በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

“እንዲህ ብላችሁ ጸልዩ”

“እንዲህ ብላችሁ ጸልዩ”

“እንዲህ ብላችሁ ጸልዩ”

የጌታ ጸሎት የሚባለውን ታውቀዋለህ? ይህ ጸሎት ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ ያስተማረው የናሙና ጸሎት ነው። ዝነኛ በሆነው የተራራ ስብከቱ ላይ “እናንተ ግን እንዲህ ብላችሁ ጸልዩ” ብሎ ነበር። (ማቴዎስ 6:9) ይህንን ጸሎት ያስተማረው ኢየሱስ በመሆኑ አብዛኛውን ጊዜ የጌታ ጸሎት ተብሎ የሚጠራ ሲሆን “አባታችን ሆይ” በመባልም ይታወቃል።—በግዕዝ አቡነ ዘበሰማያት

በዓለም ዙሪያ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች የጌታን ጸሎት በቃላቸው የሚያውቁት ከመሆኑም በላይ አዘውትረው አንዳንዶችም በየቀኑ ይደግሙታል። በቅርብ ዓመታት ውስጥ በርካታ ሰዎች በትምህርት ቤቶችና ሕዝብ በሚሰበሰብባቸው ቦታዎች በአንድነት ይህንን ጸሎት አቅርበዋል። የጌታ ጸሎት ይህን ያህል ትልቅ ቦታ የተሰጠው ለምንድን ነው?

ሲፕርያን የተባሉት የሦስተኛው መቶ ዘመን የሃይማኖት ምሑር እንዲህ ሲሉ ጽፈዋል:- “ክርስቶስ ካስተማረን ጸሎት የበለጠ መንፈሳዊ ሐሳብ የያዘ ምን ጸሎት ሊኖር ይችላል? እርሱ ራሱ እውነት የሆነው ወልድ ካስተማረን ጸሎት የተሻለ ለአብ የሚቀርብ ምን እውነተኛ ጸሎት ሊኖር ይችላል?”—ዮሐንስ 14:6

የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን የሃይማኖት ማስተማሪያ መጽሐፍ አባታችን ሆይ የተባለው ጸሎት “ዋነኛው የክርስቲያኖች ጸሎት” እንደሆነ ገልጿል። ዘ ዎርልድ ቡክ ኢንሳይክሎፒዲያ ይህ ጸሎት በሁሉም የሕዝበ ክርስትና ሃይማኖቶች ውስጥ ትልቅ ቦታ እንደሚሰጠው ከጠቀሰ በኋላ “ከክርስትና እምነት መሠረታዊ ትምህርቶች” አንዱ እንደሆነ ይገልጻል።

ይሁን እንጂ የጌታን ጸሎት ከሚደግሙት ሰዎች አብዛኞቹ የጸሎቱን ሙሉ ትርጉም እንደማይረዱት ልብ ሊባል ይገባል። ኦታዋ ሲቲዝን የተሰኘው የካናዳ ጋዜጣ እንዲህ ይላል:- “በየትኛውም የክርስትና እምነት ውስጥ ያደግህ ከሆንህ የጌታን ጸሎት ለአፍታም ቆም ሳትል በአንዴ ትወጣው ይሆናል። ይሁን እንጂ ረጋ ብለህ ትርጉሙን እያስተዋልክ ይህንን ጸሎት ማቅረብ ሊያስቸግርህ ይችላል።”

ለአምላክ የምናቀርበውን ጸሎት ትርጉም መረዳታችን ያን ያህል አስፈላጊ ነው? ኢየሱስ የጌታን ጸሎት የሰጠን ለምንድን ነው? ይህ ጸሎት ለአንተ ምን ትርጉም አለው? የእነዚህን ጥያቄዎች መልስ እስቲ እንመልከት።