በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የአንባቢያን ጥያቄዎች

የአንባቢያን ጥያቄዎች

የአንባቢያን ጥያቄዎች

‘የሕዝቦች ሀብት ሁሉ’ የተባሉት ወደ ይሖዋ እውነተኛ የአምልኮ “ቤት” እንዲመጡ ያደረጋቸው ምንድን ነው?—ሐጌ 2:7

ይሖዋ በነቢዩ ሐጌ አማካኝነት “ሕዝቦችን ሁሉ አናውጣለሁ፤ የሕዝቦችም ሀብት ሁሉ ወደዚህ ይመጣል፤ ይህንም ቤት በክብር እሞላዋለሁ” የሚል ትንቢት አስነግሯል። (ሐጌ 2:7) ‘የሕዝቦች ሀብት ሁሉ’ የተባሉት ልበ ቅን ሰዎች ወደ እውነተኛው አምልኮ እንዲመጡ የሚያደርጋቸው ‘የሕዝቦች መናወጥ’ ነው? አይደለም።

ሕዝቦችን የሚያናውጣቸው ምን እንደሆነና ይህ መናወጥ ምን እንደሚያስከትል ተመልከት። መጽሐፍ ቅዱስ “ሕዝቦች ለምን ያሤራሉ? ሰዎችስ ለምን ከንቱ ነገር ያውጠነጥናሉ?” ሲል ይጠይቃል። (መዝሙር 2:1) ሕዝቦች ‘የሚያውጠነጥኑት’ ወይም የሚያሰላስሉት “ከንቱ ነገር” ስለ ሉዓላዊነታቸው መራዘም ነው። ለሥልጣናቸው የሚያሰጋ ነገር እንዳለ ከማወቅ የበለጠ የሚያናውጣቸው ነገር የለም።

የይሖዋ ምሥክሮች ስለተቋቋመችው የአምላክ መንግሥት በመላው ዓለም መስበካቸው ሕዝቦችን ስጋት ላይ ጥሏቸዋል። ደግሞም በኢየሱስ ክርስቶስ የሚተዳደረው የአምላክ መሲሐዊ መንግሥት ሰብዓዊ “መንግሥታት[ን] ሁሉ ያደቃል፤ እስከ መጨረሻውም ያጠፋቸዋል።” (ዳንኤል 2:44) የፍርድ መልእክት ማወጅን የሚያካትተው የስብከቱ ሥራችን ሕዝቦችን ያናውጣቸዋል። (ኢሳይያስ 61:2) የሚታወጀው መልእክት ኃይለኛ እየሆነና በብዙ ቦታዎች እየተዳረሰ ሲሄድ ነውጡም የዚያኑ ያህል ይጨምራል። ታዲያ በሐጌ 2:7 ላይ ትንቢት የተነገረለት ነውጥ የምን ነገር መቅድም ነው?

በሐጌ 2:6 ላይ እንዲህ እናነባለን:- “ሁሉን የሚገዛ እግዚአብሔር ጸባኦት እንዲህ ይላል፤ ‘በቅርብ ጊዜ እንደ ገና ሰማያትንና ምድርን፣ ባሕሩንና የብሱን አንድ ጊዜ አናውጣለሁ።’” ሐዋርያው ጳውሎስ ይህን ጥቅስ በመጥቀስ እንደሚከተለው ሲል ጽፏል:- “‘ምድርን ብቻ ሳይሆን፣ ሰማያትንም አንድ ጊዜ ደግሜ አናውጣለሁ’ ብሎ ቃል ገብቶአል። አንድ ጊዜ ‘ደግሜ’ የሚለው ቃል የሚያመለክተው የማይናወጡት ጸንተው ይኖሩ ዘንድ፣ የሚናወጡት ይኸውም የተፈጠሩት የሚወገዱ መሆናቸውን ነው።” (ዕብራውያን 12:26, 27) አዎን፣ ይህ ሥርዓት አምላክ ላዘጋጀው አዲስ ዓለም ቦታውን በመልቀቅ ተጠራርጎ ይጠፋል።

ልበ ቅን ሰዎች ወደ እውነተኛው አምልኮ የሚሳቡት ሕዝቦች ስለሚናወጡ አይደለም። እነዚህ ሰዎች ወደ ይሖዋና ወደ አምልኮቱ እንዲሳቡ የሚያደርጋቸው ሕዝቦችን እያናወጣቸው ያለውና የተቋቋመውን የአምላክ መንግሥት አስመልክቶ በመላው ዓለም የሚሰጠው ምሥክርነት ነው። “የዘላለም ወንጌል” መታወጅ ለሕይወት የተዘጋጁ ሰዎች ወደ ይሖዋ አምልኮ እንዲመጡ ያነሳሳቸዋል።—ራእይ 14:6, 7

የመንግሥቱ ወንጌል የፍርድና የመዳን መልእክት ይዟል። (ኢሳይያስ 61:1, 2) በመላው ዓለም የሚታወጀው ይህ መልእክት ሁለት ገጽታዎች አሉት:- ሕዝቦችን ያናውጣል እንዲሁም የሕዝቦች ሀብት ሁሉ የተባሉት ለይሖዋ ክብር የሚያመጡ ሰዎች እንዲሰበሰቡ ያደርጋል።