በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የአንባቢያን ጥያቄዎች

የአንባቢያን ጥያቄዎች

የአንባቢያን ጥያቄዎች

ኢየሱስ በማቴዎስ 5:22 ላይ ያስጠነቀቀው ስለ የትኞቹ ሦስት አደገኛ ሁኔታዎች ነው?

ኢየሱስ ክርስቶስ በተራራ ስብከቱ ላይ ተከታዮቹን እንደሚከተለው ሲል አስጠንቅቋቸዋል:- “እኔ ግን እላችኋለሁ፤ ወንድሙን ያለ አግባብ የሚቈጣ [“በአካባቢው ሸንጎ፣” NW ] ይፈረድበታል፤ ማንም ወንድሙን ‘ጅል’ የሚል በሸንጎ [“በከፍተኛ ፍርድ ቤት፣” NW ] ፊት ይጠየቅበታል፤ ‘ደደብ’ የሚለው ደግሞ የገሃነመ እሳት ፍርድ ይጠብቀዋል።”​—⁠ማቴዎስ 5:​22

እዚህ ላይ ኢየሱስ እንደ ኃጢአቱ ክብደት እየጨመረ ስለሚሄደው ቅጣት ለማስረዳት አይሁዳውያን በደንብ የሚያውቋቸውን የፍርድ ሥርዓቶች ማለትም የአካባቢ ሸንጎን፣ ከፍተኛ ፍርድ ቤትንና ገሃነመ እሳትን ተጠቅሟል።

በመጀመሪያ ኢየሱስ፣ በወንድሙ ላይ የሚቆጣ ማንኛውም ሰው “በአካባቢው ሸንጎ” ፊት ሊቀርብ እንደሚገባ ተናገረ። በተለምዶ እንዲህ ዓይነቶቹ ፍርድ ቤቶች 120 ወይም ከዚያ በላይ አባ ወራዎች ባሉበት ከተማ ውስጥ ይቋቋሙ ነበር። (ማቴዎስ 10:17፤ ማርቆስ 13:9) በአካባቢ ሸንጎ ውስጥ የሚሰየሙት ዳኞች በነፍስ ማጥፋት ወንጀል ላይ እንኳ ሳይቀር ፍርድ የመስጠት ሥልጣን ነበራቸው። (ዘዳግም 16:18፤ 19:12፤ 21:​1, 2) በመሆኑም ኢየሱስ፣ ለወንድሙ የጥላቻ ስሜት የሚያሳድር ሰው ከባድ ኃጢአት እየፈጸመ መሆኑን ማሳየቱ ነው።

ቀጥሎም ኢየሱስ “ወንድሙን ‘ጅል’” ብሎ የሚሰድብ ሰው በከፍተኛ ፍርድ ቤት መቅረብ እንደሚገባው ተናግሯል። “ጅል” ተብሎ የተተረጎመው ረሀካ የተሰኘ ግሪክኛ ቃል “ባዶ” ወይም “ደንቆሮ” ማለት ነው። ዘ ኒው ቴየርስ ግሪክ-ኢንግሊሽ ሌክሲከን ኦቭ ዘ ኒው ቴስታመንት እንደሚለው ከሆነ ቃሉን “በኢየሱስ ዘመን የነበሩ አይሁዳውያን እንደ ስድብ አድርገው ይጠቀሙበት ነበር።” ይህም በመሆኑ ኢየሱስ አንድ ሰው ከጥላቻ በመነሳሳት የአገሩን ልጅ አንቋሽሾ መናገሩ በቀላሉ የሚታይ ነገር አለመሆኑን በመግለጽ አስጠንቅቋል። እዚህ ላይ ኢየሱስ፣ ይህን ቃል ተጠቅሞ የሚሳደብ ሰው ጉዳዩ በአካባቢው ሸንጎ ሳይሆን ኢየሩሳሌም በሚገኘው ከፍተኛ ፍርድ ቤት መታየት እንዳለበት የገለጸ ያህል ነበር፤ ሳንሄድሪን የሚባለው ሸንጎ ሊቀ ካህኑን፣ 70 ሽማግሌዎችንና ጸሐፍትን ያቀፈ ነበር።​—⁠ማርቆስ 15:1

በመጨረሻም ኢየሱስ አንድ ሰው ሌላውን “ደደብ” ቢለው የገሃነመ እሳት ፍርድ እንደሚገባው ገለጸ። ‘ገሃነም’ የሚለው ቃል የመጣው ጌህሂኖም ከተባለው የዕብራይስጥ ቃል ሲሆን ትርጉሙም “የሄኖም ሸለቆ” ማለት ነው። ይህ ሸለቆ ከጥንቷ ኢየሩሳሌም በስተ ምዕራብና በስተ ደቡብ በኩል ይገኝ ነበር። በኢየሱስ ዘመን ስፍራው በክብር ሊቀበሩ የማይገባቸውን ወንጀለኞች ሬሳ ጨምሮ ሌሎች ቆሻሻዎች የሚጣሉበት ቦታ ነበር። ስለሆነም ‘ገሃነም’ የሚለው ቃል ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ መጥፋትን ለማመልከት ተስማሚ ምሳሌ ሆኗል።

“ደደብ” የሚለው አባባል የሚያመለክተው ምንድን ነው? ኢየሱስ እዚህ ላይ የተጠቀመበት አገላለጽ “ዓመጸኛ” ወይም “አድመኛ” የሚል ትርጉም ካለው የዕብራይስጥ ቃል ጋር ይመሳሰላል። ቃሉ በሥነ ምግባር የረከሰን፣ ከሃዲንና በአምላክ ላይ ያመጸን ሰው ያመለክታል። በመሆኑም አንድ ሰው “ደደብ” ብሎ መሳደቡ፣ የተሰደበው ግለሰብ በአምላክ ላይ ያመጸ ሰው ሊደርስበት የሚገባው ቅጣት ይኸውም የዘላለም ጥፋት ይገባዋል ማለቱ ነበር። በአምላክ ዓይን ሲታይ እንዲህ ዓይነቱን የውግዘት ቃል በሌላው ላይ የሚናገር ሰው ራሱ ይህ ቅጣት ማለትም ዘላለማዊ ጥፋት ይገባዋል።​—⁠ዘዳግም 19:17-​19

ኢየሱስ የሙሴ ሕግ ከሚያስተላልፈው መንፈስ የሚልቁ መሥፈርቶችን ለደቀ መዛሙርቱ ሰጥቷቸዋል። በጊዜው የነበሩ ሰዎች ነፍስ ያጠፋ ሰው “በሸንጎ ፊት” መቅረብ እንደሚገባው ቢያምኑም እንኳ ኢየሱስ የነፍስ ማጥፋት ድርጊቱ ብቻ ሳይሆን የልባቸው ሁኔታም ሊያስጠይቃቸው እንደሚችል በመናገር ደቀ መዛሙርቱን አሳስቧቸዋል። ኢየሱስ ተከታዮቹ ወንድሞቻቸውን መጥላታቸው አደገኛ እንደሆነ አስተምሯቸዋል።​—⁠ማቴዎስ 5:​21, 22