በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

“በእግዚአብሔር ዘንድ ሀብታም” ነህ?

“በእግዚአብሔር ዘንድ ሀብታም” ነህ?

“በእግዚአብሔር ዘንድ ሀብታም” ነህ?

ኢየሱስ ክርስቶስ ከተናገራቸው ስሜት የሚነኩ ብዙ ምሳሌዎች መካከል ስለ አንድ ሀብታም ባለርስት የተናገረው ምሳሌ ይገኝበታል። ይህ ባለርስት የወደፊት ሕይወቱን አስተማማኝ ለማድረግ በማሰብ ሰፋፊ ጎተራዎችን ለመሥራት እቅድ አወጣ። ይሁን እንጂ ይህ ሰው በምሳሌው ላይ “ሞኝ” ተብሎ ተጠርቷል። (ሉቃስ 12:16-21) እንዲህ ያለ ኃይለኛ ቃል መጠቀም ያስፈለገው ለምንድን ነው?

ከሁኔታው መረዳት እንደምንችለው የዚህ ሀብታም ሰው እቅድ አምላክን ከግምት ውስጥ ያስገባ አልነበረም፤ በተጨማሪም ብዙ ምርት አግኝቶ እንኳ አምላክን ሳያመሰግን ቀርቷል። (ማቴዎስ 5:45) ከዚህ ይልቅ “ነፍሴ ሆይ፤ ለብዙ ዘመን የሚበቃሽ ሀብት አከማችቼልሻለሁ፤ እንግዲህ ዕረፊ፤ ብዪ፤ ጠጪ፤ ደስም ይበልሽ” በማለት በጉራ ተናገረ። አዎን፣ የድካሙ ፍሬ እንደ “ረጅም ግንብ” ከለላ የሚሆንለት መስሎት ነበር።—ምሳሌ 18:11

ደቀ መዝሙሩ ያዕቆብ ይህን ዓይነቱን የትዕቢት መንፈስ አስመልክቶ ሲያስጠነቅቅ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “እናንተ ‘ዛሬ ወይም ነገ ወደዚህች ወይም ወደዚያች ከተማ እንሄዳለን፤ በእርሷም አንድ ዓመት እንቈያለን፤ እንነግዳለን፤ እናተርፋለንም’ የምትሉ እንግዲህ ስሙ። ነገ የሚሆነውን እንኳ አታውቁም። ሕይወታችሁ ምንድን ናት? ለጥቂት ጊዜ ታይቶ ኋላ እንደሚጠፋ እንፋሎት ናችሁ።”—ያዕቆብ 4:13, 14

ኢየሱስ በምሳሌው ላይ ለጠቀሰው ሀብታም ሰው “አንተ ሞኝ፤ ነፍስህን በዚህች ሌሊት ከአንተ ሊወስዱ ይፈልጓታል፤ እንግዲህ፣ ለራስህ ያከማቸኸው ለማን ይሆናል?” በማለት ስለተነገረው በእርግጥም ከላይ የተጠቀሱት የያዕቆብ ቃላት እውነት ናቸው። ይህ ባለጸጋ አንዴ ታይቶ እንደሚጠፋ እንፋሎት ሕልሙ እውን ሳይሆን ይሞታል። በዚህ ምሳሌ ውስጥ ምን ትምህርት ለማስጨበጥ እንደተፈለገ ገብቶናል? ኢየሱስ “ስለዚህ ለራሱ ሀብት የሚያከማች፣ ዳሩ ግን በእግዚአብሔር ዘንድ ሀብታም ያልሆነ ሰው መጨረሻው ይኸው ነው” ብሏል። ታዲያ አንተ “በእግዚአብሔር ዘንድ ሀብታም” ነህ?