በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የአንባቢያን ጥያቄዎች

የአንባቢያን ጥያቄዎች

የአንባቢያን ጥያቄዎች

ሐዋርያው ዮሐንስ “ፍጹም ፍቅር . . . ፍርሀትን አውጥቶ ይጥላል” በማለት ተናግሯል፤ “ፍጹም ፍቅር” ሲል ምን ማለቱ ነበር? አውጥተን የምንጥለውስ “ፍርሀት” ምንድን ነው?

ሐዋርያው ዮሐንስ እንዲህ ብሎ ጽፏል:- “በፍቅር ፍርሀት የለም፤ ፍጹም ፍቅር ግን ፍርሀትን አውጥቶ ይጥላል፤ ፍርሀት ከቅጣት ጋር የተያያዘ ነውና። የሚፈራም ሰው ፍቅሩ ፍጹም አይደለም።”—1 ዮሐንስ 4:18

በጥቅሱ ዙሪያ ካለው ሐሳብ ማስተዋል እንደምንችለው ሐዋርያው ዮሐንስ በድፍረት ስለ መናገር በተለይ ደግሞ ለአምላክ ባለን ፍቅርና እርሱን በድፍረት በማነጋገር መካከል ስላለው ዝምድና እየተናገረ ነበር። ይህንን በቁጥር 17 ላይ ካለው ሐሳብ መረዳት ይቻላል፤ ጥቅሱ እንዲህ ይላል:- “በፍርድ ቀን ድፍረት ይኖረን ዘንድ፣ ፍቅር በዚህ ዐይነት በመካከላችን ፍጹም ሆኖአል።” አንድ ክርስቲያን አምላክን የሚወድድበት መጠንና በውስጡ ያለው አምላክ ይወደኛል የሚለው ስሜት፣ በሚጸልይበት ጊዜ በድፍረት እንዲናገር አሊያም ድፍረት እንዲያጣ ቀጥተኛ ተጽዕኖ ያደርጉበታል።

“ፍጹም ፍቅር” የሚለው አነጋገር ልዩ ትርጉም አለው። መጽሐፍ ቅዱስ “ፍጹም” የሚለውን ቃል ሙሉ ለሙሉ ፍጹም መሆንን ለማመልከት ብቻ ሳይሆን በተወሰነ ደረጃ ፍጽምናን ማሳየትንም ለማመልከት ይጠቀምበታል። ለምሳሌ ያህል ኢየሱስ በተራራ ስብከቱ ላይ “ስለዚህ የሰማይ አባታችሁ ፍጹም እንደ ሆነ እናንተም ፍጹማን ሁኑ” ብሎ ነበር። ኢየሱስ ተከታዮቹ የሚወዷቸውን ብቻ ቢወዱ ፍቅራቸው ጉድለት ያለበት ወይም ያልተሟላ እንደሚሆን እየነገራቸው ነበር። ፍቅራቸው ፍጹም ሊሆን በሌላ አነጋገር ጠላቶቻቸውን ጭምር በመውደድ የተሟላ ፍቅር ሊያሳዩ ይገባ ነበር። በተመሳሳይም ሐዋርያው ዮሐንስ “ፍጹም ፍቅር” በማለት ሲጽፍ ከልብ ስለሚመነጨው፣ እየዳበረ ስለሚሄደውና የአንድን ሰው የሕይወት ዘርፍ ሁሉ ስለሚያቅፈው አምላካዊ ፍቅር መናገሩ ነበር።—ማቴዎስ 5:46-48፤ 19:20, 21

አንድ ክርስቲያን ከአምላክ ጋር በጸሎት በሚነጋገርበት ወቅት ኃጢአተኛ መሆኑንና ፍጽምና እንደሚጎድለው በሚገባ ያውቃል። ነገር ግን ለይሖዋ ያለው ፍቅር እያደገ ከሄደና አምላክ ይወደኛል የሚል ስሜት በውስጡ ከኮተኮተ ተቀባይነት አጣለሁ ወይም በኃጢአቴ እኮነናለሁ ብሎ አይፈራም። ከዚህ ይልቅ በልቡ ውስጥ ያለውን በነጻነት ይገልጻል እንዲሁም አምላክ በፍቅር ተገፋፍቶ ባዘጋጀው የክርስቶስ ቤዛዊ መሥዋዕት አማካኝነት ይቅርታ ለማግኘት ይለምናል። በተጨማሪም የሚያቀርባቸው ልመናዎች በአምላክ ዘንድ ተቀባይነት እንደሚያገኙ እርግጠኛ ይሆናል።

አንድ ሰው “ፍጹም ፍቅር” ሊኖረውና በኃጢአቴ ምክንያት እኮነናለሁ ወይም ተቀባይነት አጣለሁ የሚለውን ፍርሃት ‘አውጥቶ ሊጥል’ የሚችለው እንዴት ነው? ሐዋርያው ዮሐንስ እንዲህ ብሏል:- “ማንም ቃሉን [የአምላክን ቃል] ቢጠብቅ፣ በእውነት የእግዚአብሔር ፍቅር በእርሱ ፍጹም ሆኖአል።” (1 ዮሐንስ 2:5) እስቲ አስበው፤ አምላክ ገና ኃጢአተኞች ሳለን ከወደደን ከልባችን ንስሐ ከገባንና በትጋት ‘ቃሉን ከጠበቅን’ የበለጠ አይወደንም? (ሮሜ 5:8፤ 1 ዮሐንስ 4:10) አዎን፣ ታማኝነታችንን እስከጠበቅን ድረስ እኛም ሐዋርያው ጳውሎስ ስለ አምላክ የተሰማው ዓይነት ስሜት ይሰማናል፤ እንዲህ ብሏል:- “ለገዛ ልጁ ያልሳሳለት፣ ነገር ግን ለሁላችንም አሳልፎ የሰጠው እርሱ፣ ሁሉንስ ነገር ከእርሱ ጋር እንደ ምን በልግስና አይሰጠን?”—ሮሜ 8:32