በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

መጽሐፍ ቅዱስን በመረዳት ደስታ ማግኘት ትችላለህ

መጽሐፍ ቅዱስን በመረዳት ደስታ ማግኘት ትችላለህ

መጽሐፍ ቅዱስን በመረዳት ደስታ ማግኘት ትችላለህ

መጽሐፍ ቅዱስ ከአምላክ የተገኙ ውድ እውነቶችን ይዟል። የሕይወት ዓላማ ምን እንደሆነ፣ የሰው ልጆች ለምን መከራ እንደሚደርስባቸውና ወደፊት ምን እንደሚጠብቃቸው ይነግረናል። ደስታ ማግኘት፣ ወዳጆች ማፍራት እንዲሁም ችግሮችን መፍታት የምንችለው እንዴት እንደሆነ ያስተምረናል። ከሁሉም በላይ ፈጣሪያችን ስለሆነው የሰማዩ አባታችን ይሖዋ መማር እንችላለን። እንዲህ ዓይነቱ እውቀት ደስታ የሚያስገኝልን ከመሆኑም በላይ ሕይወታችን ትርጉም ያለው እንዲሆን ያደርጋል።

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ አምላክ እውቀት መቅሰምን ምግብ ከመመገብ ጋር ያመሳስለዋል። ኢየሱስ “ሰው ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣው ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም” በማለት ተናግሯል። (ማቴዎስ 4:4፤ ዕብራውያን 5:12-14) በሕይወት ለመቀጠል በየዕለቱ ገንቢ ምግብ መመገብ እንደሚኖርብን ሁሉ አምላክ ቃል ከገባልን የዘላለም ሕይወት ተስፋ ተጠቃሚዎች ለመሆን ከፈለግን የአምላክን ቃል በየዕለቱ ማንበባችን አስፈላጊ ነው።

ምግብ መመገብ የሚያስደስተን አንድም በመመገብ ደስታ እንድናገኝ ተደርገን በመፈጠራችን ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ መሠረታዊ ፍላጎታችንን የሚያረካ በመሆኑ ነው። ይሁንና ደስተኞች መሆን ከፈለግን ልናሟላው የሚገባን ሌላም መሠረታዊ ፍላጎት አለን። ኢየሱስ “በመንፈስ ድኾች የሆኑ [“ለመንፈሳዊ ፍላጎታቸው ንቁ የሆኑ፣” NW] ብፁዓን ናቸው” ብሏል። (ማቴዎስ 5:3) የአምላክን ቃል መረዳታችን መንፈሳዊ ፍላጎታችንን ስለሚያሟላልን ደስተኞች መሆን እንችላለን።

አንዳንድ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን መረዳት አስቸጋሪ እንደሚሆንባቸው እሙን ነው። ለአብነት ያህል፣ እንግዳ ስለሆኑ ልማዶች አሊያም ምሳሌያዊ አነጋገሮች የሚገልጹ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶችን ትርጉም ለመረዳት እገዛ ያስፈልግህ ይሆናል። ከዚህ በተጨማሪ ከጉዳዩ ጋር ተዛማጅነት ያላቸውን ተጨማሪ ጥቅሶች እስካላነበብን ድረስ ለመረዳት የሚያዳግቱ ምሳሌያዊ ትንቢቶችም አሉ። (ዳንኤል 7:1-7፤ ራእይ 13:1, 2) ያም ሆኖ መጽሐፍ ቅዱስን በሚገባ መረዳት ትችላለህ። መጽሐፍ ቅዱስን መረዳት እንደሚቻል እንዴት እርግጠኛ መሆን ትችላለህ?

ሁሉም ሰው ሊያገኘው የሚችለው ደስታ

መጽሐፍ ቅዱስ የአምላክ ቃል ነው። አምላክ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ለእኛ ያለውን ፈቃድ አስፍሮልናል። አምላክ ለመረዳት የሚያዳግት አሊያም ለሊቃውንት ብቻ ግልጽ ሊሆን የሚችል መጽሐፍ ይሰጠናል? በጭራሽ፣ ይሖዋ ደግ አምላክ በመሆኑ እንዲህ አያደርግም። ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሚከተለው ብሏል:- “ከእናንተ መካከል አባት ሆኖ ሳለ ልጁ ዓሣ ቢለምነው እባብ የሚሰጠው ይኖራልን? ወይስ ዕንቊላል ቢለምነው ጊንጥ ይሰጠዋልን? እናንተ ክፉዎች ሆናችሁ ሳላችሁ፣ ለልጆቻችሁ መልካም ስጦታን መስጠት ካወቃችሁበት፣ የሰማዩ አባታችሁ ታዲያ ለሚለምኑት መንፈስ ቅዱስን እንዴት አብልጦ አይሰጥ!” (ሉቃስ 11:11-13) በመሆኑም መጽሐፍ ቅዱስን መረዳት አስቸጋሪ እንደማይሆንብህና አምላክም ቢሆን አጥብቀህ ከጠየቅኸው ቃሉን መረዳት እንድትችል እገዛ እንደሚያደርግልህ ልትተማመን ትችላለህ። የሚገርመው ልጆች እንኳን ሳይቀሩ የመጽሐፍ ቅዱስን መሠረታዊ ትምህርቶች መረዳት ይችላሉ!—2 ጢሞቴዎስ 3:15

መጽሐፍ ቅዱስን መረዳት ጥረት ይጠይቃል፤ ሆኖም እንዲህ ማድረጋችን በእጅጉ ያበረታታናል። ኢየሱስ ከሞት ከተነሳ በኋላ ከደቀ መዛሙርቱ ለሁለቱ ተገለጠላቸውና ስለ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትንቢቶች ይነግራቸው ጀመር። የሉቃስ ዘገባ እንዲህ ይላል:- “ከሙሴና ከነቢያት ሁሉ ጀምሮ በቅዱሳት መጻሕፍት ስለ እርሱ የተጻፈውን አስረዳቸው።” ውጤቱስ ምን ነበር? እነዚህ ደቀ መዛሙርት በዚሁ ዕለት ምሽት፣ ኢየሱስ በነገራቸው ነገር ላይ ሲያሰላስሉ “በመንገድ ሳለን፣ እያነጋገረን ቅዱሳት መጻሕፍትንም ገልጦ ሲያስረዳን፣ ልባችን እንደ እሳት ይቃጠልብን አልነበረምን?” ተባባሉ። (ሉቃስ 24:13-32) የአምላክን ቃል መረዳታቸው እምነታቸው እንዲጠነክርና ስለ ወደፊቱ ጊዜ ብሩህ አመለካከት እንዲይዙ ስለረዳቸው ተደስተዋል።

የአምላክን ቃል መረዳት ከባድ ሸክም ከመሆን ይልቅ ማራኪና ጠቃሚ እንዲሁም ግሩም ምግብ የመመገብን ያህል አስደሳች ነው። የአምላክን ቃል ለመረዳት ምን ማድረግ ይኖርብሃል? የሚቀጥለው ርዕስ ‘አምላክን ማወቅ’ እንዴት ደስታ ሊያስገኝልህ እንደሚችል ያብራራል።—ምሳሌ 2:1-5

[በገጽ 4 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ይሖዋ ልክ እንደ አንድ አፍቃሪ አባት፣ መጽሐፍ ቅዱስን ለመረዳት እንድንችል መንፈስ ቅዱስን ይሰጠናል