በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የሐቀኝነት ምሳሌ

የሐቀኝነት ምሳሌ

የሐቀኝነት ምሳሌ

በብራዚል ክሩዜሮ ዶ ሱል በሚባል ከተማ በፀጉር ሥራ የምትተዳደረው ኔልማ በቅርቡ ክርስቲያናዊ የታማኝነት አቋሟን የሚፈትን ሁኔታ አጋጥሟት ነበር። የምትኖርበት አካባቢ በጎርፍ በተጥለቀለቀበት ወቅት ከአንዲት ደንበኛዋ የተወሰኑ ልብሶችን በእርዳታ አግኝታ ነበር። ልብሶቹን በመልክ በመልኩ እየለየች እያለ ከአንድ ሱሪ ኪስ ውስጥ ወደ 1,000 የአሜሪካ ዶላር የሚጠጋ ገንዘብ አገኘች።

ኔልማ ያገኘችው ይህ ገንዘብ የሰባት ወር ደሞዟን የሚያህል ሲሆን ገንዘቡ በወቅቱ በጣም ያስፈልጋት ነበር። ቤቷ በጎርፉ ጉዳት የደረሰበት ከመሆኑም በላይ አባቷ እንዲሁም ወንድሞቿና እህቶቿ በርካታ ንብረቶቻቸውን አጥተዋል። ይህ ገንዘብ ቤቷን ለማደስ ብቻ ሳይሆን ዘመዶቿንም ለመርዳት ይተርፍ ነበር። ይሁን እንጂ ኔልማ በመጽሐፍ ቅዱስ የሠለጠነው ሕሊናዋ ገንዘቡን ለራሷ አስቀርታ እንድትጠቀምበት አልፈቀደላትም።—ዕብራውያን 13:18 NW

በማግሥቱ ጠዋት ከሥራ መግቢያ ሰዓት ቀደም ብላ ወደምትሠራበት ቦታ በመሄድ ልብሶቹን የሰጠቻትን ነጋዴ አነጋገረቻት። ኔልማ ሴትየዋን ለሰጠቻት ልብሶች ካመሰገነቻት በኋላ ከልብሱ ውስጥ ያገኘችውን ነገር ግን መውሰድ እንደማትፈልግ ገለጸችላት። ሴትየዋ ገንዘቡን በማግኘቷ በጣም ተደሰተች፤ ገንዘቡ ለሠራተኞቿ ደሞዝ ለመክፈል ያስቀመጠችው ነበር። ነጋዴዋ ሴት “ሐቀኝነት በብዙ ሰዎች ላይ የሚታይ ባሕርይ አይደለም” በማለት ተናግራለች።

እርግጥ ነው፣ አንዳንዶች ሐቀኛ መሆን ልዩ አድናቆት ሊቸረው የሚገባ ባሕርይ እንደሆነ አይሰማቸው ይሆናል። ነገር ግን ሐቀኝነት እውነተኛውን አምላክ ይሖዋን ለማስደሰት ጥረት በሚያደርጉ ሰዎች ዘንድ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ባሕርይ ነው። (ኤፌሶን 4:25, 28) ኔልማ “ከዚህ የተለየ ነገር ባደርግ ኖሮ ሌሊት እንቅልፍ አይወስደኝም ነበር” ብላለች።