በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የአንባቢያን ጥያቄዎች

የአንባቢያን ጥያቄዎች

የአንባቢያን ጥያቄዎች

በዘፍጥረት 44:5 ላይ የተጠቀሰው ሐሳብ የአምላክ ታማኝ አገልጋይ የነበረው ዮሴፍ የተሰወረ ነገርን የሚያውቅበት ልዩ የብር ዋንጫ እንደነበረው ያመለክታል?

ዮሴፍ የትኛውንም ዓይነት የጥንቆላ ተግባር ይፈጽም ነበር ለማለት የሚያስችል አንዳች ምክንያት የለም።

ዮሴፍ አስማታዊ ድርጊቶችን ተጠቅሞ የወደፊቱን ጊዜ ለማወቅ ስለሚደረገው ጥረት ምን ዓይነት አመለካከት እንደነበረው መጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ ይናገራል። ቀደም ብሎ የፈርዖንን ሕልም እንዲፈታ በተጠየቀ ጊዜ ዮሴፍ ወደፊት የሚፈጸሙ ክንውኖችን ‘ትርጉም መስጠት’ የሚችለው አምላክ ብቻ እንደሆነ በተደጋጋሚ ተናግሯል። በመሆኑም ዮሴፍ ስለ ወደፊቱ ጊዜ ዝርዝር ሁኔታዎችን እንዲያውቅ የረዳው ምትሃታዊ ኃይል ሳይሆን የሚያመልከው እውነተኛ አምላክ መሆኑን ፈርዖን ሳይቀር ተገንዝቧል። (ዘፍጥረት 41:16, 25, 28, 32, 39) ከጊዜ በኋላ ለሙሴ በተሰጠው ሕግ ላይ ይሖዋ፣ የወደፊቱን ጊዜ ማሳወቅ የሚችለው እርሱ ብቻ እንደሆነ አስረግጦ በመንገር ሕዝቡ በአስማት ወይም በጥንቆላ ድርጊት እንዳይካፈል ከልክሏል።​—⁠ዘዳግም 18:10-​12

ታዲያ ዮሴፍ፣ ‘የተሰወረ ነገርን የሚያውቅበት’ ዋንጫ እንዳለው በአገልጋዩ አማካኝነት የተናገረው ለምንድን ነው? a (ዘፍጥረት 44:5) ይህ ቃል በተነገረበት ጊዜ የነበሩትን አንዳንድ ሁኔታዎች በጥንቃቄ መመርመር ይኖርብናል።

የዮሴፍ ወንድሞች ተከስቶ በነበረው አስከፊ ረሐብ ሳቢያ እህል ለመሸመት ወደ ግብጽ ተጉዘው ነበር። ከዓመታት በፊት እነዚሁ ወንድማማቾች ዮሴፍን ለባርነት ሸጠውታል። አሁን ሳያውቁት በግብጽ ውስጥ የእህል አስተዳዳሪ የሆነውን ወንድማቸውን የእርዳታ እጁን እንዲዘረጋላቸው ጠየቁት። በዚህ ጊዜ ዮሴፍ ማንነቱን ከመግለጥ ይልቅ ሊፈትናቸው ወሰነ። ዮሴፍ እንዲህ ለማድረግ የፈለገው ለሠሩት ጥፋት ከልብ መጸጸታቸውን ለማወቅ ነበር። ከዚህም በላይ ለወንድማቸው ለብንያምም ሆነ ብንያምን በጣም ይወደው ለነበረው ለአባታቸው ለያዕቆብ ምን ያህል ፍቅር እንዳላቸው ማወቅ ፈልጎ ነበር። በመሆኑም ዮሴፍ ይህን ግቡን ለማሳካት አንድ ብልሃት ፈጠረ።​—⁠ዘፍጥረት 41:55-44:3

ዮሴፍ ከአገልጋዮቹ መካከል አንዱን ጠርቶ ወንድሞቹ የገዙትን እህልና እህሉ የተገዛበትን ገንዘብ በየስልቻዎቻቸው እንዲከትላቸው ነገረው። እንዲሁም የራሱን የብር ዋንጫ በብንያም ስልቻ አፍ ውስጥ ከትቶ እንዲያስር አዘዘው። ይህን ሁሉ ሲያደርግ ዮሴፍ ራሱን ያቀረበው እንደ አንድ የአረማዊ አገር አስተዳዳሪ አድርጎ ነው። ዮሴፍ ማንነቱን፣ ነገረ ሥራውንና ቋንቋውን በመለወጥ ፈጽሞ ያልጠረጠሩት ወንድሞቹ እንደሚጠብቁት ዓይነት አስተዳዳሪ ሆኖ ቀረባቸው።

ዮሴፍ ወንድሞቹ ፊቱ በቀረቡ ጊዜ አሁንም ማንነቱን በመደበቅ “እንደ እኔ ያለ ሰው ስውር ነገርን የሚያውቅበት ልዩ ጥበብ እንዳለው አታውቁምን?” ሲል ጠየቃቸው። (ዘፍጥረት 44:15) በመሆኑም ዋንጫው ዮሴፍ ወንድሞቹን ለማውጣጣት የተጠቀመበት ብልሃት ብቻ መሆኑ ግልጽ ነው። ብንያም ዋንጫውን እንዳልሰረቀው ሁሉ ዮሴፍም የተሰወረ ነገርን ለማወቅ በዋንጫ አይጠቀምም ነበር።

[የግርጌ ማስታወሻ]

a በኤፍ ሲ ኩክ የተዘጋጀው ዘ ሆሊ ባይብል ዊዝ አን ኤክስፕላናቶሪ ኤንድ ክሪቲከል ኮሜንተሪ የተባለው መጽሐፍ በጥንት ዘመን ይደረግ የነበረውን ይህን ዓይነቱን ልማድ አስመልክቶ የሚከተለውን አስፍሯል:- “ሰዎች ውኃ በተሞላ ዋንጫ ውስጥ እንደ ወርቅ፣ ብር ወይም እንቁ ያሉ ነገሮችን በመክተትና ሁኔታውን በማስተዋል አሊያም እንዲሁ ውኃውን እንደ መስታወት በመመልከት ይህን ድርጊት ይፈጽሙ ነበር።” የመጽሐፍ ቅዱስ ምሑር የሆኑት ክሪስተፈር ዎርድስወርዝ “አንዳንድ ጊዜ ዋንጫው በውኃ ከተሞላ በኋላ የፀሐይ ብርሃን ውኃው ላይ ሲያርፍ የሚፈጥረውን ምስል በመመልከት መልስ ይሰጣል” በማለት ተናግረዋል።