በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

በመንፈሳዊ የሚረዳህ ጥሩ አማካሪ አለህ?

በመንፈሳዊ የሚረዳህ ጥሩ አማካሪ አለህ?

በመንፈሳዊ የሚረዳህ ጥሩ አማካሪ አለህ?

ዖዝያን የ16 ዓመት ወጣት ሳለ በደቡባዊው የይሁዳ መንግሥት ላይ ንጉሥ እንዲሆን የተሾመ ሲሆን ከ829 እስከ 778 ከክርስቶስ ልደት በፊት ድረስ ማለትም ከ50 ለሚበልጡ ዓመታት ገዝቷል። ይህ ንጉሥ ገና ከወጣትነት ዕድሜው አንስቶ ‘በአምላክ ፊት ቅን የሆነውን ነገር ያደርግ’ ነበር። ዖዝያን ቅን መንገድ እንዲከተል ተጽዕኖ ያሳደረበት ማን ነበር? የታሪክ ዘገባው እንዲህ ይላል:- “[ዖዝያን] እግዚአብሔርን መፍራት ባስተማረው በዘካርያስ ዘመን እግዚአብሔርን ፈለገ፤ እግዚአብሔርን በፈለገ መጠንም አምላክ ነገሮችን አከናወነለት።”—2 ዜና መዋዕል 26:1, 4, 5

የንጉሡ አማካሪ ስለነበረው ስለ ዘካርያስ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከላይ ከሰፈረው ዘገባ ውጪ ብዙም የሚታወቅ ነገር የለም። ይሁንና ዘካርያስ ለወጣቱ ገዢ ‘አምላክን መፍራት በማስተማር’ ይህ ንጉሥ ትክክል የሆነውን ማድረግ እንዲችል በጎ ተጽዕኖ አሳድሮበታል። ዚ ኤክስፖዚተርስ ባይብል የተባለው መጽሐፍ ዘካርያስ “የቅዱሳን መጻሕፍት እውቀት ያለው፣ ከፍተኛ የሆነ መንፈሳዊ ተሞክሮ ያካበተና እውቀቱን ለሌሎች የማካፈል ችሎታ ያለው ሰው” እንደነበር እሙን ነው በማለት አስተያየቱን ሰጥቷል። አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሑር ዘካርያስን በሚመለከት እንደሚከተለው ብለዋል:- “ትንቢቶችን ጠንቅቆ የሚያውቅ . . . አስተዋይ፣ ለአምላክ ያደረ እንዲሁም ጥሩ ሰው ነበር፤ ይህም በዖዝያን ላይ ትልቅ ተጽዕኖ ያሳደረ ይመስላል።”

ዖዝያን የተከተለው የታማኝነት ጎዳና ብዙ በረከቶችን ያስገኘለት ከመሆኑም በላይ የእውነተኛው አምላክ ‘እርዳታ’ ስላልተለየው ‘እጅግ በርትቶ ነበር።’ አዎን፣ ዖዝያን “በዘካርያስ ዘመን” ጥረቱ ሁሉ ሊሳካለት የቻለው በተከተለው የታማኝነት ጎዳና ምክንያት ነበር። (2 ዜና መዋዕል 26:6-8 የ1954 ትርጉም) ዖዝያን ስኬታማ ከሆነ በኋላ ከአማካሪው ከዘካርያስ ያገኛቸውን ትምህርቶች ችላ ማለት ጀመረ። እንዲያውም ዖዝያን “ለጥፋት ልቡ ታበየ፣ አምላኩንም እግዚአብሔርን በደለ።” በተለይ በአንድ ወቅት በወሰደው የድፍረት እርምጃ ምክንያት በከባድ የቆዳ በሽታ ስለተጠቃ የንግሥና ተግባሩን ሙሉ በሙሉ መወጣት ሳይችል ቀርቷል።—2 ዜና መዋዕል 26:16-21 የ1954 ትርጉም

አንተስ ‘አምላክን እንድትፈልግ’ የሚያበረታታህ አስተማሪ ወይም አማካሪ አለህ? ወጣትም እንሁን ጎልማሳ፣ ወንድም እንሁን ሴት ሁላችንም እንዲህ ያለ አማካሪ ሊኖረን ይችላል። አማካሪህን እንደ ውድ ሀብት ልትመለከተው ይገባል፤ ምክንያቱም የሚሰጥህ ምክር በይሖዋ ዓይን ትክክል የሆነውን ነገር ማድረግህን እንድትቀጥል ሊረዳህ ይችላል። ይህን የጎለመሰ ክርስቲያን አዳምጠው፤ የሚሰጥህንም ምክር በትኩረት ተከታተል። ‘አምላክን መፍራት የሚያስተምርህ’ እንዲህ ዓይነቱ ሰው የሚሰጥህን ጥበብ ያዘለ ምክር በፍጹም ቸል አትበል።—ምሳሌ 1:5፤ 12:15፤ 19:20