በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ንጹሕ አቋምህን መጠበቅህ አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?

ንጹሕ አቋምህን መጠበቅህ አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?

ንጹሕ አቋምህን መጠበቅህ አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?

“ይሖዋ ሆይ፤ . . . እንደ ንጹሕ አቋሜ ፍረድልኝ።”—መዝ. 7:8 NW

1, 2. አንድ ክርስቲያን ንጹሕ አቋሙን መጠበቅ አስቸጋሪ እንዲሆንበት የሚያደርጉ አንዳንድ የተለመዱ ሁኔታዎች የትኞቹ ናቸው?

እስቲ የሚከተሉትን ሦስት ሁኔታዎች በአእምሮህ ለመሳል ሞክር። አንድ ልጅ አብረውት ከሚማሩት ልጆች መካከል የተወሰኑት እያሾፉበት ነው። ልጁ በንዴት ገንፍሎ እንዲሳደብ ወይም እንዲጣላ ለማድረግ እየተነኮሱት ነው። ይህ ልጅ አጸፋውን ይመልስ ይሆን ወይስ ራሱን በመግዛት ትቷቸው ይሄዳል? አንድ ባል ቤት ውስጥ ብቻውን ሆኖ በኢንተርኔት አማካኝነት ምርምር እያደረገ ሳለ የብልግና ምስሎች የሚታዩበትን ድረ ገጽ እንዲከፍት የሚጋብዝ መልእክት ኮምፒውተሩ ላይ ብቅ አለ። ይህ ሰው ድረ ገጹን ለመመልከት ተፈትኖ ይከፍተው ይሆን ወይስ ይህንን ድረ ገጽ ከመመልከት ይቆጠባል? አንዲት ክርስቲያን ሴት ደግሞ ከተወሰኑ እህቶች ጋር እየተጫወተች ሳለ ውይይቱ መልኩን ለውጦ በጉባኤያቸው ውስጥ የምትገኝ እህትን ማማት ተጀመረ። ይህች እህት ከእነሱ ጋር በመተባበር ሌሎችን ማማት ትጀምራለች ወይስ ርዕሱን ለመቀየር ጥረት ታደርጋለች?

2 እነዚህ ሦስት ሁኔታዎች የተለያዩ ቢሆኑም ሁሉንም የሚያመሳስላቸው አንድ ነገር አለ። ሦስቱም ሁኔታዎች ክርስቲያኖች ንጹሕ አቋማቸውን ለመጠበቅ የሚያደርጉትን ትግል ያሳያሉ። በሕይወትህ ውስጥ ከሚያሳስቡህና ከሚያስፈልጉህ ነገሮች እንዲሁም ከምታወጣቸው ግቦች ጋር በተያያዘ ንጹሕ አቋምህን ስለመጠበቅ ታስባለህ? ሰዎች ስለ መልካቸውና ስለ አለባበሳቸው፣ ስለ ጤንነታቸው፣ መተዳደሪያ ስለማግኘት እንዲሁም ከወዳጆቻቸው ጋር በተያያዘ ስለሚገጥሟቸው ጥሩና መጥፎ ሁኔታዎች ምናልባትም የፍቅር ግንኙነት ስለመመሥረት አዘውትረው ያስባሉ። እኛም እንደነዚህ ላሉት ሁኔታዎች ከፍተኛ ትኩረት እንሰጥ ይሆናል። ሆኖም ይሖዋ ልባችንን ሲመረምር በተለይ የሚያተኩረው በየትኛው ነገር ላይ ነው? (መዝ. 139:23, 24) ንጹሕ አቋማችንን ጠብቀን በመኖራችን ላይ ነው።

3. ይሖዋ ምን ምርጫ እንድናደርግ አጋጣሚ ሰጥቶናል? በዚህ ርዕስ ውስጥ የትኞቹን ነጥቦች እንመረምራለን?

3 ‘የበጎ ስጦታና የፍጹም በረከት ሁሉ’ ምንጭ የሆነው ይሖዋ ለእያንዳንዳችን የተለያዩ ስጦታዎችን ሰጥቶናል። (ያዕ. 1:17) ይሖዋ አካል፣ አእምሮና የተለያዩ ችሎታዎች እንዲሁም በተወሰነ መጠንም ቢሆን ጤንነት ስለሰጠን አመስጋኞች ነን። (1 ቆሮ. 4:7) ይሖዋ ንጹሕ አቋማችንን እንድንጠብቅ አያስገድደንም። ከዚህ ይልቅ በራሳችን ፍላጎት ይህንን ባሕርይ ለማዳበር እንድንመርጥ አጋጣሚ ይሰጠናል። (ዘዳ. 30:19) በመሆኑም ንጹሕ አቋም ሲባል ምን ማለት እንደሆነ መመርመራችን አስፈላጊ ነው። ከዚህም በተጨማሪ ንጹሕ አቋምን መጠበቅ በጣም አስፈላጊ የሆነባቸውን ሦስት ምክንያቶች እንመለከታለን።

ንጹሕ አቋም ሲባል ምን ማለት ነው?

4. ንጹሕ አቋም ሲባል ምን ነገሮችን ያካትታል? ይሖዋ የእንስሳት መሥዋዕትን አስመልክቶ ከሰጠው ሕግ ምን ትምህርት ማግኘት እንችላለን?

4 ንጹሕ አቋም ሲባል ምን ማለት እንደሆነ ለብዙ ሰዎች ግልጽ አይደለም። ለምሳሌ፣ ብዙውን ጊዜ ሰዎች ንጹሕ አቋምን መጠበቅ ሲባል ሐቀኛ መሆን ማለት ይመስላቸዋል። ሐቀኛ መሆን አስፈላጊ ቢሆንም ንጹሕ አቋምን መጠበቅ ግን ከዚህ የበለጠ ነገርን ይጨምራል። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከተሠራበት ሁኔታ አንጻር ንጹሕ አቋም የሚለው ሐሳብ፣ በሥነ ምግባር ረገድ እንከን የለሽ መሆንን እንዲሁም ጥሩ ሥነ ምግባር መያዝን ያካትታል። “ንጹሕ አቋም” ከሚለው ሐሳብ ጋር ተዛማጅነት ያላቸው የዕብራይስጥ ቃላት ጥሩ፣ ሙሉ ወይም እንከን የሌለበት የሚል መሠረታዊ ትርጉም አላቸው። ከእነዚህ ቃላት መካከል አንዱ ለይሖዋ ከሚቀርቡ መሥዋዕቶች ጋር በተያያዘ ተሠርቶበታል። ለመሥዋዕት የሚቀርብ አንድ እንስሳ በይሖዋ ዘንድ ተቀባይነት የሚያገኘው እንከን የሌለበት ከሆነ ብቻ ነበር። (ዘሌዋውያን 22:19, 20ን አንብብ።) ይሖዋ፣ ሆን ብለው ይህንን መመሪያ በመተላለፍ አንካሳ፣ በሽተኛ ወይም እውር እንስሳ መሥዋዕት አድርገው ያቀረቡ ሰዎችን አውግዟቸዋል።—ሚል. 1:6-8

5, 6. (ሀ) ብዙውን ጊዜ እንከን የሌለበትን ወይም ሙሉ የሆነውን ነገር ከፍ አድርገን እንደምንመለከት የትኞቹ ምሳሌዎች ያሳያሉ? (ለ) ፍጽምና የጎደላቸው ሰዎች ንጹሕ አቋማቸውን ይጠብቃሉ ሲባል ፍጹም መሆን አለባቸው ማለት ነው? አብራራ።

5 እንከን የሌለበትን ወይም ሙሉ የሆነውን ነገር መፈለግና እንዲህ ያለውን ነገር ከፍ አድርጎ መመልከት ያልተለመደ አይደለም። ለምሳሌ፣ መጻሕፍትን የሚያሰባስብ አንድ ሰው ለረጅም ጊዜ ሲፈልገው የነበረውን ትልቅ ቦታ የሚሰጠው መጽሐፍ አገኘ እንበል። ይሁንና መጽሐፉ አስፈላጊ የሆኑ በርካታ ገጾች እንደጎደሉት ሲመለከት በዚህ በመበሳጨት መጽሐፉን መደርደሪያው ላይ መልሶ ያስቀምጠው ይሆናል። እንቁላል ለመግዛት ገበያ የወጣችን አንዲት ሴት ደግሞ እንደ ምሳሌ እንውሰድ። ይህች ሴት የምትገዛው ምን ዓይነት እንቁላሎችን ነው? ያልተበላሹ ወይም እንከን የሌለባቸውን እንቁላሎች እንደምትገዛ ጥርጥር የለውም። በተመሳሳይም አምላክ የሚፈልገው እንከን የለሽ አቋም ያላቸውን ወይም በእሱ ፊት ልባቸው ፍጹም የሆነውን ሰዎች ነው።—2 ዜና 16:9

6 ‘ታዲያ ንጹሕ አቋምን ለመጠበቅ ፍጹም መሆን ያስፈልጋል ማለት ነው?’ የሚል ጥያቄ ይፈጠርብህ ይሆናል። ኃጢአተኞችና ፍጽምና የጎደለን በመሆናችን የተወሰኑ ገጾች እንደጎደሉት መጽሐፍ ወይም እንከን እንዳለበት እንቁላል እንደሆንን ይሰማን ይሆናል። አንተስ አንዳንድ ጊዜ እንደዚህ አይሰማህም? ይሖዋ ሙሉ በሙሉ ፍጹም እንድንሆን እንደማይጠብቅብን ማወቁ የሚያጽናና ነው። ፈጽሞ ከአቅማችን በላይ አይጠብቅብንም። * (መዝ. 103:14፤ ያዕ. 3:2) ያም ቢሆን ንጹሕ አቋማችንን ሳናጎድፍ እንድንኖር ይፈልግብናል። ታዲያ ፍጹም በመሆንና ንጹሕ አቋምን በመጠበቅ መካከል ልዩነት አለ ማለት ነው? አዎ አለ። ነጥቡን በምሳሌ ለማስረዳት ያህል፣ አንድ ወንድ ሊያገባት ያሰባትን ወጣት እንደሚወዳት የታወቀ ነው፤ ይህ ሲባል ግን ፍጹም እንድትሆን ይጠብቅባታል ማለት አይደለም። ያም ቢሆን በሙሉ ልቧ እንድትወደው ማለትም እሱን ብቻ እንድታፈቅረው መጠበቁ ተገቢ ነው። በተመሳሳይም ይሖዋ እሱ ብቻ እንዲመለክ የሚፈልግ “ቀናተኛ አምላክ” ነው። (ዘፀ. 20:5) ይሖዋ፣ ፍጹም እንድንሆን ባይጠብቅብንም በፍጹም ልባችን እንድንወደውና እሱን ብቻ እንድናመልከው ይፈልግብናል።

7, 8. (ሀ) ንጹሕ አቋምን በመጠበቅ ረገድ ኢየሱስ ምን ምሳሌ ትቷል? (ለ) ከቅዱሳን መጻሕፍት አንጻር ንጹሕ አቋም ምን ያመለክታል?

7 ኢየሱስ ከትእዛዛት ሁሉ የሚበልጠው የትኛው እንደሆነ በተጠየቀ ጊዜ የሰጠውን መልስ እናስታውስ ይሆናል። (ማርቆስ 12:28-30ን አንብብ።) ለቀረበለት ጥያቄ መልስ በመስጠት ብቻ ሳይወሰን ከተናገረው ሐሳብ ጋር በሚስማማ መንገድ ኖሯል። ይሖዋን በፍጹም ሐሳቡ፣ ልቡ፣ ነፍሱና ኃይሉ በመውደድ የላቀ ምሳሌ ትቷል። ኢየሱስ ንጹሕ አቋም የሚገለጸው በቃል ብቻ ሳይሆን በንጹሕ ልብ ተነሳስቶ መልካም ሥራዎችን በማከናወን እንደሆነ አሳይቷል። ንጹሕ አቋማችንን ለመጠበቅ የኢየሱስን ፈለግ መከተል ይኖርብናል።—1 ጴጥ. 2:21

8 በመሆኑም ከቅዱሳን መጻሕፍት አንጻር ንጹሕ አቋም፣ በሰማይ ለሚኖረው ለይሖዋ አምላክ ብቻ እንዲሁም ለፈቃዱና ለዓላማው በሙሉ ልብ ማደርን ያመለክታል። ንጹሕ አቋማችንን እንጠብቃለን ሲባል በዕለታዊ ሕይወታችን ይሖዋ አምላክን የሚያስደስተውን ነገር ከምንም ነገር በላይ ማስቀደም እንፈልጋለን ማለት ነው። በሕይወታችን ውስጥ ቅድሚያ የምንሰጠው ይሖዋ ከፍ አድርጎ ለሚመለከታቸው ነገሮች ነው። ንጹሕ አቋማችንን መጠበቅ በጣም አስፈላጊ የሆነባቸውን ሦስት ምክንያቶች እስቲ እንመልከት።

1. ንጹሕ አቋማችንና ከይሖዋ ሉዓላዊነት ጋር በተያያዘ የተነሳው ጉዳይ

9. በግለሰብ ደረጃ ንጹሕ አቋማችንን መጠበቃችን ከይሖዋ አጽናፈ ዓለማዊ ሉዓላዊነት ጋር በተያያዘ ከተነሳው ጉዳይ ጋር የሚዛመደው እንዴት ነው?

9 ይሖዋ ሉዓላዊ ገዥ መሆኑ እኛ ንጹሕ አቋማችንን በመጠበቃችን ላይ የተመካ አይደለም። ሉዓላዊነቱ ወይም አገዛዙ ፍትሕ የሰፈነበትና ዘላለማዊ ነው። እንዲሁም ይሖዋ በአጽናፈ ዓለም ሁሉ ላይ ሉዓላዊ ነው። የትኛውም ፍጥረት የሚናገረው ወይም የሚያደርገው ነገር ይህን ሐቅ አይለውጠውም። ያም ሆኖ በሰማይም ሆነ በምድር በአምላክ ሉዓላዊነት ላይ የሐሰት ክስ ተሰንዝሯል። በመሆኑም ይሖዋ ሉዓላዊ ገዥ መሆኑ ተገቢ እንደሆነ እንዲሁም አገዛዙ ትክክለኛና ፍቅር የሚንጸባረቅበት መሆኑ የማሰብ ችሎታ ባላቸው ፍጡራን ሁሉ ፊት መረጋገጥ ይኖርበታል። የይሖዋ ምሥክሮች እንደመሆናችን መጠን ለመስማት ፈቃደኛ ለሆኑ ሰዎች ሁሉ ስለ አምላክ አጽናፈ ዓለማዊ ሉዓላዊነት መናገር ያስደስተናል። በግለሰብ ደረጃስ የይሖዋን ሉዓላዊ ገዥነት መደገፍ የምንችለው እንዴት ነው? ይሖዋ ሉዓላዊ ገዥያችን እንዲሆን መምረጣችንን እንዴት ማሳየት እንችላለን? ይህንን የምናደርገው ንጹሕ አቋማችንን በመጠበቅ ነው።

10. ሰይጣን፣ የሰው ልጆች ንጹሕ አቋማቸውን ከመጠበቃቸው ጋር በተያያዘ ምን ክስ ሰንዝሯል? አንተስ ለዚህ ክስ ምን ምላሽ ትሰጣለህ?

10 ንጹሕ አቋምህን መጠበቅህ ከይሖዋ ሉዓላዊነት ጋር የሚያያዘው እንዴት እንደሆነ እንመልከት። ሰይጣን፣ ማንም ሰው የአምላክን ሉዓላዊነት እንደማይደግፍ እንዲሁም ከራስ ወዳድነት ነፃ በሆነ ፍቅር ተነሳስቶ ይሖዋን እንደማያገለግል በተዘዋዋሪ መንገድ ገልጿል። በርካታ ቁጥር ባላቸው መንፈሳዊ ፍጡራን ፊት ይሖዋን “‘ቍርበት ስለ ቍርበት ነው’ እንዲሉ ሰው ለሕይወቱ ሲል ያለውን ሁሉ ይሰጣል” ብሎታል። (ኢዮብ 2:4) ሰይጣን ይህንን ክስ የሰነዘረው ጻድቅ ሰው በነበረው በኢዮብ ላይ ብቻ ሳይሆን በጠቅላላው የሰው ዘር ላይ እንደሆነ ልብ በል። መጽሐፍ ቅዱስ፣ ሰይጣንን “የወንድሞቻችን ከሳሽ” በማለት የሚጠራው ለዚህ ነው። (ራእይ 12:10) ሰይጣን፣ አንተን ጨምሮ ሁሉም ክርስቲያኖች ታማኝነታቸውን ጠብቀው እንደማይኖሩ በመናገር በይሖዋ ላይ ስድብ ሰንዝሯል። ‘ቍርበትህን’ ማለትም ሕይወትህን ለማትረፍ ስትል ይሖዋን እንደምትክደው ተናግሯል። ሰይጣን በአንተ ላይ ስለሰነዘራቸው ስለነዚህ ክሶች ምን ይሰማሃል? ውሸታም መሆኑን ለማረጋገጥ የሚያስችልህ አጋጣሚ ብታገኝ አትደሰትም? ንጹሕ አቋምህን በመጠበቅ ሰይጣን ሐሰተኛ መሆኑን ማሳየት ትችላለህ።

11, 12. (ሀ) በዕለት ተዕለት ሕይወታችን የምናደርጋቸው ውሳኔዎች በግለሰብ ደረጃ ንጹሕ አቋማችንን ከመጠበቃችን ጋር እንደሚያያዙ የሚያሳዩት የትኞቹ ምሳሌዎች ናቸው? (ለ) ንጹሕ አቋምን መጠበቅ ልዩ መብት ነው የምንለው ለምንድን ነው?

11 እንግዲያው በዕለታዊ ሕይወትህ የምታከናውናቸው ነገሮችና የምታደርጋቸው ምርጫዎች ንጹሕ አቋምህን ከመጠበቅህ ጋር የተያያዙ ስለሆኑ ከፍተኛ ትኩረት ልትሰጣቸው ይገባል። በዚህ ርዕስ መግቢያ ላይ የተጠቀሱትን ሦስት ሁኔታዎች እስቲ መለስ ብለን እንመልከታቸው። እነዚህ ሰዎች ንጹሕ አቋማቸውን መጠበቅ የሚችሉት እንዴት ነው? አብረውት የሚማሩት ልጆች የሚያሾፉበት ወጣት በሁኔታው ተናዶ አጸፋውን ለመመለስ ቢፈተንም የሚከተለውን ምክር ያስታውሳል፦ “ወዳጆቼ ሆይ፤ ለእግዚአብሔር ቁጣ ፈንታ ስጡ እንጂ አትበቀሉ፤ ‘በቀል የእኔ ነው፤ እኔ ብድራትን እመልሳለሁ’ ይላል ጌታ ተብሎ ተጽፎአልና።” (ሮሜ 12:19) በመሆኑም ይህ ወጣት ልጆቹን ትቷቸው ይሄዳል። ኢንተርኔት ይጠቀም የነበረው ባል የብልግና ምስል የሚታይበትን ድረ ገጽ መመልከት የሚችል ቢሆንም ኢዮብ “ወደ ኰረዳዪቱ ላለመመልከት፣ ከዐይኔ ጋር ቃል ኪዳን ገብቻለሁ” በማለት በተናገረው ሐሳብ ላይ የሚገኘውን መሠረታዊ ሥርዓት ያስታውሳል። (ኢዮብ 31:1) ይህ ሰው የብልግና ምስሎችን እንደ መርዝ በመቁጠር እንደነዚህ ያሉ ነገሮችን ከመመልከት ይቆጠባል። ከጥቂት እህቶች ጋር ትጫወት የነበረችው ክርስቲያን ሴትም ሐሜት ስትሰማ “እያንዳንዳችን ባልንጀራችንን ለማነጽ፣ እርሱንም ለመጥቀም ደስ የሚያሰኘውን ነገር ማድረግ ይገባናል” የሚለውን መመሪያ በማስታወስ አንደበቷን ትቆጣጠራለች። (ሮሜ 15:2) ይህች እህት በሐሜቱ መካፈሏ የሚያንጽ አይደለም። እንዲህ ማድረጓ ሌሎች ለክርስቲያን እህቷ ጥሩ አመለካከት እንዳይኖራቸው የሚያደርግ ከመሆኑም በላይ በሰማይ የሚኖረውን አባቷን ያሳዝነዋል። ስለዚህ አንደበቷን በመቆጣጠር የውይይቱን ርዕስ ለመቀየር ጥረት ታደርጋለች።

12 በእነዚህ በሦስቱም ሁኔታዎች አንድ ክርስቲያን ‘ይሖዋ ገዢዬ ነው፤ ከዚህ ጉዳይ ጋር በተያያዘ እሱን የሚያስደስተውን ነገር ለማድረግ እጥራለሁ’ እንደሚል የሚያሳይ ምርጫ ያደርጋል። አንተስ አንዳንድ ምርጫዎችንና ውሳኔዎችን ስታደርግ ይሖዋን ለማስደሰት ትጥራለህ? እንዲህ የምታደርግ ከሆነ በምሳሌ 27:11 (የ1954 ትርጉም) ላይ ከሚገኘው “ልጄ ሆይ፣ ጠቢብ ሁን፣ ልቤንም ደስ አሰኘው፣ ለሚሰድበኝ መልስ መስጠት ይቻለኝ ዘንድ” ከሚለው ሐሳብ ጋር ተስማምተህ እየኖርክ ነው። የአምላክን ልብ ማስደሰት መቻላችን በእርግጥም እንዴት ያለ ታላቅ መብት ነው! ታዲያ ይህን ማወቃችን ንጹሕ አቋማችንን ለመጠበቅ የምንችለውን ሁሉ እንድናደርግ አያነሳሳንም?

2. ለመለኮታዊ ፍርድ መሠረት ነው

13. ኢዮብና ዳዊት የተናገሯቸው ሐሳቦች ይሖዋ የሚፈርድልን በንጹሕ አቋማችን መሠረት መሆኑን የሚያሳዩት እንዴት ነው?

13 ንጹሕ አቋማችንን መጠበቅ የይሖዋን ሉዓላዊነት ለመደገፍ እንደሚያስችለን ተመልክተናል። በመሆኑም አምላክ የሚፈርድልን ንጹሕ አቋማችንን መሠረት በማድረግ ነው። ኢዮብ ይህንን እውነታ በሚገባ ተገንዝቦ ነበር። (ኢዮብ 31:6ን አንብብ።) አምላክ፣ ንጹሕ አቋማችንን ጠብቀን እንደምንኖር ለማረጋገጥ ፍጹም በሆነው የፍትሕ መሥፈርቱ አማካኝነት የሰውን ዘር በሙሉ “በእውነተኛ ሚዛን” እንደሚመዝን ኢዮብ ያውቅ ነበር። ዳዊትም በተመሳሳይ እንዲህ ብሏል፦ “ይሖዋ ራሱ በሕዝቦች ላይ ይፈርዳል። ይሖዋ ሆይ፤ እንደ ጽድቄና እንደ ንጹሕ አቋሜ ፍረድልኝ። . . . ጻድቅ የሆነው አምላክ ልባችንንና ኵላሊታችንን ይመረምራል።” (መዝ. 7:8, 9 NW) አምላክ የአንድን ሰው ‘ልብና ኵላሊት’ ማለትም ውስጣዊ ማንነቱን መመልከት እንደሚችል እናውቃለን። ሆኖም ይሖዋ ለምን እንደሚመለከተን ማስታወስ ይኖርብናል። ዳዊት እንደገለጸው ይሖዋ የሚፈርድልን በንጹሕ አቋማችን መሠረት ነው።

14. ፍጽምና የጎደለንና ኃጢአተኞች መሆናችን ንጹሕ አቋማችንን እንዳንጠብቅ እንቅፋት እንደሚሆንብን ማሰብ የሌለብን ለምንድን ነው?

14 ይሖዋ አምላክ በዛሬው ጊዜ የሚኖሩ በቢሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎችን ልብ ሲመረምር በዓይነ ሕሊናህ ይታይህ። (1 ዜና 28:9) ክርስቲያናዊ ንጹሕ አቋሙን የሚጠብቅ ምን ያህል ሰው ያገኛል? ብዙ ሰው አያገኝም! ያም ቢሆን ግን ፍጹም አለመሆናችን ንጹሕ አቋማችንን ለመጠበቅ እንቅፋት እንደሚሆንብን ማሰብ አይኖርብንም። ዳዊትና ኢዮብ፣ ይሖዋ ንጹሕ አቋማቸውን እንደጠበቁ አድርጎ እንደሚመለከታቸው እርግጠኞች ነበሩ። እኛም ፍጹማን ባንሆንም ይሖዋ እንደዚህ አድርጎ እንደሚመለከተን ለመተማመን የሚያስችል በቂ ምክንያት አለን። አንድ ሰው ፍጹም ስለሆነ ብቻ ንጹሕ አቋሙን ይጠብቃል ማለት እንደማይቻል አስታውስ። በምድር ላይ የኖሩት ፍጹም ሰዎች ሦስት ብቻ ሲሆኑ ሁለቱ ማለትም አዳምና ሔዋን ንጹሕ አቋማቸውን አልጠበቁም። በሌላ በኩል ግን በብዙ ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ፍጽምና የጎደላቸው ሰዎች ንጹሕ አቋማቸውን ጠብቀዋል። አንተም ንጹሕ አቋምህን መጠበቅ ትችላለህ።

3. ለተስፋችን በጣም አስፈላጊ ነው

15. ዳዊት፣ ንጹሕ አቋማችንን መጠበቃችን ለተስፋችን በጣም አስፈላጊ መሆኑን ያሳየው እንዴት ነው?

15 ይሖዋ የሚፈርድልን ንጹሕ አቋማችንን መሠረት አድርጎ ስለሆነ እንዲህ ያለ አቋም መያዛችን ለተስፋችን በጣም አስፈላጊ ነው። ዳዊት ይህን ያውቅ ነበር። (መዝሙር 41:12ን በNW አንብብ። *) ይህ የአምላክ አገልጋይ ለዘላለም የአምላክን ሞገስ የማግኘት ተስፋ ነበረው። በዛሬው ጊዜ እንዳሉት እውነተኛ ክርስቲያኖች ሁሉ ዳዊትም ይሖዋ አምላክን በማገልገልና ከእሱ ጋር ያለውን ዝምድና ይበልጥ እያጠናከረ በመሄድ ለዘላለም ለመኖር ተስፋ ያደርግ ነበር። ዳዊት ይህ ተስፋው ሲፈጸም ለማየት ከፈለገ ንጹሕ አቋሙን ጠብቆ መኖር እንዳለበት ያውቅ ነበር። በተመሳሳይ እኛም ንጹሕ አቋማችንን ስንጠብቅ ይሖዋ ይደግፈናል፣ ያስተምረናል፣ ይመራናል እንዲሁም ይባርከናል።

16, 17. (ሀ) ምንጊዜም ቢሆን ንጹሕ አቋምህን ጠብቀህ ለመኖር ቁርጥ ውሳኔ ማድረግ ያለብህ ለምንድን ነው? (ለ) በሚቀጥለው ርዕስ ላይ የትኞቹ ጥያቄዎች ይብራራሉ?

16 ተስፋ በአሁኑ ጊዜም ደስተኞች እንድንሆን ይረዳናል። አስቸጋሪ ሁኔታዎችን ለመቋቋም የሚያስፈልገንን ደስታ የሚሰጠን ከመሆኑም ባሻገር አስተሳሰባችንን ሊጠብቅልን ይችላል። መጽሐፍ ቅዱስ ተስፋን ከራስ ቊር ጋር እንደሚያመሳስለው አስታውስ። (1 ተሰ. 5:8) የራስ ቊር፣ በውጊያ ላይ ያለ አንድ ወታደር በጭንቅላቱ ላይ ጉዳት እንዳይደርስበት እንደሚከላከልለት ሁሉ ተስፋም ሊጠፋ በተቃረበው በዚህ አሮጌ ዓለም ውስጥ ሰይጣን በሚያስፋፋው ጎጂና አፍራሽ አስተሳሰብ እእምሯችን እንዳይበከል ይከላከልልናል። ተስፋ ከሌለን ሕይወታችን ትርጉም ያጣል። በመሆኑም ንጹሕ አቋማችንን ምን ያህል እንደምንጠብቅና ተስፋችን ምን ያህል ጠንካራ እንደሆነ ለማወቅ ራሳችንን በሐቀኝነት መመርመር ይኖርብናል። ንጹሕ አቋምህን ስትጠብቅ የይሖዋን ሉዓላዊነት እየደገፍክ እንዲሁም ድንቅ የሆነው የወደፊት ተስፋህ እውን እንዲሆን እያደረግህ መሆኑን አትዘንጋ። ምንጊዜም ቢሆን ንጹሕ አቋምህን ጠብቀህ እንድትኖር እንመኛለን!

17 ንጹሕ አቋማችንን መጠበቃችን በጣም አስፈላጊ በመሆኑ አንዳንድ ተጨማሪ ጥያቄዎችን መመርመር ያስፈልገናል። ንጹሕ አቋም መያዝ የምንችለው እንዴት ነው? ንጹሕ አቋማችንን ጠብቀን ለመኖር ምን ማድረግ እንችላለን? አንድ ሰው በሆነ ወቅት ላይ ንጹሕ አቋሙን ቢያጎድፍ ምን ማድረግ ይኖርበታል? የሚቀጥለው ርዕስ ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ ይሰጣል።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.6 እርግጥ ነው፣ ኢየሱስ “የሰማይ አባታችሁ ፍጹም እንደ ሆነ እናንተም ፍጹማን ሁኑ” ብሏል። (ማቴ. 5:48) ኢየሱስ፣ ፍጽምና የጎደላቸው ሰዎችም እንኳ በአንጻራዊ ሁኔታ ሙሉ ወይም ፍጹም መሆን እንደሚችሉ ተገንዝቦ ነበር። በእርግጥም ሰውን ሁሉ እንድንወድ የተሰጠንን ትእዛዝ መፈጸም እንችላለን፤ እንዲህ በማድረግም አምላክን እናስደስታለን። ከእኛ በተቃራኒ ግን ይሖዋ ሙሉ በሙሉ ፍጹም ነው። “ንጹሕ አቋም” የሚለው ቃል ከይሖዋ ጋር በተያያዘ ሲሠራበት ፍጹም መሆንንም ይጨምራል።—መዝ. 18:30

^ አን.15 መዝሙር 41:12 (NW)፦ “ንጹሕ አቋሜን በመጠበቄ ደግፈህ ያዝኸኝ። በፊትህም ለዘላለም ታኖረኛለህ።”

ምን ብለህ ትመልሳለህ?

• ንጹሕ አቋም ሲባል ምን ማለት ነው?

• ንጹሕ አቋምን መጠበቅ ከአጽናፈ ዓለም ሉዓላዊነት ጋር በተያያዘ ከተነሳው ጉዳይ ጋር የሚዛመደው እንዴት ነው?

• ንጹሕ አቋም ለተስፋችን መሠረት የሚሆነው እንዴት ነው?

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 5 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ንጹሕ አቋማችንን ጠብቀን መኖር አስቸጋሪ እንዲሆንብን የሚያደርጉ በርካታ ነገሮች በየዕለቱ ያጋጥሙናል