በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የአንባቢያን ጥያቄዎች

የአንባቢያን ጥያቄዎች

የአንባቢያን ጥያቄዎች

ሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉሞች ዘዳግም 31:2ን ሙሴ የእስራኤል መሪ ሆኖ ‘ሊወጣና ሊገባ እንደማይችል’ አድርገው ሲተረጉሙት የአዲስ ዓለም ትርጉም ግን ‘ከእንግዲህ ወዲህ እንድወጣና እንድገባ አልተፈቀደልኝም’ በማለት የተረጎመው ለምንድን ነው?

የዕብራይስጡ ቃል በሁለቱም መንገድ ሊተረጎም ቢችልም አንዳንድ የአማርኛ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉሞች ሙሴ በሕይወቱ መጨረሻ አካባቢ ስለደከመና አካላዊ ሁኔታው ስላልፈቀደለት ሕዝቡን የመምራት ኃላፊነቱን መወጣት እንዳልቻለ አድርገው ተርጉመውታል። ለምሳሌ፣ አዲሱ መደበኛ ትርጉም እንዲህ ብሎታል:- “እነሆ፤ መቶ ሃያ ዓመት ሆኖኛል፤ ከእንግዲህ ልወጣና ልገባ አልችልም።” የ1980 ትርጉም ደግሞ “እነሆ የእኔ ዕድሜ መቶ ሃያ ዓመት ስለሆነ ከእንግዲህ ወዲህ እናንተን መምራት አይቻለኝም” በማለት ተርጉሞታል።

ሆኖም ከዘዳግም 34:7 መመልከት እንደምንችለው ሙሴ በዕድሜ የገፋ ቢሆንም እንኳ እንደ ልቡ መንቀሳቀስ ይችል ነበር። ጥቅሱ እንዲህ ይላል:- “ሙሴ በሞተ ጊዜ ዕድሜው መቶ ሃያ ዓመት ነበር፤ ሆኖም ዐይኑ አልፈዘዘም፤ ጕልበቱም አልደከመም።” በመሆኑም ሙሴ ሕዝቡን ለመምራት የሚያስችል አካላዊ ብቃት ነበረው። ይሖዋ ግን ሙሴ ሥራውን እንዲቀጥል አልፈቀደለትም። ይህንንም መረዳት የምንችለው ሙሴ በዘዳግም 31:2 ላይ “እግዚአብሔርም ‘ዮርዳኖስን አትሻገርም’ ብሎኛል” ሲል አክሎ ከተናገራቸው ቃላት ነው። ይሖዋ እዚህ ላይ በመሪባ ውኃ አጠገብ ያሳለፈውን ውሳኔ በድጋሚ መናገሩ ሊሆን ይችላል።—ዘኍልቍ 20:9-12

ሙሴ ያሳለፈው ረጅምና አስደናቂ ሕይወት በሦስት ሊከፈል ይችላል። ለ40 ዓመታት በግብጽ የኖረ ሲሆን በዚያም “የግብፆችን ጥበብ ሁሉ ተማረ፤ በንግግሩና በተግባሩም ብርቱ ሆነ።” (የሐዋርያት ሥራ 7:20-22) ለቀጣዮቹ 40 ዓመታት ደግሞ በምድያም ምድር ኖረ። እዚያም የይሖዋን ሕዝቦች ለመምራት የሚያስችሉትን መንፈሳዊ ባሕርያት መኮትኮት ችሏል። በመጨረሻም ሙሴ ለ40 ዓመት እስራኤላውያንን መርቷል እንዲሁም አስተዳድሯል። አሁን ግን ይሖዋ ሕዝቡ የዮርዳኖስን ወንዝ አቋርጠው ወደ ተስፋይቱ ምድር እንዲገቡ የሚመራቸው ሙሴ ሳይሆን ኢያሱ እንደሆነ ተናገረ።—ዘዳግም 31:3

በመሆኑም የአዲስ ዓለም ትርጉም በዘዳግም 31:2 ላይ ትክክለኛውን ሐሳብ አስቀምጧል። ሙሴ ከዚያ በኋላ የእስራኤል መሪ ሆኖ መቀጠል ያልቻለው አካሉ ስለደከመ ሳይሆን ይሖዋ እንደዚያ እንዲያደርግ ስላልፈቀደለት ነው።