በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ሃይማኖት ምን ጥቅም አለው?

ሃይማኖት ምን ጥቅም አለው?

ሃይማኖት ምን ጥቅም አለው?

“ሃይማኖት ሳይኖረኝ ጥሩ ሰው መሆን እችላለሁ!” ብዙ ሰዎች እንደዚህ ይሰማቸዋል። ሐቀኛና ርኅሩኅ የሆኑ እንዲሁም ኃላፊነት የሚሰማቸው ብዙ ሰዎች ለሃይማኖት ግድ የላቸውም። ለምሳሌ ያህል፣ በምዕራብ አውሮፓ የሚኖሩ አብዛኞቹ ሰዎች በአምላክ እንደሚያምኑ ቢናገሩም አዘውትረው ወደ ቤተ ክርስቲያን የሚሄዱት ጥቂቶች ናቸው። a በላቲን አሜሪካ እንኳ ከካቶሊኮች መካከል ቤተ ክርስቲያን የሚያዘወትሩት ከ15 እስከ 20 በመቶ የሚሆኑት ብቻ ናቸው።

ምናልባት አንተም እንደ አብዛኞቹ ሰዎች፣ ሃይማኖት አንድን ሰው የተሻለ ሕይወት እንዲመራ እንደማይረዳው ይሰማህ ይሆናል። ይሁንና ከብዙ አሥርተ ዓመታት በፊት ማለትም በአያቶችህ ዘመን የነበሩት አብዛኞቹ ሰዎች በዚህ ዘመን ካሉት ሰዎች ይበልጥ ሃይማኖተኞች እንደነበሩ ታውቅ ይሆናል። ታዲያ ሃይማኖት የነበረውን ሰፊ ተቀባይነት ያጣው እንዴት ነው? አንድ ሰው ሃይማኖተኛ ሳይሆን ጥሩ ሰው ሊሆን ይችላል? አንተን ሊጠቅምህ የሚችል ሃይማኖት ይኖር ይሆን?

ብዙዎች ለሃይማኖት ጀርባቸውን የሰጡት ለምንድን ነው?

በመቶዎች ለሚቆጠሩ ዘመናት አብዛኞቹ የሕዝበ ክርስትና አማኞች አምላክ ከአምላኪዎቹ ታዛዥነትን እንደሚጠብቅ ያምኑ ነበር። ስለዚህ የሃይማኖት መሪዎች የሚያከናውኑትን ሃይማኖታዊ ሥርዓትም ሆነ ሰባኪዎች የሚሰጡትን መመሪያ በመከተል የአምላክን ሞገስ ለማግኘት ሲሉ ወደ ቤተ ክርስቲያን ይሄዱ ነበር። እርግጥ ነው፣ አብዛኞቹ ሰዎች በሃይማኖት ውስጥ ያለውን ግብዝነት ይገነዘባሉ። ሃይማኖት በጦርነት ውስጥ የሚጫወተው ሚና እንዲሁም የአንዳንዶቹ ቀሳውስት ብልሹ ምግባር በደንብ ይታወቃል። ቢሆንም አብዛኞቹ ሰዎች ሃይማኖት በራሱ ጥሩ ነገር እንደሆነ ያምኑ ነበር። ሌሎችን ደግሞ የሚማርካቸው በሃይማኖት ውስጥ ያለው ምስጢራዊ ሁኔታ፣ ባሕሉና ሙዚቃው ነው። እንዲያውም አንዳንዶችን ሃይማኖተኛ እንዲሆኑ የሚገፋፋቸው በሲኦል ለዘላለም ስለመቃጠል የሚገልጸው ትምህርት ነው፤ እንዲህ ያለው ሐሳብ ግን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አይገኝም። እያደር ብዙ ሰዎች ለሃይማኖት ያላቸውን አመለካከት እንዲለውጡ የሚያደርጉ የተለያዩ ሁኔታዎች ብቅ አሉ።

ከእነዚህ ሁኔታዎች አንዱ የዝግመተ ለውጥ ንድፈ ሐሳብ መዛመት ነው። አንዳንድ ሰዎች ሕይወት የተገኘው አምላክ ፈጥሮት ሳይሆን በአጋጣሚ እንደሆነ አመኑ። አብዛኞቹ ሃይማኖቶች ደግሞ አምላክ የሕይወት ምንጭ እንደሆነ የሚያሳምን ማስረጃ ማቅረብ አቃታቸው። (መዝሙር 36:9) በተጨማሪም ቴክኖሎጂ እያደገ ሲሄድ በሕክምና፣ በመጓጓዣና በመገናኛ መስኮች የተገኙት ከፍተኛ ውጤቶች በሰዎች አእምሮ ውስጥ ማንኛውም ችግር በሳይንስ ሊፈታ ይችላል የሚል ስሜት አሳደሩ። ከዚህም ሌላ ከአብያተ ክርስቲያናት ይልቅ ስለ ማኅበራዊ ሕይወት የሚያጠኑ ሊቃውንትና የሥነ ልቦና ምሁራን የተሻለ አመራር ይሰጣሉ የሚል አስተሳሰብ መጣ። ሃይማኖቶችም በፊናቸው የአምላክን ሕግ ተግባራዊ እያደረጉ መኖር የተሻለ ሕይወት እንደሚያስገኝ በግልጽ ማሳየት አልቻሉም።—ያዕቆብ 1:25

የሰዎች አመለካከት በመቀየሩ ብዙ ሃይማኖቶች የሚሰብኩትን መልእክት ለወጡ። ቀሳውስትና ሰባኪዎች አምላክ ከአምላኪዎቹ ታዛዥነትን እንደሚጠብቅ ማስተማራቸውን አቆሙ። በምትኩ ብዙዎች፣ እያንዳንዱ ግለሰብ ትክክልና ስህተት የሆነውን ራሱ መወሰን እንዳለበት አስተማሩ። አንዳንዶቹ የሃይማኖት መሪዎች ተወዳጅነት ለማግኘት ሲሉ ሰዎች እንደፈለጉት ቢኖሩም አምላክ እንደሚቀበላቸው መናገር ጀመሩ። እንዲህ ያለው ትምህርት መጽሐፍ ቅዱስ “ሰዎች ትክክለኛ የሆነውን ትምህርት የማይቀበሉበት ጊዜ ይመጣል፤ ከዚህ ይልቅ ለገዛ ምኞቶቻቸው የሚስማማውን፣ የሚያሳክክ ጆሮአቸው ሊሰማ የሚፈልገውን እንዲነግሯቸው በዙሪያቸው ብዙ አስተማሪዎችን ይሰበስባሉ” በማለት አስቀድሞ የተናገረውን ትንቢት ያስታውሰናል።—2 ጢሞቴዎስ 4:3

እንዲህ ዓይነቱ ትምህርት ሰዎችን በመሳብ ፈንታ ይብሱን ከሃይማኖት እንዲርቁ አደረጋቸው። ‘አብያተ ክርስቲያናት አምላክ ለመፍጠር የሚያስችል ኃይልና ሕግ ለማውጣት የሚያስችል ጥበብ ያለው መሆኑን የሚጠራጠሩ ከሆነ ወደ ቤተ ክርስቲያን መሄዴ ምን ይጠቅመኛል? ስለ ሃይማኖት ለልጆቼ ለማስተማርስ ጥረት የማደርገው ለምንድን ነው?’ ብለው ወደ ማሰብ መራቸው። በጨዋነት ለመኖር የሚጥሩ ሰዎች ሃይማኖት እርባና ቢስ እንደሆነ ማሰብ ጀመሩ። ወደ አብያተ ክርስቲያናት መሄዳቸውን ያቆሙ ሲሆን ሃይማኖት ለእነሱ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ነገር መሆኑም አከተመ። ጠቃሚ መሆን የነበረበትን ነገር እርባና ቢስ እንዲሆን ያደረገው ምንድን ነው? ለዚህ ጥያቄ መጽሐፍ ቅዱስ አሳማኝ ማብራሪያ ይሰጣል።

ሃይማኖት የክፋት ዓላማን ለማሳካት አገለገለ

ሐዋርያው ጳውሎስ የጥንት ክርስቲያኖችን ሲያስጠነቅቅ አንዳንድ ሰዎች ክርስትናን የክፋት ዓላማቸውን ለማሳካት እንደሚጠቀሙበት ገልጿል። እንዲህ ብሎ ነበር:- “ነጣቂ ተኵላዎች መጥተው በመካከላችሁ ሰርገው እንደሚገቡና ለመንጋውም እንደማይራሩ ዐውቃለሁ። ከእናንተው መካከል እንኳ የራሳቸውን ደቀ መዛሙርት ለማፍራት እውነትን የሚያጣምሙ ይነሣሉ።” (የሐዋርያት ሥራ 20:29, 30) ‘እውነትን ካጣመሙት’ ሰዎች መካከል የሮም ካቶሊክ ሃይማኖታዊ ምሁር የሆነው አውጉስቲን ይገኝበታል። ኢየሱስ፣ ደቀ መዛሙርቱ በቅዱሳን ጽሑፎች ተጠቅመው ሰዎችን እንዲያሳምኑ አስተምሮ ነበር። አውጉስቲን ግን በሉቃስ 14:23 ላይ ያሉትን “በግድ አምጥተህ አስገባ” የሚሉትን የኢየሱስ ቃላት በማጣመም፣ ሰዎችን ወደ ክርስትና ለመለወጥ በኃይል መጠቀም ተገቢ እንደሆነ አስተማረ። (ማቴዎስ 28:19, 20፤ የሐዋርያት ሥራ 28:23, 24) አውጉስቲን ሰዎችን ለመቆጣጠር በሃይማኖት ተጠቅሟል።

ከበስተ ጀርባ ሆኖ ሃይማኖት አላግባብ መጠቀሚያ እንዲሆንና እንዲበከል ያደረገው ዓመጸኛው መልአክ ሰይጣን ነው። ሰይጣን በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበሩትን የሃይማኖት ሰዎች የክርስቲያን ጉባኤን እንዲበክሉ አነሳስቷቸዋል። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ስላሉት ሰዎች ሲናገር እንዲህ ይላል:- “እንደነዚህ ያሉ ሰዎች የክርስቶስን ሐዋርያት ለመምሰል ራሳቸውን የሚለዋውጡ፣ ሐሰተኞች ሐዋርያትና አታላዮች ሠራተኞች ናቸው። ይህም የሚያስደንቅ ነገር አይደለም፤ ምክንያቱም ሰይጣን ራሱ የብርሃን መልአክ ለመምሰል ራሱን ይለዋውጣል። እንግዲህ የእርሱ አገልጋዮች፣ የጽድቅ አገልጋዮች ለመምሰል ራሳቸውን ቢለውጡ የሚያስገርም አይደለም።”—2 ቆሮንቶስ 11:13-15

ሰይጣን፣ ሰዎች በአምላክ መሥፈርቶች መመራታቸውን ትተው በእርሱ መሥፈርት እንዲመሩ ሲል ክርስቲያን እንደሆኑ፣ ጥሩ ሥነ ምግባር እንደሚከተሉና እውቀት እንደሚሰጡ በሚያስመስሉ ሃይማኖቶች አሁንም ይጠቀማል። (ሉቃስ 4:5-7) ምናልባት አንተም በዛሬው ጊዜ ያሉ ብዙ ቀሳውስት በማዕረግ ስሞች ራሳቸውን ከፍ ከፍ ለማድረግና ከምእመናኖቻቸው ገንዘብ ለማግኘት በሃይማኖት እንደሚጠቀሙ ሳታስተውል አትቀርም። በተጨማሪም መንግሥታት ዜጎቻቸው ለጦርነት ራሳቸውን እንዲያቀርቡ ለማሳመን በሃይማኖት ተጠቅመዋል።

ዲያብሎስ አብዛኞቹ ሰዎች ከሚያስቡት በላይ ሃይማኖትን በሰፊው ይጠቀምበታል። የሰይጣንን ዓላማ እየፈጸሙ ያሉት ጥቂት ሃይማኖታዊ አክራሪዎች ብቻ እንደሆኑ ይሰማህ ይሆናል። መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው ግን ‘ዲያብሎስ ወይም ሰይጣን ዓለምን ሁሉ እያሳተ ነው።’ በተጨማሪም መጽሐፍ ቅዱስ “መላው ዓለምም በክፉው ሥር እንደ ሆነ” ይናገራል። (ራእይ 12:9፤ 1 ዮሐንስ 5:19) ሰዎችን የራሳቸው ተከታይ የማድረግ ፍላጎት ያላቸው ሃይማኖታዊና ፖለቲካዊ መሪዎች መጠቀሚያ ስላደረጓቸው ሃይማኖቶች አምላክ ምን ይሰማዋል?

“ምን ይጠቅመኛል?”

የአንዳንዶቹ የሕዝበ ክርስትና አብያተ ክርስቲያናት ምግባር ያበሳጭህ ይሆናል፤ ሁሉን ቻይ የሆነው አምላክም በእነዚህ ሃይማኖቶች በጣም ያዝናል። ሕዝበ ክርስትና ከአምላክ ጋር ቃል ኪዳን እንደገባች ትናገራለች፤ የጥንቷ እስራኤልም ይህንኑ ትናገር ነበር። ሆኖም ሁለቱም ታማኞች እንዳልሆኑ አረጋግጠዋል። በዚህም ምክንያት ይሖዋ በእስራኤል ላይ የተናገረው የውግዘት ቃል በዛሬው ጊዜ ባለችው ሕዝበ ክርስትና ላይም በእኩል ደረጃ ይሠራል። ይሖዋ እንዲህ ብሎ ነበር:- ‘ቃሌን አላዳመጡም፣ ሕጌንም ንቀዋል። ዕጣን ከሳባ ምድር ቢመጣ ምን ይጠቅመኛል? መሥዋዕታችሁ ደስ አያሰኘኝም።’ (ኤርምያስ 6:19, 20) አምላክ ግብዞች የሚፈጽሙትን የአምልኮ ሥርዓት አይቀበልም። ሃይማኖታዊ ሥርዓታቸውም ሆነ ጸሎታቸው አያስደስተውም። እስራኤላውያንን እንዲህ ብሏቸዋል:- “የተደነገጉ በዓሎቻችሁን ነፍሴ ጠልታለች፤ ሸክም ሆነውብኛል፤ መታገሥም አልቻልሁም። እጆቻችሁን ለጸሎት ወደ እኔ ስትዘረጉ፣ ዐይኖቼን ከእናንተ እሰውራለሁ፤ አብዝታችሁ ብትጸልዩም እንኳ አልሰማችሁም።”—ኢሳይያስ 1:14, 15

ይሖዋ፣ ሥረ መሠረታቸው ለሐሰት አማልክት ክብር ለመስጠት የተቋቋሙ ሆነው ሳሉ ክርስቲያናዊ እንደሆኑ አድርገው አብያተ ክርስቲያናት ባቀረቧቸው በዓሎች ይደሰታል? የክርስቶስን ትምህርቶች አዛብተው የሚያስተምሩ ቀሳውስት የሚያቀርቧቸውን ጸሎቶችስ ይሰማል? አምላክ ሕጉን የሚንቅ ማንኛውንም ሃይማኖት ይቀበላል? አምላክ የጥንቷ እስራኤል ያቀረበችው መሥዋዕት “ምን ይጠቅመኛል?” እንዳለ ሁሉ በዛሬው ጊዜም ለሚፈጸሙት የቤተ ክርስቲያን ሥርዓቶች ተመሳሳይ ተቃውሞ እንደሚያሰማ እርግጠኛ ልትሆን ትችላለህ።

ሆኖም ይሖዋ ቅን ሰዎች በእውነት የሚያቀርቡለትን አምልኮ በአድናቆት ይመለከታል። ግለሰቦች ከእሱ ላገኙት ነገር ሁሉ አድናቆታቸውን ሲገልጹ ይደሰታል። (ሚልክያስ 3:16, 17) ታዲያ አምላክን የማታመልክ ብትሆንም ጥሩ ሰው ልትሆን ትችላለህ? አፍቃሪ ለሆኑ ወላጆቹ ምንም ነገር አድርጎ የማያውቅ ሰው ራሱን ጥሩ ሰው እንደሆነ አድርጎ ቢቆጥር ተገቢ ይሆናል? አምላክን ለማገልገል ምንም የማያደርግ ግለሰብ ጥሩ ሰው ሊሆን ይችላል? በምክንያታዊነት ካሰብነው የሕይወት ምንጭ ስለሆነው እውነተኛ አምላክ በጥልቅ ልናስብ ይገባል። በሚቀጥለው ርዕሰ ትምህርት ላይ እውነተኛ አምልኮ ለአምላክ ክብር ከማምጣትም አልፎ እኛን እንዴት ሊጠቅመን እንደሚችል እንመረምራለን።

[የግርጌ ማስታወሻ]

a “የ1960ዎቹ ዓመታት . . . በብዙ አገሮች ሃይማኖታዊ ባሕል በአጠቃላይ መንኮታኮት መጀመሩን አመላክተዋል።”—በምዕራብ አውሮፓ የሕዝበ ክርስትና መዳከም፣ 1750-2000

[በገጽ 4 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

አብያተ ክርስቲያናት አምላክ ሁሉንም ነገር መፍጠሩን የሚያሳየውን ማስረጃ አቅርበዋል?

[በገጽ 5 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

የአምላክ ወኪል የሆነ ሰው እንዲህ ባለው ቦታ መገኘት ይኖርበታል?

[በገጽ 5 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

አምላክ እንዲህ ያለውን በዓል እንዴት ይመለከተዋል?

[ምንጭ]

AP Photo/Georgy Abdaladze