በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

መጠሪያ ስም የማግኘት መብት

መጠሪያ ስም የማግኘት መብት

መጠሪያ ስም የማግኘት መብት

ሁሉም ሰው መጠሪያ ስም የማግኘት መብት አለው። በታሂቲ፣ አባትና እናቱ ለማይታወቁ ሕፃን እንኳ ስም ይወጣለታል። ማዘጋጃ ቤቱ፣ ተጥሎ ለተገኘው ሕፃን የአባት ስም ጭምር ይሰጠዋል።

ሆኖም ሁሉም የሰው ልጆች ያላቸውን ይህን መሠረታዊ መብት የተነፈገ አንድ አካል አለ። የሚገርመው ደግሞ “በሰማይና በምድር ያለ ቤተሰብ ሁሉ ስያሜ” ያገኘው ከዚህ አካል ነው! (ኤፌሶን 3:14, 15) በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የፈጣሪ ስም ቢኖርም እንኳ ብዙ ሰዎች በስሙ ለመጠቀም አሻፈረኝ ብለዋል። እንዲያውም ስሙን “አምላክ”፣ “ጌታ” ወይም “ዘላለማዊ” እንደሚሉት ባሉ የማዕረግ ስሞች ለመተካት መርጠዋል። ታዲያ ፈጣሪያችን ስሙ ማነው? መዝሙራዊው እንዲህ በማለት መልሱን ይሰጠናል:- “ስምህ እግዚአብሔር [“ይሖዋ፣” NW] የሆነው አንተ ብቻ፣ በምድር ሁሉ ላይ ልዑል እንደ ሆንህ ይወቁ።”—መዝሙር 83:18፤ ዘፀአት 6:3 የ1879 ትርጉም

በ19ኛው መቶ ዘመን መጀመሪያ አካባቢ የለንደን ሚስዮናውያን ማኅበር አባላት ወደ ታሂቲ በሄዱ ጊዜ የፖሊኔዥያ ሰዎች የተለያዩ አማልክትን ያመልኩ ነበር። እያንዳንዱ አምላክ የራሱ የሆነ ልዩ ስም ሲኖረው ዋናዎቹ አማልክት ኦሮ እና ታአሮአ ተብለው ይጠራሉ። እነዚህ ሚስዮናውያን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጠቀሰውን አምላክ ከሌሎቹ አማልክት ለመለየት መለኮታዊውን ስም በታሂቲ ቋንቋ ዬሆቫ ብለው በመተርጎም ስሙን በስፋት ተጠቅመውበታል።

ይህ ስም በስፋት የታወቀ ሲሆን በዕለት ተዕለት ንግግርም ሆነ በጽሑፎች ላይ በሰፊው ይሠራበት ጀመር። በ19ኛው መቶ ዘመን መጀመሪያ ላይ የታሂቲ ንጉሥ የነበሩት ፖማሪ ዳግማዊ በየዕለቱ በሚጽፉት ደብዳቤ ላይ የአምላክን የግል ስም በተደጋጋሚ ይጠቀሙበት ነበር። በሥዕሉ ላይ የሚታየው ደብዳቤ ለዚህ ማረጋገጫ ይሆነናል። ይህ በእንግሊዝኛ የተጻፈ ደብዳቤ ሙዚየም ኦቭ ታሂቲ ኤንድ ኢትስ አይላንድስ በሚባለው ሙዚየም ውስጥ ይገኛል። ይህ ደግሞ በዚያን ጊዜ የነበሩ ሰዎች መለኮታዊውን ስም ይጠቀሙበት እንደነበር ያረጋግጣል። ከዚህም በተጨማሪ በ1835 ተተርጉሞ በተጠናቀቀው የመጀመሪያው የታሂቲ የመጽሐፍ ቅዱስ እትም ውስጥ የአምላክ የግል ስም በሺህ ለሚቆጠሩ ጊዜያት ተጠቅሶ ይገኛል።

[በገጽ 32 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ንጉሥ ፖማሪ ዳግማዊ

[በገጽ 32 ላይ የሚገኝ የሥዕል ምንጭ]

ንጉሥ እና ደብዳቤ:- Collection du Musée de Tahiti et de ses Îles, Punaauia, Tahiti