በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ውብ በሆነችው ምድር ላይ በደስታ መኖር

ውብ በሆነችው ምድር ላይ በደስታ መኖር

ውብ በሆነችው ምድር ላይ በደስታ መኖር

የሥነ ፈለክ ተመራማሪዎች የሰው ልጆች መኖሪያ የሆነችው ምድር፣ በጣም ሰፊ በሆነው አጽናፈ ዓለም ውስጥ ትንሽ ቅንጣት ሆና እንደምትታይ ተናግረዋል። በግኡዙ አጽናፈ ዓለም ውስጥ ሕይወት ከምድር በስተቀር በሌላ በየትም ቦታ ላይ አይገኝም። ለሕይወት አስፈላጊ የሆኑትን ነገሮች አሟልታ የያዘችው ፕላኔት ምድር ብቻ ናት።

በተጨማሪም በዚህች ውብ ምድር ላይ ተደስተን መኖር እንችላለን። ብርዳማ በሆነ ቀን ፀሐይ ስትወጣ እንዴት ደስ ይላል! ፀሐይ ስትወጣም ሆነ ስትጠልቅ ተመልክቶ የማይማረክ ማን አለ? እርግጥ ነው፣ ፀሐይ እኛ እንድንደሰት ከማድረግ የበለጠ ነገር ታከናውናለች። ሕልውናችን የተመካው በፀሐይ ላይ ነው።

የፀሐይ የስበት ኃይል፣ በሚሊዮን ለሚቆጠሩ ዓመታት ምድርና ሌሎች ፕላኔቶች ምሕዋራቸውን ጠብቀው እንዲጓዙ አድርጓቸዋል። በተጨማሪም ተማሪዎች በትምህርት ቤት እንደሚማሩት፣ መላው ሥርዓተ ፀሐይ ፍኖተ ሐሊብ በሚባለው በእኛ ጋላክሲ እምብርት ዙሪያ ይሽከረከራል። ይሁንና ፀሐይ በእኛ ጋላክሲ ውስጥ ከሚሽከረከሩት ከ100 ቢሊዮን የሚበልጡ ከዋክብት መካከል አንዷ ብቻ ነች።

ፍኖተ ሐሊብ የሚባለው ጋላክሲ፣ እርስ በርሳቸው በስበት ኃይል የተያያዙ 35 የሚያህሉ ጋላክሲዎችን ባቀፈ ክላስተር (የጋላክሲዎች ስብስብ) ውስጥ ይገኛል። አንዳንዶቹ ትላልቅ ክላስተሮች በሺህ የሚቆጠሩ ጋላክሲዎችን ይይዛሉ። ያለንበት ሥርዓተ ፀሐይ ብዙ ጋላክሲዎች ባሉት ግዙፍ ክላስተር ውስጥ የሚገኝ ቢሆን ኖሮ ባለበት ቦታ የመርጋት አጋጣሚው የመነመነ ይሆን ነበር። ጊልዬርሞ ጎንዛሌዝ እና ጄይ ሪቻርድስ፣ ዘ ፕሪቭሌጅድ ፕላኔት በተሰኘው መጽሐፋቸው ላይ በአጽናፈ ዓለም ውስጥ “ለሕይወት ተስማሚ የሆኑት” ቦታዎች በጣም ጥቂት መሆናቸውን ገልጸዋል።

በዚህች ፕላኔት ላይ ሕይወት የተገኘው በአጋጣሚ ወይም ተከስቷል ተብሎ በሚታመነው “ታላቅ ፍንዳታ” ምክንያት ነው? ወይስ በዚህች ውብ ፕላኔት ላይ ሕይወት የተፈጠረው በዓላማ ነው?

ብዙ ሰዎች መኖሪያችን የሆነችው ምድር ለሕይወት ተስማሚ እንድትሆን ተደርጋ እንደተሠራች ያምናሉ። a ከብዙ መቶ ዓመታት በፊት የኖረ አንድ ዕብራዊ ገጣሚ ምድርንና ሰማይን አስመልክቶ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “የጣቶችህን ሥራ፣ ሰማያትህን ስመለከት፣ በስፍራቸው ያኖርሃቸውን፣ ጨረቃንና ከዋክብትን ሳይ፣ . . . ሰው ምንድን ነው?” (መዝሙር 8:3, 4) ገጣሚው ፈጣሪ አለ የሚል እምነት ነበረው። ይሁንና በሳይንስና በቴክኖሎጂ በተራቀቀው በዚህ ዘመን እንዲህ ብሎ ማመን ምክንያታዊ ነው?

[የግርጌ ማስታወሻዎች]

a የመዝሙር መጽሐፍን በተለይም መዝሙር 8ን ተመልከት።

[በገጽ 3 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

“ምድራችን ከሩቅ ስትታይ በጨለማ ውስጥ እንዳለ ሰማያዊ ዕንቁ ታበራለች።”—ዚ ኢለስትሬትድ ሳይንስ ኢንሳይክሎፒዲያ—አሜዚንግ ፕላኔት ኧርዝ

[ምንጭ]

ሉል:- U.S. Fish & Wildlife Service, Washington, D.C./NASA