በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የአንባቢያን ጥያቄዎች

የአንባቢያን ጥያቄዎች

የአንባቢያን ጥያቄዎች

በዘፀአት 23:19 ላይ ከሚገኘው “ጠቦት ፍየልን በእናቱ ወተት አትቀቅል” ከሚለው ሕግ ምን ትምህርት ማግኘት እንችላለን?

መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሦስት ጊዜ ተጽፎ የሚገኘውና የሙሴ ሕግ ክፍል የሆነው ይህ ትእዛዝ ይሖዋ ትክክለኛ ለሆነው ነገር ያለውን አመለካከት፣ አዛኝነቱንና ርኅራኄውን እንድናስተውል ይረዳናል። እንዲሁም ለሐሰት ሃይማኖት ያለውን ጥላቻ ጎላ አድርጎ ያሳያል።—ዘፀአት 34:26፤ ዘዳግም 14:21

ጠቦት ፍየልን ወይም ሌላ እንስሳን በእናቱ ወተት መቀቀል ይሖዋ በተፈጥሮ ካደረገው ዝግጅት ጋር የሚጋጭ ነው። አምላክ የእናት ጡት ወተትን ያዘጋጀው ግልገሉ እየተመገበው እንዲያድግበት ነው። አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁር እንደተናገሩት ግልገልን በእናቱ ወተት መቀቀል “አምላክ በወላጆችና በልጆች መካከል ለፈጠረውና ለቀደሰው ዝምድና ንቀት” ማሳየት ነው።

በተጨማሪም ጠቦትን በእናቱ ወተት መቀቀል፣ ዝናብ እንዲዘንብ ለመለማመን የሚከናወን አረማዊ የአምልኮ ሥርዓት ሊሆን እንደሚችል አንዳንዶች ይገምታሉ። ይህ እውነት ከሆነ፣ እገዳው እስራኤላውያንን በዙሪያቸው የነበሩ አሕዛብ ከሚፈጽሟቸው ፍሬ ቢስና ጭካኔ የሞላባቸው ሃይማኖታዊ ልማዶች ጠብቋቸዋል። እስራኤላውያን የእነዚህን ብሔራት ልማድ እንዳይከተሉ የሙሴ ሕግ በግልጽ ያዝዛል።—ዘሌዋውያን 20:23

በመጨረሻም፣ ይህ ሕግ ስለ ይሖዋ ርኅራኄ ትምህርት ይሰጠናል። ሕጉ በእንስሳት ላይ ጭካኔ መፈጸምንና ተፈጥሮን የሚጻረሩ ነገሮች ማድረግን የሚከለክሉ በዘፀአት 23:19 ላይ ካለው ጋር የሚመሳሰሉ በርካታ ደንቦች ይዟል። ለምሳሌ ያህል፣ አንድ እንስሳ ከእናቱ ጋር ቢያንስ ለሰባት ቀን ካልቆየ መሥዋዕት መሆን እንደሌለበት፣ አንዲት እንሰሳንና ልጅዋን በአንድ ቀን መሠዋት እንደማይገባ እንዲሁም ወፍንና እንቁላሎቿን ወይም ልጆቿን ከጎጆዋቸው አብሮ መውሰድ ተገቢ እንዳልሆነ ሕጉ ያዝዛል።—ዘሌዋውያን 22:27, 28፤ ዘዳግም 22:6, 7

ሕጉ የያዘው ውስብስብ የሆኑ ትእዛዞችና እገዳዎች ብቻ እንዳልሆነ ከዚህ በግልጽ ማየት ይቻላል። የሙሴ ሕግ በርካታ ጥቅሞች ያስገኝልናል፤ ከእነዚህም አንዱ ሕጉ የያዛቸው መሠረታዊ ሥርዓቶች የይሖዋን ግሩም ባሕርያት በሚገባ የሚያንጸባርቅ ላቅ ያለ የሥነ ምግባር አቋም እንዲኖረን ማስቻሉ ነው።—መዝሙር 19:7-11

[በገጽ 31 ላይ የሚገኝ የሥዕል ምንጭ]

© Timothy O’Keefe/Index Stock Imagery