በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

በጭንቀት በተሞላ ዓለም ውስጥ ተስፋ ማግኘት

በጭንቀት በተሞላ ዓለም ውስጥ ተስፋ ማግኘት

በጭንቀት በተሞላ ዓለም ውስጥ ተስፋ ማግኘት

“ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ ዛሬ፣ ተራ ሰዎች ለሕዝብ የሚጠቅም ነገር ለማድረግና የሚያጋጥሟቸውን የተለመዱ ችግሮች ለመፍታት የሚያስችል ኃይል አላቸው።” በመጋቢት 2006 ኦታዋ፣ ካናዳ በተደረገ ስብሰባ ላይ ይህን የተናገሩት የዩናይትድ ስቴትስ የቀድሞ ፕሬዚዳንት ቢል ክሊንተን ናቸው። አክለውም በ2004 ከተከሰተው የሱናሚ አደጋ ጀምሮ በዓለም አቀፍ ደረጃ የመረዳዳት አዝማሚያ እየታየ መሆኑን ከገለጹ በኋላ ተስፋ በሚንጸባረቅበት ስሜት ዓለም በአሁኑ ጊዜ “ከዚህ በፊት ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ መረዳዳት ባለበት ጊዜ ላይ” እንደምትገኝ ተናግረዋል።

የተፈጥሮ አደጋዎች ሰዎች የወደፊቱን ጊዜ የተሻለ ለማድረግ እንዲሠሩ ያነሳሷቸዋል ብለን መጠበቅ ይኖርብናል? እርስ በርስ ‘መረዳዳት’ እውነተኛ ሰላምና ዘላቂ ደህንነት ለማግኘት የሚያስችል አስተማማኝ መሠረት ሊሆን ይችላል?

የእውነተኛ ተስፋ ምንጭ

የሰው ዘር ከ6,000 ዓመታት በላይ ያስመዘገበው ታሪክ ሰዎች እምነት የማይጣልባቸው መሆናቸውን አሳይቷል። በመሆኑም በመንፈስ አነሳሽነት የተጻፈው መጽሐፍ ቅዱስ “በገዦች አትታመኑ፤ ማዳን በማይችሉ ሥጋ ለባሾችም አትመኩ” የሚል ምክር መስጠቱ ምክንያታዊ ነው። (መዝሙር 146:3) ይህ ዓለም ባቋቋማቸው ድርጅቶች፣ በቁሳዊ ሀብቱና በምኞቶቹ ላይ ተስፋ ማድረግ ለሐዘን መዳረጉ አይቀርም። ለምን? ምክንያቱም “ዓለምና ምኞቱ ያልፋሉ።”—1 ዮሐንስ 2:17

ይሁንና በታሪክ ዘመናት ሁሉ አምላክ ጻድቅ ለሆኑ ሰዎች አስተማማኝ ተስፋ ሆኖላቸዋል። መጽሐፍ ቅዱስ አምላክን “[የጥንቷ] እስራኤል ተስፋ” እና ‘[የእስራኤል] አባቶች ተስፋ’ በማለት የሚጠራው ሲሆን እርሱን መታመኛ፣ መመኪያና ተስፋ ስለ ማድረግ የሚናገሩ በርካታ ሐሳቦችን ይዟል። (ኤርምያስ 14:8፤ 17:13፤ 50:7) ቅዱሳን መጻሕፍት “እግዚአብሔርን ተስፋ አድርግ” በማለት ማበረታቻ መስጠታቸው ተገቢ ነው።—መዝሙር 27:14

ምሳሌ 3:5, 6 እንዲህ ሲል ይመክረናል:- “በፍጹም ልብህ በእግዚአብሔር ታመን፤ በራስህ ማስተዋል አትደገፍ፤ በመንገድህ ሁሉ እርሱን ዕወቅ፤ እርሱም ጐዳናህን ቀና ያደርገዋል።” ይሖዋ አምላክ የማይለወጥ፣ እምነት የሚጣልበትና ቃሉን የማያጥፍ በመሆኑ እንዲህ ባለው ተስፋ ላይ ሙሉ በሙሉ ለመተማመን የሚያስችል በቂ ምክንያት አለህ። (ሚልክያስ 3:6፤ ያዕቆብ 1:17) አምላክ፣ መልካም የሆነውን ሁሉ እንድታገኝ ይፈልጋል። በቃሉ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተገለጸውን ሁልጊዜ የምትታዘዝ ከሆነ ፍርሃት በነገሠበት በዚህ ዘመን ይመራሃል።—ኢሳይያስ 48:17, 18

የአምላክን መመሪያ ከልቡ የሚከተል ሰው ይህ ተስፋ እንደሚፈጸምለት እርግጠኛ መሆን ይችላል:- “እኔ ከአንተ ጋር ነኝና አትፍራ፤ አምላክህ ነኝና አትደንግጥ። አበረታሃለሁ፤ እረዳሃለሁ፤ በጽድቄም ቀኝ እጄ ደግፌ እይዝሃለሁ።” (ኢሳይያስ 41:10) ከልብ የመነጨ ጸሎት ማቅረብና በዚህ ተስፋ ላይ ማሰላሰል አስቸጋሪና አስጨናቂ ሁኔታዎችን ለመቋቋም ስለሚረዳ፣ ይሖዋ አምላክን ከልብ የሚወዱ ሁሉ እንዲህ ማድረጋቸው በእጅጉ ያጽናናቸዋል።

የሁለት ልጆች እናት የሆነችውን አንድሬያ የተባለች የይሖዋ ምሥክር ሁኔታ ተመልከት። እንዲህ ትላለች:- “በሕይወቴ ውስጥ የሚያሰጉ ሁኔታዎች ሲያጋጥሙኝ ይሖዋ በሰጣቸው ተስፋዎች ላይ ማሰላሰሌና መጸለዬ ብርታት አስገኝቶልኛል። በሕይወቴ ውስጥ ለይሖዋ የሰጠሁትን ቦታ እስካለወጥኩት ድረስ ተረጋግቼ መኖር እንደምችል አውቃለሁ።”

በይሖዋ ላይ ያለህን ተስፋ አጠናክር

አንድ መዝሙራዊ በይሖዋ ተስፋ ማድረግ ምን ያህል አስፈላጊ መሆኑን በአጽንኦት ሲናገር “ሕግህን የሚወዱ ብዙ ሰላም አላቸው፤ ዕንቅፋትም የለባቸውም” ብሏል። (መዝሙር 119:165) የአምላክን ቃል በቅንዓት ማጥናት በመንፈሳዊ ሊገነቡህ በሚችሉ ነገሮች ይኸውም ‘እውነት፣ ክቡር፣ ትክክል፣ ንጹሕ፣ ተወዳጅ፣ መልካምና በጎ በሆኑ ነገሮች እንዲሁም በምስጋና’ አእምሮህንና ልብህን ለመሙላት በእጅጉ ይረዳሃል። እነዚህን ነገሮች ለመስማት፣ ለመማር፣ ለመቀበልና በተግባር ላይ ለማዋል የታሰበበት ጥረት የምታደርግ ከሆነ ‘የሰላም አምላክ ከአንተ ጋር ይሆናል።’—ፊልጵስዩስ 4:8, 9

ጆን ለአሥርተ ዓመታት ካካበተው የሕይወት ተሞክሮ በመነሳት እንዲህ ብሏል:- “ስለ ወደፊቱ ጊዜ ያለኝ ስሜት እንዲቀየር እንዲሁም ፍጹም ከሆነና ከማይታይ አምላክ ጋር ዝምድና መመሥረት እንድችል፣ በመጀመሪያ በባሕርዬና በአስተሳሰቤ ላይ ከፍተኛ ለውጥ ማድረግ ነበረብኝ። ከአምላክ ጋር ዝምድና መመሥረት የምችለው መንፈሳዊ ሰው ከሆንኩ ብቻ ነው። ይህ ደግሞ በመንፈስ አነሳሽነት የተጻፈውን የአምላክ ቃል በማንበብና ባነበብነው ላይ በማሰላሰል ሁልጊዜ አምላክን ማሰብንና አምላክ ለነገሮች ያለውን አመለካከት መያዝን ይጠይቃል።”

በቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ የሚገኘውን መንፈስን የሚያድስና ሕይወት ሰጪ የእውነት ውኃ የምትጠጣ ከሆነ በመገናኛ ብዙኃን በየዕለቱ የሚጎርፈውን መጥፎ ዜና ለመቋቋም የሚያስችል ውጤታማና ፍቱን ዘዴ ታገኛለህ። መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠውን ምክር በሥራ ላይ ማዋል የቤተሰብህን አንድነት የሚያጠናክር ከመሆኑም ሌላ ጭንቀትን ለመቀነስ ይረዳሃል። ከዚህም በተጨማሪ አምላክ “በፍጹም ልባቸው የሚታመኑበትን ለማበርታት” ዝግጁ እንደሆነ ተናግሯል። (2 ዜና መዋዕል 16:9) ይሖዋ ለሁኔታዎች እልባት የሚሰጥበት መንገድ የወደፊቱን ጊዜ በመተማመን እንድትጠባበቅ የሚያደርግ ነው።

ጦርነትንና ጅምላ ጭፍጨፋን በዓይኑ ያየው ፊንሃስ እንዲህ ብሏል:- “ሕይወቴን ለይሖዋ አደራ መስጠት እንዳለብኝ ተምሬያለሁ። የመጽሐፍ ቅዱስን መመሪያዎች በተግባር ማዋሌ ከብዙ ችግር ጠብቆኛል።” በይሖዋ አምላክ ከልብህ ከታመንህ እንደ ተራራ የማይገፋ የመሰለህን ችግር እንድትወጣ ይረዳሃል። (መዝሙር 18:29) ከወላጆቹ ጋር የሚቀራረብ አንድ ትንሽ ልጅ በሚታመምበት ወይም በሆነ ምክንያት በሚጨነቅበት ጊዜ እንኳ በእነርሱ ሙሉ በሙሉ ይታመናል፤ እንክብካቤያቸውን ስለሚያገኝም ስጋት አያድርበትም። አንተም በይሖዋ ላይ ተስፋ እንድታደርግ የቀረበልህን ግብዣ ለመቀበል ጥረት ካደረግህ ተመሳሳይ ስሜት ይኖርሃል።—መዝሙር 37:34 የ1980 ትርጉም

ተስፋ ለማድረግ የሚያስችል ጠንካራ መሠረት

ኢየሱስ ክርስቶስ ለተከታዮቹ እንዲህ ብሏቸዋል:- “እንዲህ ብላችሁ ጸልዩ፤ ‘በሰማያት የምትኖር አባታችን ሆይ፤ ስምህ ይቀደስ፤ መንግሥትህ ትምጣ፤ ፈቃድህ በሰማይ እንደ ሆነች፣ እንዲሁ በምድር ትሁን።’” (ማቴዎስ 6:9, 10) በኢየሱስ ክርስቶስ የሚመራው ይህ ሰማያዊ መንግሥት፣ አምላክ በምድር ላይ ሉዓላዊ ገዥ የመሆን መብት እንዳለው የሚያረጋግጥበት መሣሪያ ነው።—መዝሙር 2:7-12፤ ዳንኤል 7:13, 14

በዛሬው ጊዜ በማንኛውም የሕይወት ዘርፍ ሊያጋጥሙ የሚችሉ ለፍርሃት መንስኤ የሚሆኑ ነገሮች አምላክ ጣልቃ መግባቱ አስፈላጊ እንደሆነ በግልጽ ያሳያሉ። ይህ የሚሆንበት ጊዜ ቅርብ መሆኑ ያስደስታል! መሲሐዊ ንጉሥ በመሆን በአምላክ የተሾመው ኢየሱስ ክርስቶስ የይሖዋን ሉዓላዊነት የማስከበርና ስሙን የማስቀደስ ሥልጣን ተሰጥቶታል። (ማቴዎስ 28:18) በቅርቡ ይህ መንግሥት ትኩረቱን ወደ ምድር በማዞር ለፍርሃትና ለጭንቀት መንስኤ የሆኑትን ነገሮች በሙሉ ያስወግዳል። ኢሳይያስ 9:6 ኢየሱስ እኛን ከፍርሃት ነፃ ለማውጣት ብቃት ያለው መሪ መሆኑን ያሳያል። ለምሳሌ ያህል ኢየሱስ “የዘላለም አባት፣” “ድንቅ መካር” እና “የሰላም ልዑል” ተብሎ ተጠርቷል።

“የዘላለም አባት” የሚለውን ማራኪ የሆነ መግለጫ ተመልከት። ኢየሱስ የዘላለም አባት እንደመሆኑ መጠን፣ በቤዛዊ መሥዋዕቱ አማካኝነት ታዛዥ ለሆኑ የሰው ልጆች በምድር ላይ ለዘላለም የመኖር አጋጣሚ ለመስጠት ኃይልና ሥልጣን ብቻ ሳይሆን ፍላጎትም አለው። ይህም ሲባል የሰው ልጆች ከመጀመሪያው ሰው ከአዳም ከወረሱት ኃጢአትና አለፍጽምና በመጨረሻ ነፃ ይወጣሉ ማለት ነው። (ማቴዎስ 20:28፤ ሮሜ 5:12፤ 6:23) በተጨማሪም ክርስቶስ ከአምላክ የተሰጠውን ሥልጣን የሞቱ ሰዎችን ለማስነሳት ይጠቀምበታል።—ዮሐንስ 11:25, 26

ኢየሱስ በምድር በነበረበት ጊዜ “ድንቅ መካር” መሆኑን አስመሥክሯል። ስለ አምላክ ቃል እውቀት ስለነበረውና የሰዎችን ተፈጥሯዊ ባሕርይ በተመለከተ የተለየ ማስተዋል ስለነበረው በዕለት ተዕለት ሕይወት የሚያጋጥሙ ችግሮችን እንዴት መፍታት እንደሚቻል ያውቅ ነበር። ክርስቶስ በሰማይ ከነገሠ በኋላም፣ ይሖዋ ለሰው ልጆች ሐሳቡን ለማስተላለፍ የሚጠቀምበት ዋነኛ መሣሪያ ሆኖ በማገልገል “ድንቅ መካር” መሆኑን ቀጥሏል። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ተመዝግቦ የሚገኘው የኢየሱስ ምክር ምንጊዜም ጥበብ ያለበትና እንከን የማይወጣለት ነው። ይህንን ማወቅና ማመን ከጭንቀትና ከሚያሽመደምድ ፍርሃት ነፃ የሆነ ሕይወት እንድትመራ ያስችልሃል።

በተጨማሪም ኢሳይያስ 9:6 ኢየሱስን “የሰላም ልዑል” በማለት ይጠራዋል። ክርስቶስ የሰላም ልዑል እንደመሆኑ መጠን በቅርቡ ሥልጣኑን ተጠቅሞ ማንኛውንም ዓይነት ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልዩነት ያስወግዳል። ይህን የሚያደርገው እንዴት ነው? መላው የሰው ዘር በመሲሐዊው መንግሥት የሰላም አገዛዝ ሥር እንዲሆን በማድረግ ነው።—ዳንኤል 2:44

የአምላክ መንግሥት ሲገዛ በምድር ዙሪያ ዘላቂ ሰላም ይሰፍናል። ይህ እንደሚሆን እንዴት እርግጠኛ መሆን ትችላለህ? ምክንያቱ በኢሳይያስ 11:9 ላይ ተገልጿል። ጥቅሱ እንዲህ ይላል:- “[የመንግሥቱ ተገዥዎች] በተቀደሰው ተራራዬ ሁሉ ላይ ጕዳት ወይም ጥፋት አያደርሱም፤ ውሃ ባሕርን እንደሚሸፍን፣ ምድር ሁሉ እግዚአብሔርን [“ይሖዋን፣” NW] በማወቅ ትሞላለችና።” በመጨረሻ በምድር ላይ የሚኖር እያንዳንዱ ሰው ስለ አምላክ ትክክለኛ እውቀት ይኖረዋል፤ ለእርሱም ታዛዥ ይሆናል። ይህ ተስፋ ያስደስትሃል? ከሆነ በዋጋ የማይተመነውን ‘የይሖዋን እውቀት’ ለመቅሰም አፋጣኝ እርምጃ ውሰድ።

መጽሐፍ ቅዱስ በዘመናችን ስለሚከናወኑት ነገሮችና መጭው ጊዜ ስላዘለው ብሩህ ተስፋ ያሰፈረውን ትክክለኛ ትምህርት በመቅሰም፣ እምነት ከሚያጠነክረውና ሕይወት ሰጭ ከሆነው የአምላክ እውቀት ጥቅም ማግኘት ትችላለህ። በመሆኑም በአካባቢህ የሚገኙ የይሖዋ ምሥክሮች ከሚያካሂዱት መጽሐፍ ቅዱስን የማስተማር ፕሮግራም ተጠቃሚ እንድትሆን እናበረታታሃለን። እንዲህ ማድረግህ በጭንቀት በተሞላው በዚህ ዓለም ተረጋግተህ እንድትኖርና እውነተኛ ተስፋ እንድታገኝ ይረዳሃል።

[በገጽ 7 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

የአምላክ መንግሥት፣ ተስፋ ይፈነጥቃል የምንለው ለምንድን ነው?

ኢየሱስ ክርስቶስ የአምላክ መንግሥት ንጉሥ እንደመሆኑ መጠን በአጽናፈ ዓለም ላይ የመግዛት ችሎታና መብት ተሰጥቶታል። (ማቴዎስ 28:18) ኢየሱስ የምድራችን ሥነ ምህዳር ሚዛኑን እንዲጠብቅ ያደርጋል። ሕመምንና በሽታን ያስወግዳል። ኢየሱስ በምድር ሳለ የፈጸማቸው ድንቅ ተአምራት፣ ወደፊት በግዛቱ ውስጥ የሚፈሱትን ታላላቅ በረከቶች የሚያመላክቱ ሲሆን ፍጹምና እምነት የሚጣልበት ንጉሥ መሆኑን ያረጋግጣሉ። ከታች ከተዘረዘሩት መሲሐዊው ንጉሥ ካሉት ባሕርያት መካከል ይበልጥ የሚማርክህ የትኛው ነው?

በቀላሉ የሚቀረብ።ማርቆስ 10:13-16

ምክንያታዊና የማያዳላ።ማርቆስ 10:35-45

ኃላፊነት የሚሰማውና ራስ ወዳድ ያልሆነ።ማቴዎስ 4:5-7፤ ሉቃስ 6:19

ጻድቅና ፍትሐዊ።ኢሳይያስ 11:3-5፤ ዮሐንስ 5:30፤ 8:16

አሳቢ፣ የሌሎችን ስሜት ግምት ውስጥ የሚያስገባና ትሑት።ዮሐንስ 13:3-15

[በገጽ 4 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብና ማሰላሰል በይሖዋ ተስፋ እንድናደርግ ይረዳናል