ ከአሁኑ “በይሖዋ መመካት ተማሩ” እንጂ “አትድከሙ ለመሆን ዝነኛ።”

ሳይታወቃችሁ ዝነኛ መሆንን በሕይወታችሁ ውስጥ ካስቀደማችሁ የተሰጣችሁ ሥልጠና ሁሉ መና ሆኖ ሊቀርና የወደፊት ሕይወታችሁን ልታበላሹ ትችላላችሁ። ዝነኛ የመሆን ፍላጎት በመንፈሳዊ እንድትዘናጉ ሊያደርጋችሁ ይችላል። አንዳንዶች ጥሩ ሰዎች ከሚመስሉ እንዲያውም የሚማርክ ቁመና ካላቸው ሆኖም በክርስቲያናዊ የሥነ ምግባር መሥፈርቶች ለመመራት ከማይፈልጉ ሰዎች ጋር መቀራረብ ጀምረዋል። የወጣቶች ጥያቄ—እውነተኛ ጓደኞች ማፍራት የምችለው እንዴት ነው? በተሰኘው የቪዲዮ ፊልም ላይ ዋና ገጸ ባሕርይ የነበረችው ታራ ያጋጠማት ሁኔታ ይህን ይመስል ነበር። እንደ ታራ በእውነተኛው አምልኮ ለመካፈል ምንም ፍላጎት ከሌላቸው ሰዎች ጋር የሚቀራረቡ ክርስቲያን ወጣቶች ሁሉ ውለው አድረው መዝሙሩ እንደሚለው “መጥፎ ባልንጀራ አጥፊ ነውና” ማለታቸው አይቀርም። ጥሩ ልማዶችን ለማዳበር የዓመታት ጥረት የሚጠይቅ ቢሆንም በአጭር ጊዜ ውስጥ ሊበላሹ ይችላሉ።

ፈሪሃ አምላክ እንዳለን በሚያሳይ ሁኔታ መኖር ቀላል እንዳልሆነ አይካድም። ቢሆንም መዝሙሩ አክሎ እንደሚለው “በልጅነት ብታስቡ አምላክን” እንዲሁም “በእውነት ብታመልኩ ይሖዋን” ስኬታማ ለመሆን የሚያስችላችሁ አስተማማኝ መሠረት መጣል ትችላላችሁ። እያደጋችሁ ስትሄዱም “ብዙ በረከት ታገኛላችሁ።” የይሖዋ ፍቅራዊ አመራር እስካልተለያችሁ ድረስ በእርሱ ዓይን መልካም የሆነውን ከማድረግ ምንም ነገር ሊያግዳችሁ እንደማይችል ይበልጥ እየተገነዘባችሁ ትሄዳላችሁ። ፈሪሃ አምላክ ያለው የጎለመሰ ክርስቲያን ልትሆኑ የምትችሉት በዚህ መንገድ ነው። ከዚህም በላይ የተሰጣችሁን ክርስቲያናዊ ሥልጠና በአግባቡ ከተጠቀማችሁበት “አምላክንም ታስደስታላችሁ።” ደግሞስ አምላክን ከማስደሰት የበለጠ ምን ክብር ይኖራል?—ምሳሌ 27:11

ስለዚህ ወጣቶች ከይሖዋና ከክርስቲያን ወላጆቻችሁ ያገኛችሁት ሥልጠና ምን ያህል ትልቅ ዋጋ እንዳለው አስታውሱ። እነርሱ ለእናንተ ያላቸው ፍቅር በይሖዋ ፊት መልካም የሆነውን ለማድረግ ሊያነሳሳችሁ ይገባል። እንደ ኢየሱስ ክርስቶስና እንደ ታማኙ ወጣት ጢሞቴዎስ እናንተም በሰማይ የሚኖረውን አባታችሁንና ወላጆቻችሁን ልታስደስቱ ትችላላችሁ። ወደፊት ወላጅ ከሆናችሁ ደግሞ ቀደም ሲል የጠቀስናት አንሄሊካ በተናገረችው በሚከተለው አባባል እንደምትስማሙ አያጠራጥርም:- “ልጅ ከወለድኩ ገና ከጨቅላነቱ አንስቶ የይሖዋን ፍቅር በልቡ ውስጥ ለመቅረጽና ሕይወቱን በዚያ እንዲመራ ለማድረግ የተቻለኝን ሁሉ እጥራለሁ።” በእርግጥም ወደ ዘላለም ሕይወት የሚመራውን ቀና መንገድ ማስተማር ወላጆች ለልጆቻቸው ሊሰጧቸው ከሚችሉት ከምንም ነገር የላቀ ውርሻ ነው!

[የግርጌ ማስታወሻዎች]

a መጽሐፍ ቅዱስን የማስተማሩ ሥራ ክፍል የሆነው ይህ ትምህርት ቤት በይሖዋ ምሥክሮች ጉባኤ ውስጥ የሚካሄድ ሲሆን ወጣቶችም ሆኑ አረጋውያን ይሳተፉበታል።

b እነዚህ ጽሑፎች በይሖዋ ምሥክሮች የታተሙ ናቸው።