በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

በጭካኔ የተሞላ ዓለም

በጭካኔ የተሞላ ዓለም

በጭካኔ የተሞላ ዓለም

ማሪያ ስልሳ አራት ዓመታቸው ሲሆን የሚኖሩትም ብቻቸውን ነበር። አንድ ቀን በገዛ ቤታቸው ውስጥ ተደብድበውና በሽቦ ታንቀው ተገኙ።

በቁጣ የገነፈሉ ሰዎች፣ ሁለት ልጆች አፍናችሁ ወስዳችኋል በማለት ሦስት ፖሊሶችን ደበደቡ። ከዚያም በሁለቱ ፖሊሶች ላይ ጋዝ አርከፍክፈው እሳት ለኮሱባቸው። ሦስተኛው ፖሊስ ለማምለጥ የቻለ ቢሆንም ሁለቱን ግን እሳቱ በላቸው።

ማንነቱን ያልገለጸ አንድ ሰው በስልክ የሰጠው ጥቆማ አንድ አሰቃቂ ነገር እንዲጋለጥ ምክንያት ሆነ። ለመዝናናት ወደ አካባቢው የመጡ አራት ሰዎች አስከሬናቸው ከአንድ የአትክልት ስፍራ ተቆፍሮ ወጣ። ሰዎቹ ዓይናቸው ተሸፍኗል እንዲሁም እጆቻቸው ታስረዋል። የአስከሬን ምርመራ ውጤት እንዳሳየው ሰዎቹ የተቀበሩት ከነሕይወታቸው ነበር።

እነዚህ አረመኔያዊ ድርጊቶች አስፈሪ ከሆኑ የዓመጽ ፊልሞች ላይ የተቀነጨቡ አይደሉም። ከዚህ ይልቅ በአንድ የላቲን አሜሪካ አገር በቅርቡ ርዕሰ ዜና የነበሩ እውነተኛ ታሪኮች ናቸው። ይሁንና እነዚህን የመሰሉት ድርጊቶች የሚፈጸሙት በዚህች አገር ብቻ አይደለም።

የጭካኔ ድርጊቶች የዕለት ተዕለት ዜና ሆነዋል። የቦምብ ፍንዳታዎች፣ የአሸባሪዎች ጥቃት፣ የነፍስ ግድያ፣ ድብደባና አስገድዶ መድፈር ከብዙዎቹ ጥቂቶቹ ናቸው። መገናኛ ብዙኃን አሰቃቂ ስለሆኑ ድርጊቶች የሚያወሱ ዝርዝር ዘገባዎችን ደጋግመው ስለሚያቀርቡ፣ አሁን አሁን ብዙ ሰዎች እንዲህ ዓይነቶቹን የጭካኔ ድርጊቶች ማየትም ሆነ መስማት አያስደነግጣቸውም።

‘ዓለማችን ምን እየሆነች ነው? ሰዎች ለሌሎች ስሜት ማሰብም ሆነ ለሕይወት አክብሮት መስጠት ጨርሶ ተስኗቸዋል ማለት ነው?’ ብለህ ጠይቀህ ይሆናል። የምንኖርባት ዓለም እንዲህ የሆነችው ለምንድን ነው?

አሁን ደግሞ የካንሰር በሽተኛ የሆኑት የ69 ዓመቱ ሃሪ ያጋጠማቸውን ሁኔታ ተመልከት። ባለቤታቸው መልቲፕል ስክለሮሲስ በሚባል የነርቭ ሥርዓትን በሚያጠቃ በሽታ ይሠቃያሉ። ሆኖም ጎረቤቶቻቸውና ወዳጆቻቸው በፈቃደኝነት ይረዷቸዋል። ሃሪ “እነዚህ ሁሉ ሰዎች ባይረዱን ኖሮ ምን ይውጠን እንደነበር አላውቅም” ሲሉ ተናግረዋል። እርሳቸው በሚኖሩበት በካናዳ የተደረገ አንድ ጥናት እንደሚያሳየው አረጋውያንን ከሚንከባከቡ ሰዎች መካከል ከ50 በመቶ የሚበልጡት፣ ከሚረዷቸው ሰዎች ጋር ምንም ዓይነት የሥጋ ዝምድና የላቸውም። አንተም ሳያሰልሱ ደግነትና የወዳጅነት መንፈስ የሚያሳዩ ሰዎች እንደምታውቅ ጥርጥር የለውም። እውነት ነው፣ የሰው ልጆች ጨካኝ ከመሆን ይልቅ ርኅራኄና ደግነት የማሳየት ችሎታ አላቸው።

ታዲያ የጭካኔ ድርጊት የበዛው ለምንድን ነው? ሰዎች ጨካኝ እንዲሆኑ የሚያደርጋቸው ምንድን ነው? በሌሎች ላይ የጭካኔ ድርጊት የሚፈጽሙ ሰዎች መለወጥ ይችላሉ? የጭካኔ ድርጊት የማይኖርበት ጊዜ ይመጣ ይሆን? የሚመጣ ከሆነስ፣ እውን የሚሆነው እንዴትና መቼ ነው?

[በገጽ 3 ላይ የሚገኝ የሥዕል ምንጭ]

ባቡር:- CORDON PRESS