በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

አክብሮት በማሳየት ረገድ ቀዳሚ ነህ?

አክብሮት በማሳየት ረገድ ቀዳሚ ነህ?

አክብሮት በማሳየት ረገድ ቀዳሚ ነህ?

“አንዳችሁ ሌላውን ለማክበር ቀዳሚ ሁኑ።”—ሮሜ 12:10 NW

1. በብዙ የዓለም ክፍሎች እየቀረ የመጣው የትኛው ልማድ ነው?

በአንዳንድ የዓለም ክፍሎች ልጆች፣ በዕድሜ ከሚበልጧቸው ሰዎች አጠገብ በሚሆኑበት ጊዜ ከእነሱ ረዝመው ላለመታየት ሲሉ ይንበረከካሉ፤ ይህን የሚያደርጉት በዕድሜ ለሚበልጧቸው ሰዎች አክብሮት ለማሳየት ነው። በእነዚህ ማኅበረሰቦች ውስጥ አንድ ልጅ ለትልቅ ሰው ጀርባውን መስጠቱም አክብሮት የጎደለው ድርጊት እንደሆነ ተደርጎ ይቆጠራል። ሰዎች አክብሮት የሚያሳዩበት መንገድ እንደየባሕሉ የተለያየ ቢሆንም እነዚህ የአክብሮት መግለጫዎች የሙሴን ሕግ ያስታውሱናል። በሙሴ ሕግ ውስጥ “ዕድሜው ለገፋ [በአክብሮት] ተነሥለት፤ ሽማግሌውን አክብር” የሚል ትእዛዝ ይገኛል። (ዘሌ. 19:32) ሆኖም በብዙ ቦታዎች ለሌሎች አክብሮት ማሳየት እየቀረ መሆኑ የሚያሳዝን ነው። አክብሮት አለማሳየት በዛሬው ጊዜ የተለመደ ነገር ሆኗል።

2. የአምላክ ቃል እነማንን እንድናከብር ያዘናል?

2 የአምላክ ቃል፣ አክብሮት የማሳየትን አስፈላጊነት ጎላ አድርጎ ይገልጻል። መጽሐፍ ቅዱስ ይሖዋንና ኢየሱስን እንድናከብር ይነግረናል። (ዮሐ. 5:23) ከዚህም በተጨማሪ ለቤተሰባችን አባላትና ለእምነት ባልንጀሮቻችን አክብሮት እንድናሳይ ያዘናል፤ ከክርስቲያን ጉባኤ ውጭ ደግሞ ለአንዳንድ ሰዎች የተለየ አክብሮት እንድናሳይ ቀጥተኛ ምክር ሰጥቶናል። (ሮሜ 12:10፤ ኤፌ. 6:1, 2፤ 1 ጴጥ. 2:17) ይሖዋን እንደምናከብር የምናሳይባቸው አንዳንድ መንገዶች የትኞቹ ናቸው? ለክርስቲያን ወንድሞቻችንና እህቶቻችን አክብሮት ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው? እስቲ እነዚህንና ከእነዚህ ጋር ተዛማጅነት ያላቸው ሌሎች ጥያቄዎችን እንመርምር።

ለይሖዋ እንዲሁም ለስሙ አክብሮት አሳይ

3. ለይሖዋ አክብሮት የምናሳይበት ዋነኛው መንገድ ምንድን ነው?

3 ይሖዋን የምናከብርበት ዋነኛው መንገድ ለስሙ ተገቢውን አክብሮት በማሳየት ነው። የአምላክ ቃል ‘ለስሙ የሚሆን ወገን’ እንደሆንን ይናገራል። (ሥራ 15:14 የ1954 ትርጉም) በእርግጥም ሁሉን ቻይ አምላክ የሆነውን የይሖዋን ስም መሸከም ታላቅ ክብር ነው። ነቢዩ ሚክያስ እንዲህ ብሏል:- “አሕዛብ ሁሉ፣ በአማልክቶቻቸው ስም ይሄዳሉ፤ እኛ ግን በአምላካችን በእግዚአብሔር [“በይሖዋ፣” NW] ስም፣ ከዘላለም እስከ ዘላለም እንሄዳለን።” (ሚክ. 4:5) በዕለታዊ ሕይወታችን፣ የተሸከምነውን ስም በሚያስከብር መንገድ ለመኖር ጥረት በማድረግ ‘በይሖዋ ስም እንሄዳለን።’ ጳውሎስ በሮም የነበሩትን ክርስቲያኖች እንዳሳሰባቸው አኗኗራችን ከምንሰብከው የምሥራች ጋር የሚጋጭ ከሆነ የአምላክ ስም “ይሰደባል” ወይም ስሙ ይጎድፋል።—ሮሜ 2:21-24

4. ስለ ይሖዋ እንድትመሠክር የተሰጠህን መብት እንዴት ትመለከተዋለህ?

4 የስብከቱ ሥራችንም ለይሖዋ አክብሮት የምናሳይበት ሌላው መንገድ ነው። በጥንት ጊዜ ይሖዋ፣ ምሥክሮቹ እንዲሆኑ ለእስራኤላውያን አጋጣሚ ሰጥቷቸው ነበር፤ እነሱ ግን ይህንን ኃላፊነት አልተወጡም። (ኢሳ. 43:1-12) በተደጋጋሚ ጊዜያት በይሖዋ ላይ በማመፅ ‘የእስራኤልን ቅዱስ አስቈጥተውታል።’ (መዝ. 78:40, 41) የኋላ ኋላ የእስራኤል ብሔር የይሖዋን ሞገስ ሙሉ በሙሉ አጣ። በዛሬው ጊዜ የምንገኝ ክርስቲያኖች ግን ስለ ይሖዋ የመመሥከርና ስሙ እንዲታወቅ የማድረግ መብት በማግኘታችን አመስጋኞች ነን። ስለ ይሖዋ የምንመሠክረውም ሆነ ስሙ እንዲታወቅ የምናደርገው እሱን ስለምንወደውና ስሙ እንዲቀደስ ስለምንፈልግ ነው። ደግሞስ በሰማይ ስለሚኖረው አባታችንና ስለ ዓላማዎቹ እውነቱን እያወቅን ከመስበክ ወደኋላ ማለት እንዴት እንችላለን? እኛም “የምሰብከው ግዴታዬ ስለሆነ ነው፤ ወንጌልን ባልሰብክ ግን ወዮልኝ” ብሎ እንደተናገረው እንደ ሐዋርያው ጳውሎስ ይሰማናል።—1 ቆሮ. 9:16

5. በይሖዋ መታመን፣ ለእሱ አክብሮት ከማሳየት ጋር ተዛማጅነት የሚኖረው እንዴት ነው?

5 መዝሙራዊ ዳዊት “ስምህን የሚያውቁ ይታመኑብሃል፤ እግዚአብሔር [“ይሖዋ፣” NW] ሆይ፤ የሚሹህን አትተዋቸውምና” ብሏል። (መዝ. 9:10) ይሖዋን በደንብ የምናውቀውና ለስሙ አክብሮት የምናሳይ ከሆነ የጥንቶቹ ታማኝ አገልጋዮቹ እንዳደረጉት በእሱ እንታመናለን። በይሖዋ መታመናችንና በእሱ ላይ እምነት ማሳደራችን ለእሱ አክብሮት እንዳለን የምናሳይበት ሌላው መንገድ ነው። የአምላክ ቃል፣ በይሖዋ መታመንና እሱን ማክበር ያላቸውን ተዛማጅነት እንዴት እንደሚገልጸው ልብ በል። የጥንቶቹ እስራኤላውያን በይሖዋ ሳይታመኑ በመቅረታቸው ይሖዋ ሙሴን እንዲህ ሲል ጠይቆት ነበር:- “ይህ ሕዝብ እስከ መቼ ይንቀኛል? እነዚህን ሁሉ ታምራት በመካከሉ እያደረግሁ የማያምንብኝስ እስከ መቼ ነው?” (ዘኍ. 14:11) እኛ ግን ከእስራኤላውያን በተቃራኒ መከራዎች በሚያጋጥሙን ጊዜም እንኳ ይሖዋ ጥበቃ እንደሚያደርግልንና ለመጽናት እንደሚረዳን በመተማመን ለእሱ አክብሮት እንዳለን እናሳያለን።

6. ለይሖዋ ጥልቅ አክብሮት እንድናሳይ የሚያነሳሳን ምንድን ነው?

6 ኢየሱስ ለይሖዋ የምናሳየው አክብሮት ከልብ የመነጨ መሆን እንዳለበት ጠቁሟል። ከልብ ያልሆነ አምልኮ የሚያቀርቡ ሰዎችን በተመለከተ ይሖዋ “ይህ ሕዝብ በከንፈሩ ያከብረኛል፤ ልቡ ግን ከእኔ የራቀ ነው” ማለቱን ኢየሱስ ተናግሯል። (ማቴ. 15:8) ለይሖዋ እውነተኛ አክብሮት የምናሳየው ለእሱ ልባዊ ፍቅር ካለን ነው። (1 ዮሐ. 5:3) ከዚህም በላይ ይሖዋ “የሚያከብሩኝን አከብራለሁ” በማለት የገባውን ቃል አንዘነጋም።—1 ሳሙ. 2:30

የበላይ ተመልካቾች ለሌሎች አክብሮት አሳዩ

7. (ሀ) በኃላፊነት ቦታ ላይ ያሉ ወንድሞች በእነሱ ሥር ላሉት አክብሮት ማሳየት ያለባቸው ለምንድን ነው? (ለ) ጳውሎስ ለእምነት ባልንጀሮቹ አክብሮት ያሳየው እንዴት ነበር?

7 ሐዋርያው ጳውሎስ የእምነት ባልንጀሮቹን “አንዳችሁ ሌላውን ለማክበር ቀዳሚ ሁኑ” ብሏቸዋል። (ሮሜ 12:10 NW) በጉባኤ ውስጥ ኃላፊነት ያላቸው ወንድሞች በእነሱ ሥር ያሉትን ሰዎች በማክበር ረገድ ‘ቀዳሚ መሆን’ ይገባቸዋል። ከባድ ኃላፊነት ያለባቸው ወንድሞች በዚህ ረገድ የጳውሎስን ምሳሌ መኮረጅ ይኖርባቸዋል። (1 ተሰሎንቄ 2:7, 8ን አንብብ።) ጳውሎስ በጎበኛቸው ጉባኤዎች ውስጥ የነበሩት ወንድሞች፣ ይህ ሐዋርያ ራሱ ሊያደርገው የማይፈልገውን ነገር እነሱ እንዲያደርጉ ፈጽሞ እንደማይጠይቃቸው ያውቁ ነበር። ጳውሎስ ለእምነት ባልንጀሮቹ አክብሮት ያሳይ ስለነበር እነሱም አክብረውታል። ይህ ሐዋርያ፣ ጥሩ ምሳሌ የሚሆን ሰው በመሆኑ “እኔን እንድትመስሉ እለምናችኋለሁ” ብሎ በተናገረ ጊዜ ብዙዎች በፈቃደኝነት እንዲህ እንዳደረጉ እርግጠኞች መሆን እንችላለን።—1 ቆሮ. 4:16

8. (ሀ) ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ አክብሮት ያሳየበት አንዱ መንገድ የትኛው ነው? (ለ) በዛሬው ጊዜ የሚገኙ የበላይ ተመልካቾች የኢየሱስን ምሳሌ መኮረጅ የሚችሉት እንዴት ነው?

8 በጉባኤ ውስጥ ኃላፊነት ያለው አንድ ወንድም በእሱ ሥር ያሉትን እንደሚያከብር የሚያሳይበት ሌላው መንገድ ደግሞ ሌሎች እንዲሠሩ ለሚጠይቃቸው ነገሮችም ሆነ ለሚሰጣቸው መመሪያዎች ምክንያቱን በመናገር ነው። ይህ ወንድም እንዲህ በማድረግ ኢየሱስን ይኮርጃል። ለምሳሌ ኢየሱስ፣ በመከሩ ሥራ የሚሳተፉ ብዙ ሰዎች ለማግኘት እንዲጸልዩ ለደቀ መዛሙርቱ በነገራቸው ወቅት እንዲህ ያለበትን ምክንያት ገልጾላቸዋል። “መከሩ ብዙ ነው፤ የመከሩ ሠራተኞች ግን ጥቂቶች ናቸው፤ ስለዚህ የመከሩ ጌታ፣ ወደ መከሩ ሠራተኞችን እንዲልክ ለምኑት” ብሏቸዋል። (ማቴ. 9:37, 38) በተመሳሳይም “ነቅታችሁ ጠብቁ” የሚል ምክር ሲሰጣቸው ይህን ያለው ‘ጌታቸው የሚመጣበትን ቀን ስለማያውቁ’ መሆኑን ገልጾላቸዋል። (ማቴ. 24:42) ኢየሱስ በተደጋጋሚ ጊዜያት ለደቀ መዛሙርቱ ምን ማድረግ እንዳለባቸው ብቻ ሳይሆን ይህን ማድረግ ያለባቸው ለምን እንደሆነም ጭምር ይነግራቸው ነበር። በዚህ መንገድ አክብሮት አሳይቷቸዋል። ክርስቲያን የበላይ ተመልካቾች ሊከተሉት የሚገባ እንዴት ያለ ግሩም ምሳሌ ነው!

የይሖዋን ጉባኤና ጉባኤው የሚሰጠውን መመሪያ አክብር

9. ለዓለም አቀፉ የክርስቲያን ጉባኤ እንዲሁም ጉባኤውን ለሚወክሉት ወንድሞች አክብሮት ስናሳይ ማንን እያከበርን ነው? አብራራ።

9 ይሖዋን እንደምናከብር የምናሳይበት ሌላው መንገድ ደግሞ ዓለም አቀፉን የክርስቲያን ጉባኤ እንዲሁም ጉባኤውን የሚወክሉትን ወንድሞች ማክበር ነው። ታማኝና ልባም ባሪያ የሚሰጠውን ምክር ሰምተን ተግባራዊ ስናደርግ ለይሖዋ ዝግጅት አክብሮት እንዳለን እናሳያለን። ሐዋርያው ዮሐንስ፣ በመጀመሪያው መቶ ዘመን በነበረው የክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ ለተሾሙ ወንድሞች አክብሮት የማያሳዩ ግለሰቦችን መገሠጽ አስፈልጎት ነበር። (3 ዮሐንስ 9-11ን አንብብ።) ዮሐንስ የተናገረው ሐሳብ እንደሚያመለክተው እነዚህ ግለሰቦች፣ ለበላይ ተመልካቾች ብቻ ሳይሆን እነሱ ለሚያስተምሩት ትምህርትና ለሚሰጡት መመሪያም ጭምር አክብሮት አልነበራቸውም። የሚያስደስተው ግን እንዲህ ዓይነት አመለካከት የነበራቸው ሁሉም ክርስቲያኖች አይደሉም። በአጠቃላይ ሲታይ ሐዋርያት በሕይወት በነበሩበት ዘመን፣ ክርስቲያኖች አመራር ለሚሰጡት ወንድሞች ጥልቅ አክብሮት እንደነበራቸው ግልጽ ነው።—ፊልጵ. 2:12

10, 11. በክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ ለአንዳንዶች ሥልጣን መሰጠቱ ተገቢ መሆኑን የሚያሳዩ ምሳሌዎችን ከቅዱሳን መጻሕፍት ጥቀስ።

10 አንዳንዶች፣ ኢየሱስ “ሁላችሁም ወንድማማቾች ናችሁ” በማለት ስለተናገረ በክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ ለተወሰኑ ሰዎች ሥልጣን ሊሰጥ እንደማይገባ ይገልጻሉ። (ማቴ. 23:8) ይሁንና በዕብራይስጥም ሆነ በግሪክኛ ቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ አምላክ ሥልጣን ስለሰጣቸው ሰዎች የሚናገሩ በርካታ ምሳሌዎችን እናገኛለን። የእምነት አባቶችና የመሳፍንት እንዲሁም በዕብራውያን መካከል የነበሩት ነገሥታት ታሪክ፣ ይሖዋ በሰብዓዊ ወኪሎች አማካኝነት መመሪያ ይሰጥ እንደነበር የሚያሳይ በቂ ማስረጃ ነው። ሕዝቡ አምላክ ለሾማቸው ሰዎች ተገቢውን አክብሮት ባላሳዩባቸው ጊዜያት ይሖዋ ቀጥቷቸዋል።—2 ነገ. 1:2-17፤ 2:23, 24

11 በተመሳሳይም በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበሩት ክርስቲያኖች ሐዋርያት የነበራቸውን ሥልጣን ተቀብለዋል። (ሥራ 2:42) ለምሳሌ ያህል፣ ጳውሎስ ለክርስቲያን ወንድሞቹ መመሪያ ሰጥቷቸዋል። (1 ቆሮ. 16:1፤ 1 ተሰ. 4:2) ያም ቢሆን ጳውሎስ ከእሱ በላይ ሥልጣን ላላቸው ሰዎች በፈቃደኝነት ይታዘዝ ነበር። (ሥራ 15:22፤ ገላ. 2:9, 10) ከዚህ ለማየት እንደምንችለው ጳውሎስ በክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ ለነበረው ሥልጣን አክብሮት ነበረው።

12. ሥልጣንን በተመለከተ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ካሉት ምሳሌዎች የትኞቹን ሁለት ትምህርቶች እናገኛለን?

12 ከዚህ የምናገኘውን ትምህርት በሁለት ነጥቦች ማጠቃለል ይቻላል። አንደኛ፣ “ታማኝና ልባም ባሪያ” በበላይ አካሉ በኩል ወንዶችን በኃላፊነት ቦታ መሾሙ ቅዱስ ጽሑፋዊ ድጋፍ ያለው ነገር ነው፤ እንዲሁም አንዳንድ ወንድሞች፣ ኃላፊነት ባላቸው ሌሎች ወንድሞች ላይ ሥልጣን ይኖራቸዋል። (ማቴ. 24:45-47 የ1954 ትርጉም፤ 1 ጴጥ. 5:1-3) ሁለተኛ፣ የተሾሙ ወንድሞችን ጨምሮ ሁላችንም በእኛ ላይ ሥልጣን ያላቸውን ማክበር አለብን። ታዲያ በዓለም አቀፉ የክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ ኃላፊነት ላላቸው ወንድሞች አክብሮት ማሳየት የምንችለው በየትኞቹ መንገዶች ነው?

ለተጓዥ የበላይ ተመልካቾች አክብሮት ማሳየት

13. በዘመናችን ለሚገኙ የክርስቲያን ጉባኤ ተወካዮች አክብሮት እንዳለን እንዴት ማሳየት እንችላለን?

13 ጳውሎስ እንዲህ ብሏል:- “ወንድሞች ሆይ፤ በእናንተ መካከል በትጋት የሚሠሩትን፣ በጌታም የበላዮቻችሁና መካሪዎቻችሁ የሆኑትን እንድታከብሯቸው እንለምናችኋለን፤ ስለ ሥራቸውም በፍቅር እጅግ አክብሯቸው። እርስ በርሳችሁም በሰላም ኑሩ።” (1 ተሰ. 5:12, 13) “በትጋት የሚሠሩት” ከተባሉት መካከል ተጓዥ የበላይ ተመልካቾችም እንደሚገኙበት ምንም ጥርጥር የለውም። በመሆኑም ‘እጅግ ልናከብራቸው’ ይገባል። እንዲህ ማድረግ የምንችልበት አንደኛው መንገድ የሚሰጡንን ምክር ከልባችን በመቀበል ነው። እነዚህ የበላይ ተመልካቾች ታማኝና ልባም ባሪያ የሚሰጠንን መመሪያ ሲነግሩን “እሺ ባይ” በመሆን እንድንታዘዛቸው “ከሰማይ የሆነችው ጥበብ” ታነሳሳናለች።—ያዕ. 3:17

14. አንድ ጉባኤ፣ ለተጓዥ የበላይ ተመልካቾች እውነተኛ አክብሮት እንዳለው ማሳየት የሚችለው እንዴት ነው? ይህስ ምን ውጤት ያስገኛል?

14 አንድን ነገር ከዚህ በፊት እናከናውንበት ከነበረው በተለየ መንገድ እንድንሠራ መመሪያ ቢሰጠን ምን ማድረግ ይኖርብናል? አክብሮት የምናሳይ ከሆነ፣ “እዚህ ነገሮችን የምናከናውነው በዚህ መንገድ አይደለም” ወይም “ይህ ሐሳብ በሌላ ቦታ ጥሩ ሊሆን ቢችልም ለእኛ ጉባኤ ግን አይሠራም” እንደሚሉት ያሉ የተቃውሞ ሐሳቦችን ከመሰንዘር እንቆጠባለን። እንዲሁም የሚሰጠንን መመሪያ በተግባር ለማዋል ጥረት እናደርጋለን። ጉባኤው የይሖዋ እንደሆነና የጉባኤው ራስ ኢየሱስ መሆኑን ሁልጊዜ ማስታወሳችን የሚሰጡንን መመሪያዎች ተግባራዊ እንድናደርግ ይረዳናል። አንድ ጉባኤ፣ ተጓዥ የበላይ ተመልካቹ የሚሰጠውን መመሪያ በደስታ ተቀብሎ በሥራ ላይ የሚያውል ከሆነ እውነተኛ አክብሮት እንዳለው ያሳያል። በቆሮንቶስ የሚገኙት ወንድሞች፣ ክርስቲያን ሽማግሌ የሆነው ቲቶ በጎበኛቸው ወቅት የሰጣቸውን መመሪያ በአክብሮት በመታዘዛቸው ሐዋርያው ጳውሎስ አመስግኗቸዋል። (2 ቆሮ. 7:13-16) ዛሬም በተመሳሳይ ተጓዥ የበላይ ተመልካቾች የሚሰጡንን መመሪያ ተግባራዊ ለማድረግ ፈቃደኞች መሆናችን በስብከቱ ሥራ ደስታ እንድናገኝ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው እርግጠኞች መሆን እንችላለን።—2 ቆሮንቶስ 13:11ን አንብብ።

“ለሰው ሁሉ ተገቢውን አክብሮት ስጡ”

15. ለእምነት ባልንጀሮቻችን አክብሮት ማሳየት የምንችልባቸው አንዳንድ መንገዶች የትኞቹ ናቸው?

15 ጳውሎስ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “አረጋዊውን ሰው እንደ አባትህ ቈጥረህ ምከረው እንጂ በኀይለ ቃል አትናገረው። ወጣት ወንዶችን እንደ ወንድሞች ተቀበላቸው፤ እንዲሁም አሮጊቶችን እንደ እናቶች፣ ወጣት ሴቶችን ደግሞ እንደ እኅቶች በፍጹም ንጽሕና አስተናግዳቸው። በእርግጥ ችግረኛ የሆኑትን መበለቶች ተንከባከባቸው [“አክብራቸው፣” NW]።” (1 ጢሞ. 5:1-3) በእርግጥም፣ የአምላክ ቃል በክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ የሚገኙትን ሁሉ እንድናከብር ምክር ይሰጠናል። ይሁን እንጂ በጉባኤ ውስጥ በአንተና በአንድ ወንድም ወይም በአንዲት እህት መካከል አለመግባባት ቢፈጠርስ? ይህ መሆኑ ለእምነት ባልንጀራህ አክብሮት እንድታሳይ የተሰጠህን መመሪያ ላለመታዘዝ ምክንያት ሊሆንህ ይገባል? ወይስ ይህ የአምላክ አገልጋይ ያሉትን መንፈሳዊ ባሕርያት በማስተዋል አመለካከትህን ለማስተካከል ጥረት ማድረግ ትችላለህ? በተለይ የተሾሙ ወንድሞች ምንጊዜም ‘ለመንጋው’ አክብሮት ሊያሳዩ ይገባል እንጂ ፈጽሞ ‘በላያቸው መሠልጠን አይኖርባቸውም።’ (1 ጴጥ. 5:3) በእርግጥም፣ አባላቱ እርስ በርስ ባላቸው እውነተኛ ፍቅር ተለይቶ በሚታወቀው የክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ አንዳችን ለሌላው አክብሮት ማሳየት የምንችልባቸው በርካታ አጋጣሚዎች አሉ።—ዮሐንስ 13:34, 35ን አንብብ።

16, 17. (ሀ) ለምንሰብክላቸው ሰዎች ብቻ ሳይሆን ለተቃዋሚዎቻችንም ጭምር አክብሮት ማሳየታችን አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው? (ለ) “ለሰው ሁሉ ተገቢውን አክብሮት” መስጠት የምንችለው እንዴት ነው?

16 እርግጥ ነው፣ አክብሮት የምናሳየው ለክርስቲያን ጉባኤ አባላት ብቻ መሆን አይኖርበትም። ጳውሎስ በዘመኑ ለነበሩት ክርስቲያኖች “ዕድሉ ካለን ለሰው ሁሉ . . . መልካም እናድርግ” በማለት ጽፎላቸዋል። (ገላ. 6:10) የሥራ ባልደረባችን ወይም አብሮን የሚማር ልጅ ደግነት የጎደለው ድርጊት የሚፈጽምብን ከሆነ ይህን መሠረታዊ ሥርዓት ተግባራዊ ማድረግ ከባድ ሊሆንብን እንደሚችል አይካድም። እንዲህ ያለ ሁኔታ በሚያጋጥመን ጊዜ “ዐመፀኞችን በማየት አትሸበር” የሚለውን ምክር ማስታወስ ያስፈልገናል። (መዝ. 37:1) ይህንን ምክር ተግባራዊ ማድረጋችን ለተቃዋሚዎቻችን እንኳ ሳይቀር በአክብሮት መልስ ለመስጠት ያስችለናል። በተመሳሳይም በአገልግሎት ስንካፈል ትሑቶች መሆናችን ለሁሉም ሰው “በትሕትናና በአክብሮት” መልስ እንድንሰጥ ሊረዳን ይችላል። (1 ጴጥ. 3:15) ሌላው ቀርቶ አለባበሳችንና ውጫዊ ሁኔታችን እንኳ ለምንሰብክላቸው ሰዎች አክብሮት እንዳለን ሊጠቁም ይችላል።

17 በእርግጥም ከእምነት ባልንጀሮቻችንም ሆነ ከጉባኤው ውጪ ካሉ ሰዎች ጋር ባለን ግንኙነት ቀጥሎ የቀረበውን ምክር በተግባር ለማዋል ጥረት ማድረግ እንፈልጋለን:- “ለሰው ሁሉ ተገቢውን አክብሮት ስጡ፤ ወንድሞችን ውደዱ፤ እግዚአብሔርን ፍሩ፤ ንጉሥን አክብሩ።”—1 ጴጥ. 2:17

ምን ብለህ ትመልሳለህ?

• ለይሖዋ፣

• ለጉባኤ ሽማግሌዎችና ለተጓዥ የበላይ ተመልካቾች፣

• ለሁሉም የጉባኤ አባላት፣

• ለምንሰብክላቸው ሰዎች

ተገቢውን አክብሮት ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው?

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 23 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

የመጀመሪያው መቶ ዘመን ክርስቲያኖች የበላይ አካሉ ላለው ሥልጣን አክብሮት ነበራቸው

[በገጽ 24 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

በየትኛውም አገር የሚገኙ ሽማግሌዎች በበላይ አካሉ የተሾሙትን ተጓዥ የበላይ ተመልካቾች ያከብራሉ