በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ከቤት ወደ ቤት በምናከናውነው አገልግሎት የሚያጋጥሙንን ተፈታታኝ ሁኔታዎች መቋቋም

ከቤት ወደ ቤት በምናከናውነው አገልግሎት የሚያጋጥሙንን ተፈታታኝ ሁኔታዎች መቋቋም

ከቤት ወደ ቤት በምናከናውነው አገልግሎት የሚያጋጥሙንን ተፈታታኝ ሁኔታዎች መቋቋም

“የእግዚአብሔርን ወንጌል ለእናንተ እንደምናበሥር በአምላካችን ድፍረት አገኘን።”—1 ተሰ. 2:2

1. ኤርምያስ ምን ዓይነት ተፈታታኝ ሁኔታዎች አጋጥመውት ነበር? እነዚህን ሁኔታዎችስ ሊቋቋማቸው የቻለው እንዴት ነበር?

ኤርምያስ፣ እንደ እኛው ዓይነት ስሜት ያለው ሰው ነበር። ይሖዋ፣ ኤርምያስን ‘ለሕዝቦች ነቢይ’ አድርጎ እንደሾመው ሲነግረው “ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፤ እንዴት እንደምናገር አላውቅም፤ ገና ሕፃን ልጅ ነኝና” ብሎ ነበር። ያም ቢሆን በይሖዋ በመታመን የተሰጠውን ተልእኮ ተቀብሏል። (ኤር. 1:4-10) ኤርምያስ ሕዝቡ ግዴለሽ ቢሆንም፣ ቢቃወመውም፣ ቢያፌዝበትም እንዲሁም አካላዊ ጥቃት ቢሰነዝርበትም ከ40 ለሚበልጡ ዓመታት ይህንን ሁሉ ተቋቁሞ በነቢይነት አገልግሏል። (ኤር. 20:1, 2) ኤርምያስ ተስፋ ቆርጦ ሥራውን ለማቆም ያሰበባቸው ጊዜያት ቢኖሩም በሰዎች ዘንድ ተወዳጅነት የሌለውን መልእክት ልበ ደንዳና ለሆነው ሕዝብ በጽናት ሰብኳል። ኤርምያስ በራሱ ኃይል ፈጽሞ ሊያደርገው የማይችለውን ነገር አምላክ በሰጠው ብርታት ማከናወን ችሏል።—ኤርምያስ 20:7-9ን አንብብ።

2, 3. በዛሬው ጊዜ ያሉ የአምላክ አገልጋዮች፣ ልክ እንደ ኤርምያስ ተፈታታኝ ሁኔታዎች የሚያጋጥሟቸው እንዴት ነው?

2 በዛሬው ጊዜ ያሉ በርካታ የአምላክ አገልጋዮች የኤርምያስን ስሜት ይጋራሉ። አንዳንዶቻችን ከቤት ወደ ቤት ስለ መስበክ ስናስብ ‘ይህ ፈጽሞ የማላደርገው ነገር ነው’ ያልንበት ጊዜ ነበር። ሆኖም ይሖዋ ምሥራቹን እንድንሰብክ እንደሚፈልግ ስንረዳ ፍርሃታችንን አስወግደን በቅንዓት መስበክ ጀመርን። ያም ሆኖ አብዛኞቻችን ለተወሰነ ጊዜም ቢሆን በስብከቱ ሥራ መካፈላችንን መቀጠል አስቸጋሪ እንዲሆንብን የሚያደርጉ ሁኔታዎች በሕይወታችን ውስጥ አጋጥመውናል። ለመጀመሪያ ጊዜ ከቤት ወደ ቤት መስበክም ሆነ እስከ መጨረሻው በዚህ የአገልግሎት ዘርፍ መካፈል ተፈታታኝ እንደሆነ አይካድም።—ማቴ. 24:13

3 ለተወሰነ ጊዜ ያህል ከይሖዋ ምሥክሮች ጋር መጽሐፍ ቅዱስን ስታጠና እንዲሁም በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ ስትገኝ የቆየህ ቢሆንም ከቤት ወደ ቤት መስበክ ለመጀመር እያመነታህ ነው? ወይም ደግሞ ጥሩ ጤንነት ያለህ የይሖዋ ምሥክር ብትሆንም ከቤት ወደ ቤት ማገልገል ይከብድሃል? የተለያየ አስተዳደግና ሁኔታ ያላቸው ክርስቲያኖች ከቤት ወደ ቤት ከማገልገል ጋር በተያያዘ የሚያጋጥሟቸውን ተፈታታኝ ሁኔታዎች እየተቋቋሙ ነው። አንተም በይሖዋ እርዳታ እንዲህ ማድረግ ትችላለህ።

ድፍረት ማግኘት

4. ሐዋርያው ጳውሎስ ምሥራቹን በድፍረት ለመስበክ ያስቻለው ምን ነበር?

4 ዓለም አቀፉ የስብከት ሥራ የሚከናወነው በሰዎች ኃይል ወይም ጥበብ ሳይሆን በአምላክ መንፈስ መሆኑን ሳትገነዘብ አልቀረህም። (ዘካ. 4:6) እያንዳንዱ ክርስቲያን በሚያከናውነው አገልግሎት ረገድም ሁኔታው ተመሳሳይ ነው። (2 ቆሮ. 4:7) እስቲ ሐዋርያው ጳውሎስን እንደ ምሳሌ እንመልከት። ጳውሎስ፣ እሱና ሚስዮናዊ የሆነው ባልደረባው በተቃዋሚዎች የደረሰባቸውን እንግልት በማስታወስ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “ከዚህ ቀደም በፊልጵስዩስ መከራ ተቀብለን ተንገላታን፤ ነገር ግን ብርቱ ተቃውሞ ቢደርስብንም እንኳ የእግዚአብሔርን ወንጌል ለእናንተ እንደምናበሥር በአምላካችን [“በአምላካችን እርዳታ እንደምንም ብለን፣ NW] ድፍረት አገኘን።” (1 ተሰ. 2:2፤ ሥራ 16:22-24) እንደ ጳውሎስ ያለ ቀናተኛ ሰባኪ አንዳንድ ጊዜ ለመስበክ ትግል ማድረግ ጠይቆበት እንደነበር ማሰብ ሊከብደን ይችላል። ሆኖም ሁላችንም እንደምናደርገው ጳውሎስም ምሥራቹን በድፍረት ለመስበክ በይሖዋ መታመን አስፈልጎት ነበር። (ኤፌሶን 6:18-20ን አንብብ።) የጳውሎስን ምሳሌ መኮረጅ የምንችለው እንዴት ነው?

5. ለመስበክ የሚያስችል ድፍረት ለማግኘት የሚረዳን አንዱ መንገድ ምንድን ነው?

5 ለመስበክ የሚያስችል ድፍረት ለማግኘት የሚረዳን አንዱ መንገድ ጸሎት ነው። አንዲት አቅኚ እንዲህ በማለት ተናግራለች:- “በድፍረት መናገር እንድችል እጸልያለሁ፣ የሰዎችን ልብ በሚነካ መንገድ መልእክቱን ለመናገር እንድችል እጸልያለሁ፤ እንዲሁም በአገልግሎት ደስታ ለማግኘት እጸልያለሁ። ደግሞም ሥራው የእኛ ሳይሆን የይሖዋ ነው፤ በመሆኑም ያለ እሱ እርዳታ ምንም ማድረግ አንችልም።” (1 ተሰ. 5:17) ሁላችንም በድፍረት ለመስበክ እንድንችል አምላክ፣ ቅዱስ መንፈሱን እንዲሰጠን ሳናቋርጥ መጸለይ ያስፈልገናል።—ሉቃስ 11:9-13

6, 7. (ሀ) ሕዝቅኤል ምን ራእይ ተመልክቶ ነበር? ራእዩስ ምን ትርጉም ነበረው? (ለ) ሕዝቅኤል የተመለከተው ራእይ በዛሬው ጊዜ ለሚገኙ የአምላክ አገልጋዮች ምን ትምህርት ይዟል?

6 የሕዝቅኤል መጽሐፍ በድፍረት ለመናገር የሚረዳንን ሌላ ነገር ይጠቁመናል። ይሖዋ፣ በራእይ አማካኝነት ለሕዝቅኤል “የሰቈቃ፣ የልቅሶና የዋይታ ቃላት” በሁለቱም በኩል የተጻፈበት ጥቅል መጽሐፍ ከሰጠው በኋላ “የሰው ልጅ ሆይ፤ እኔ የምሰጥህን ይህን ጥቅል መጽሐፍ ብላ፤ ሆድህንም ሙላ” በማለት አዘዘው። ይህ ራእይ ምን ትርጉም ነበረው? ሕዝቅኤል የሚሰብከውን መልእክት ሙሉ በሙሉ መረዳት እንዲሁም የራሱ ማድረግ ነበረበት፤ መልእክቱ ስሜቱን ሊነካው ይገባ ነበር። ነቢዩ “እኔም በላሁት፤ በአፌም ውስጥ እንደ ማር ጣፈጠኝ” በማለት ቀጥሎ የተፈጸመውን ነገር ተናግሯል። ሕዝቅኤል የአምላክን መልእክት ለሕዝብ ማወጅ ማር እንደ መብላት አስደሳች ሆኖለት ነበር። አምላክ የሰጠውን ሥራ ለመፈጸም ልበ ደንዳና ለሆኑ ሰዎች ኃይለኛ መልእክት ማወጅ የነበረበት ቢሆንም ይሖዋን ወክሎ መናገር እንዲሁም እሱ የሰጠውን ኃላፊነት መወጣት ታላቅ መብት እንደሆነ ተሰምቶት ነበር።—ሕዝቅኤል 2:8 እስከ 3:4, 7-9ን አንብብ።

7 ይህ ራእይ በዛሬው ጊዜ ለሚገኙ የአምላክ አገልጋዮች ጠቃሚ ትምህርት ይዟል። እኛም፣ አብዛኛውን ጊዜ ጥረታችንን ለማያደንቁ ሰዎች ኃይለኛ መልእክት እናውጃለን። ክርስቲያናዊ አገልግሎታችንን፣ ምንጊዜም ቢሆን አምላክ እንደሰጠን መብት አድርገን እንድንመለከተው በመንፈሳዊ በደንብ መመገብ አለብን። የአምላክን ቃል ሙሉ በሙሉ ለመረዳት ላይ ላዩን ወይም አልፎ አልፎ የሚደረግ ጥናት በቂ አይደለም። አንተስ በግልህ የምታደርገው የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብና ጥናት ጥልቀት ያለው ወይም ቋሚ እንዲሆን ማድረግ ትችላለህ? ባነበብከው ነገር ላይ አሁን ከምታደርገው ይበልጥ አዘውትረህ ማሰላሰል ትችላለህ?—መዝ. 1:2, 3

የመጽሐፍ ቅዱስ ውይይት መጀመር

8. አንዳንድ አስፋፊዎች ከቤት ወደ ቤት በሚያከናውኑት አገልግሎት መጽሐፍ ቅዱሳዊ ውይይት ለመጀመር የረዳቸው የትኛው ዘዴ ነው?

8 ከቤት ወደ ቤት በማገልገል ረገድ አብዛኞቹ አስፋፊዎች በጣም የሚከብዳቸው ውይይት መጀመር ነው። በአንዳንድ የአገልግሎት ክልሎች ውስጥ ከሰዎች ጋር ውይይት መጀመር ተፈታታኝ መሆኑ አይካድም። ከታች ባለው ሣጥን ላይ እንደተገለጸው አንዳንድ አስፋፊዎች ከቤት ወደ ቤት ሄደው ሰዎችን ሲያነጋግሩ አስቀድመው ያሰቡበትን የመግቢያ ሐሳብ ከተናገሩ በኋላ ለቤቱ ባለቤት ትራክት በመስጠት ውይይቱን መጀመር ይቀላቸዋል። የትራክቱ ርዕስ ወይም ማራኪ የሆኑት ሥዕሎች የቤቱን ባለቤት ትኩረት ሊስቡት ይችላል፤ ይህም ወደ ቤቱ የሄድንበትን ምክንያት በአጭሩ ለመናገር እንዲሁም ጥያቄ አንስተን ለመወያየት ይረዳናል። ውይይት ለመጀመር የሚረዳን ሌላው ዘዴ ደግሞ ለቤቱ ባለቤት ሦስት ወይም አራት የተለያዩ ትራክቶች በማሳየት የፈለገውን እንዲመርጥ መጋበዝ ነው። እርግጥ ነው፣ ዓላማችን ትራክቶችን ብቻ መስጠት ወይም በየቤቱ በትራክቶች መጠቀም ሳይሆን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ለማስጀመር የሚረዳ ውይይት ማድረግ ነው።

9. በደንብ መዘጋጀት ጠቃሚ የሆነው ለምንድን ነው?

9 የምትጠቀመው በየትኛውም ዘዴ ቢሆን፣ በደንብ መዘጋጀትህ ከቤት ወደ ቤት ስታገለግል ሳትደናገጥ በግለት ለመናገር ያስችልሃል። አንድ አቅኚ እንዲህ ብሏል:- “በደንብ ተዘጋጅቼ ከሄድኩ ይበልጥ ደስተኛ እሆናለሁ። በተዘጋጀሁት የመግቢያ ሐሳብ ተጠቅሜ ለመመስከርም እፈልጋለሁ።” ሌላ አቅኚ ደግሞ “የማበረክታቸውን ጽሑፎች በደንብ ካነበብኳቸው በአገልግሎት ላይ በጽሑፎቹ ለመጠቀም እጓጓለሁ” በማለት ተናግሯል። የምትጠቀምበትን የመግቢያ ሐሳብ ድምፅህን ሳታሰማ መከለስ የተወሰነ ጥቅም ቢኖረውም ብዙዎች ድምፃቸውን ከፍ አድርገው መለማመዳቸው የበለጠ ረድቷቸዋል። እንዲህ ማድረጋቸው ለይሖዋ ምርጣቸውን ለመስጠት አስችሏቸዋል።—ቈላ. 3:23፤ 2 ጢሞ. 2:15

10. በመስክ አገልግሎት ስምሪት ስብሰባ ላይ ተግባራዊ ሊሆኑ የሚችሉ ሐሳቦችን ለማቅረብና ስብሰባው ጠቃሚ እንዲሆን ምን ማድረግ ይቻላል?

10 በመስክ አገልግሎት ስምሪት ስብሰባ ላይ ተግባራዊ ሊሆኑ የሚችሉ ሐሳቦች መቅረባቸው ከቤት ወደ ቤት የምናደርገው አገልግሎት ውጤታማ እንዲሁም አስደሳች እንዲሆን አስተዋጽኦ ያበረክታል። የዕለት ጥቅሱ ሐሳብ ከአገልግሎት ጋር በቀጥታ የሚያያዝ ከሆነ ጥቅሱን አንብቦ አጠር ያለ ውይይት ማድረግ ይቻላል። ይሁን እንጂ የመስክ አገልግሎት ስምሪት ስብሰባውን የሚመራው ወንድም፣ ለጉባኤው የአገልግሎት ክልል የሚስማማ ቀለል ያለ የመግቢያ ሐሳብ አንስቶ ለመወያየት ወይም ሠርቶ ማሳያ ለማቅረብ አሊያም በዚያን ዕለት በአገልግሎታቸው ሊጠቀሙበት የሚችሉ ሌላ ጠቃሚ ሐሳብ ለማካፈል በቂ ጊዜ ሊመድብ ይገባል። እንዲህ ማድረጉ በስብሰባው ላይ የተገኙ ወንድሞች ውጤታማ የሆነ ምሥክርነት ለመስጠት እንዲችሉ ይረዳቸዋል። ሽማግሌዎችም ሆኑ ስብሰባውን የሚመሩ ሌሎች ወንድሞች አስቀድመው ጥሩ ዝግጅት ካደረጉ በተመደበው ሰዓት ውስጥ ከላይ የሰፈሩትን ሐሳቦች ተግባራዊ ማድረግ ይችላሉ።—ሮሜ 12:8

ማዳመጥ የሚያስገኘው ጥቅም

11, 12. ርኅራኄ በሚንጸባረቅበት መንገድ ማዳመጥ ምሥራቹን የሰዎችን ልብ በሚነካ መንገድ ለማቅረብ የሚያስችለን እንዴት ነው? ምሳሌዎች ስጥ።

11 በአገልግሎት ላይ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ውይይት ለመጀመር እንዲሁም ለምናገኛቸው ሰዎች መልእክቱን ልባቸውን በሚነካ መንገድ ለማስተላለፍ እንድንችል ጥሩ ዝግጅት ከማድረግ በተጨማሪ ለሰዎች ልባዊ አሳቢነት ማሳየት ይኖርብናል። እንዲህ ያለውን አሳቢነት ከምናሳይባቸው መንገዶች አንዱ ሰዎች ሲናገሩ በጥሞና ማዳመጥ ነው። አንድ ተጓዥ የበላይ ተመልካች እንዲህ ብሏል:- “ታጋሽ መሆንና ሰዎች ሲናገሩ ለማዳመጥ ፍላጎት እንዳለን ማሳየት ሰዎች መልእክታችንን እንዲሰሙ የማድረግ ኃይል አለው፤ እንዲሁም በግለሰብ ደረጃ ከልብ እንደምናስብላቸው ያሳያል።” ቀጥሎ ካለው ተሞክሮ እንደምንመለከተው ሰዎችን ርኅራኄ በሚንጸባረቅበት መንገድ ማዳመጥ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ውይይት ለመጀመር ይበልጥ ፈቃደኞች እንዲሆኑ መንገድ ሊከፍት ይችላል።

12 አንዲት ሴት የሦስት ወር ሕፃን ልጇን በሞት በማጣቷ መሪር ሐዘን ላይ ሳለች ወደ ቤቷ ስለመጡ ሁለት ሰዎች የጻፈችው ደብዳቤ በፈረንሳይ ሴንት ኤቴይን ከተማ በሚታተመው ለ ፕሮግሬ የተባለ ጋዜጣ ላይ ወጥቶ ነበር። ሴትየዋ እንዲህ በማለት ጽፋለች:- “ገና ሳያቸው የይሖዋ ምሥክሮች መሆናቸው ስለገባኝ ላነጋግራቸው እንደማልፈልግ በትሕትና ልገልጽላቸው አሰብኩ፤ ይሁን እንጂ አምላክ መከራ እንዲኖር ለምን እንደፈቀደ የሚገልጽ ብሮሹር እንደያዙ ተመለከትኩ። በዚህ ወቅት ወደ ቤት ላስገባቸውና የሚያቀርቡት ሐሳብ ትክክል እንዳልሆነ ላሳያቸው ወሰንኩ። . . . ከእነዚህ የይሖዋ ምሥክሮች ጋር ከአንድ ሰዓት በላይ ቆየን። ርኅራኄ በሚንጸባረቅበት መንገድ ያዳመጡኝ ሲሆን በጣም ስለተጽናናሁ በሌላ ጊዜ ለመገናኘት ቀጠሮ ያዝን።” (ሮሜ 12:15) ከጊዜ በኋላ ይህቺ ሴት መጽሐፍ ቅዱስን ለማጥናት ተስማማች። ሴትየዋ ለመጀመሪያ ጊዜ የይሖዋ ምሥክሮች ቤቷ በመጡበት ወቅት ከነበሩት ሁኔታዎች ትዝ የሚላት የተናገሩት ነገር ሳይሆን ያዳመጡበት መንገድ መሆኑ ትልቅ ትምህርት ይሰጠናል።

13. ምሥራቹን የምንሰብክበትን መንገድ እንደ ሰዎች ሁኔታ ማስተካከል የምንችለው እንዴት ነው?

13 ሰዎችን ርኅራኄ በሚንጸባረቅበት መንገድ ስናዳምጣቸው የሚያሳስባቸው ነገር ምን እንደሆነ እንዲነግሩን አጋጣሚ እንሰጣቸዋለን። ይህም ምሥራቹን በተሻለ መንገድ ለመናገር ያስችለናል። ውጤታማ የሆኑ የወንጌሉ ሰባኪዎች አብዛኛውን ጊዜ ጥሩ አድማጮች እንደሆኑ ሳታስተውል አትቀርም። (ምሳሌ 20:5) እነዚህ ክርስቲያኖች በአገልግሎት ላይ ለሚያገኟቸው ሰዎች ልባዊ አሳቢነት ያሳያሉ። ያነጋገሯቸውን ሰዎች ስምና አድራሻ ብቻ ሳይሆን ሰዎቹ የሚያሳስቧቸውንና የሚያስፈልጓቸውን ነገሮችም ጭምር በማስታወሻቸው ላይ ያሰፍራሉ። አንድ ሰው የሚያሳስበውን ነገር ከነገራቸው በጉዳዩ ላይ ምርምር አድርገው ሳይዘገዩ ተመልሰው በመሄድ ያገኙትን ሐሳብ ያካፍሉታል። ሐዋርያው ጳውሎስ እንዳደረገው ሁሉ እነሱም ስለ አምላክ መንግሥት የሚናገሩበትን መንገድ እንደ ሰዎች ሁኔታ ያስተካክላሉ። (1 ቆሮንቶስ 9:19-23ን አንብብ።) እንዲህ ያለው ልባዊ አሳቢነት ሰዎች ለምሥራቹ ጥሩ ምላሽ እንዲሰጡ የሚያደርግ ከመሆኑም በላይ ‘የአምላካችንን ከአንጀት የመነጨ ርኅራኄ’ ግሩም በሆነ መንገድ የሚያንጸባርቅ ነው።—ሉቃስ 1:78 NW

አዎንታዊ አመለካከት ይኑራችሁ

14. አገልግሎታችንን በምናከናውንበት ጊዜ የይሖዋን ባሕርያት ማንጸባረቅ የምንችለው እንዴት ነው?

14 ይሖዋ የመምረጥ ነፃነት በመስጠት አክብሮናል። እሱ ሁሉን ቻይ አምላክ ቢሆንም ሰዎች በፍቅሩ ተማርከው እንዲያገለግሉት ይፈልጋል እንጂ ማንንም አያስገድድም፤ እንዲሁም ያደረጋቸውን ግሩም ዝግጅቶች የሚያደንቁ ሰዎችን ይባርካል። (ሮሜ 2:4) እኛም አገልጋዮቹ እንደመሆናችን መጠን ስለ እሱ በምንመሰክርበት ጊዜ ሁሉ፣ የአምላካችንን ምሕረት በሚያንጸባርቅ መንገድ ምሥራቹን ለመናገር ዝግጁ ልንሆን ይገባል። (2 ቆሮ. 5:20, 21፤ 6:3-6) ይህንንም ለማድረግ በአገልግሎት ክልላችን ውስጥ ለምናገኛቸው ሰዎች አዎንታዊ አመለካከት ማዳበር ይኖርብናል። እንዲህ ያለውን አመለካከት ለማዳበር ምን ሊረዳን ይችላል?

15. (ሀ) ኢየሱስ፣ ሐዋርያቱ የሚሰብኩትን መልእክት ሰዎች ካልተቀበሏቸው ምን እንዲያደርጉ መመሪያ ሰጥቷቸዋል? (ለ) ምሥራቹ የሚገባቸውን ሰዎች በመፈለጉ ሥራ ላይ እንድናተኩር ምን ሊረዳን ይችላል?

15 ኢየሱስ፣ ተከታዮቹ የሚሰብኩትን መልእክት አንዳንዶች ባይቀበሏቸው በሁኔታው ከልክ በላይ ከመጨነቅ ይልቅ የሚገባቸውን ሰዎች በመፈለጉ ሥራ ላይ እንዲያተኩሩ ለሐዋርያቱ መመሪያ ሰጥቷቸዋል። (ማቴዎስ 10:11-15ን አንብብ።) ቀለል ያሉና ሊደረስባቸው የሚችሉ ግቦችን ማውጣት ይህን ለማድረግ ሊረዳን ይችላል። አንድ ወንድም፣ ማዕድናት ከሚፈልግ ሰው ጋር ራሱን ያመሳስላል። ይህ ወንድም “ዛሬ ወርቅ ማግኘት አለብኝ” የሚል መርሕ አለው። ሌላ ወንድም ደግሞ “በየሳምንቱ፣ ፍላጎት ያለው አንድ ሰው የማግኘት እንዲሁም በጥቂት ቀናት ውስጥ ተመልሶ በመሄድ ከግለሰቡ ጋር ውይይቱን የመቀጠል” ግብ አለው። አንዳንድ አስፋፊዎች ከቤት ወደ ቤት ሲያገለግሉ ለሚያገኙት ለእያንዳንዱ ሰው ከተቻለ ቢያንስ አንድ ጥቅስ ለማንበብ ይጥራሉ። አንተስ ልትደርስበት የምትችል ምን ግብ ልታወጣ ትችላለህ?

16. በስብከቱ ሥራ እንድንቀጥል የሚያነሳሳን ምን ምክንያት አለን?

16 ከቤት ወደ ቤት በምናከናውነው አገልግሎት ውጤታማ መሆናችን፣ በአገልግሎት ክልላችን የሚገኙት ሰዎች በሚሰጡት ምላሽ ላይ ብቻ የተመካ አይደለም። እርግጥ ነው፣ የስብከቱ ሥራ ቅን ልብ ያላቸው ሰዎች እንዲድኑ በመርዳት ረገድ ትልቅ ሚና የሚጫወት ቢሆንም ከዚህ ይበልጥ አስፈላጊ የሆኑ ሌሎች ዓላማዎችም አሉት። ክርስቲያናዊው አገልግሎት ለይሖዋ ያለንን ፍቅር ለማሳየት አጋጣሚ ይሰጠናል። (1 ዮሐ. 5:3) በተጨማሪም በደም ዕዳ ተጠያቂ ከመሆን ነጻ ያደርገናል። (ሥራ 20:26, 27) ፈሪሃ አምላክ ለሌላቸው ሰዎችም ‘የፍርድ ሰዓት መድረሱን’ ያስጠነቅቃል። (ራእይ 14:6, 7) ከሁሉ በላይ ደግሞ በምሥራቹ ስብከት አማካኝነት የይሖዋ ስም በዓለም ዙሪያ ይመሰገናል ወይም ይወደሳል። (መዝ. 113:3) ስለዚህ ሰዎች ቢሰሙንም ባይሰሙንም የአምላክን መንግሥት መልእክት ማወጃችንን መቀጠል ይኖርብናል። ይሖዋ ምሥራቹን ለመስበክ የምናደርገውን ጥረት እንደሚያደንቀው ምንም ጥርጥር የለውም።—ሮሜ 10:13-15

17. ሰዎች በቅርቡ የትኛውን እውነታ አምነው ለመቀበል ይገደዳሉ?

17 በዛሬው ጊዜ የሚገኙ በርካታ ሰዎች ለምንሰብከው መልእክት ግዴለሽ ቢሆኑም በቅርቡ አመለካከታቸው ይለወጣል። (ማቴ. 24:37-39) ሕዝቅኤል ይሰብክ የነበረው የፍርድ መልእክት ፍጻሜውን ሲያገኝ ዓመጸኛ የሆነው የእስራኤል ቤት ‘በመካከላቸው ነቢይ እንደነበር እንደሚያውቁ’ ይሖዋ አረጋግጦለት ነበር። (ሕዝ. 2:5) በተመሳሳይም አምላክ በዚህ ሥርዓት ላይ ፍርዱን ሲያስፈጽም ሰዎች፣ የይሖዋ ምሥክሮች በተለያዩ ቦታዎችና ከቤት ወደ ቤት ይሰብኩ የነበረው መልእክት ከእውነተኛው አምላክ ከይሖዋ የመጣ እንደሆነ እንዲሁም የይሖዋ ምሥክሮች የእሱ እውነተኛ ወኪሎች እንደነበሩ ለማስተዋል ይገደዳሉ። ታላቅ ትርጉም ያላቸው ክንውኖች በሚፈጸሙበት በዚህ ወቅት የይሖዋን ስም የመሸከምና መልእክቱን የማወጅ አስደናቂ መብት አግኝተናል! ከቤት ወደ ቤት በምናከናውነው አገልግሎት የሚያጋጥሙንን ተፈታታኝ ሁኔታዎች እሱ በሚሰጠን ኃይል እየተቋቋምን መስበካችንን እንቀጥል።

ምን ብለህ ትመልሳለህ?

• ለመስበክ የሚያስችል ድፍረት ማግኘት የምንችለው እንዴት ነው?

• ከቤት ወደ ቤት ስናገለግል መጽሐፍ ቅዱሳዊ ውይይት ለመጀመር ምን ሊረዳን ይችላል?

• ለሰዎች ከልብ እንደምናስብላቸው ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው?

• በአገልግሎት ክልላችን ውስጥ ለምናገኛቸው ሰዎች አዎንታዊ አመለካከት እንዲኖረን ምን ሊረዳን ይችላል?

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 9 ላይ የሚገኝ ሣጥን/ሥዕል]

መጽሐፍ ቅዱሳዊ ውይይት ለመጀመር የሚያስችል ዘዴ

ውይይቱን ለመጀመር፦

▪ የቤቱን ባለቤት ሰላም ካልከው በኋላ አንድ ትራክት በመስጠት እንዲህ ልትለው ትችላለህ:- “ዛሬ ቤትዎ የመጣሁት በዚህ አስፈላጊ የሆነ ርዕሰ ጉዳይ ዙሪያ አንድ አስደሳች ሐሳብ ላካፍልዎት ነው።”

▪ ወይም ደግሞ አንድ ትራክት ካሳየኸው በኋላ “በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ላይ ምን አመለካከት አለዎት?” ብለህ ልትጠይቅ ትችላለህ።

ግለሰቡ ትራክቱን ከወሰደ፦

▪ ጊዜ ሳታጠፋ በትራክቱ ርዕስ ላይ ተመሥርተህ የአመለካከት ጥያቄ አቅርብለት።

▪ የቤቱን ባለቤት አመለካከት ማወቅ እንድትችል በጥሞና አዳምጠው። ለሰጠው ሐሳብ አመስግነው፤ እንዲሁም በውይይታችሁ ውስጥ የእሱን ሐሳብ ከግምት እያስገባህ ተናገር።

ውይይቱን ለመቀጠል፦

▪ አንድ ወይም ከዚያ በላይ ጥቅሶች አንብብና ተወያዩባቸው፤ የምታቀርበውን ሐሳብ ግለሰቡ ከሚያሳስቡትና ከሚያስፈልጉት ነገሮች ጋር ለማስማማት ሞክር።

▪ ግለሰቡ ፍላጎት ካሳየ ጽሑፍ አበርክትለት፤ ሁኔታው የሚያመች ከሆነ መጽሐፍ ቅዱስን እንዴት ማጥናት እንደሚቻል አሳየው። በሌላ ጊዜ ተመልሰህ ለመምጣት ቀጠሮ ያዝ።