በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ሚስዮናውያኑ የኤርምያስን ምሳሌ እንዲኮርጁ ማበረታቻ ተሰጣቸው

ሚስዮናውያኑ የኤርምያስን ምሳሌ እንዲኮርጁ ማበረታቻ ተሰጣቸው

125ኛው የጊልያድ ምረቃ

ሚስዮናውያኑ የኤርምያስን ምሳሌ እንዲኮርጁ ማበረታቻ ተሰጣቸው

“መቶ ሃያ አምስተኛው የጊልያድ ክፍል [በትምህርት ቤቱ] ታሪክ ውስጥ ጉልህ ስፍራ የሚሰጠው ነው”፤ ይህን የተናገረው የበላይ አካል አባል የሆነው ወንድም ጄፍሪ ጃክሰን ነበር። ወንድም ጃክሰን ንግግሩን ያቀረበው መስከረም 13, 2008 በተካሄደው የጊልያድ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ቤት የ125ኛው ክፍል የምረቃ ፕሮግራም ላይ ለተገኙት 6,156 ተሰብሳቢዎች ነበር። የጊልያድ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ቤት በዚያን ዕለት የተመረቁትን 56 ተማሪዎች ጨምሮ ከ8,000 በላይ ሚስዮናውያንን “እስከ ምድር ዳር ድረስ” ልኳል!—ሥራ 1:8

የምረቃ ፕሮግራሙ ሊቀ መንበር የሆነው ወንድም ጃክሰን “እምነት የሚጣልባችሁ መሆናችሁ በአገልግሎታችሁ ይበልጥ ውጤታማ እንድትሆኑ ይረዳችኋል?” የሚል ጥያቄ ካቀረበ በኋላ ሚስዮናውያኑ እምነት የሚጣልባቸው እንዲሆኑ የሚረዷቸውን አራት ነጥቦች ጠቀሰ። እነዚህም፦ ትክክለኛ አመለካከት ማዳበር፣ ጥሩ ምሳሌ መሆን፣ ሙሉ በሙሉ በአምላክ ቃል ላይ የተመሠረተ ትምህርት ማስተማር እንዲሁም የይሖዋን ስም በማሳወቅ ላይ ትኩረት ማድረግ ናቸው።

በትምህርት ኮሚቴ ውስጥ የሚያገለግለው ወንድም ዴቪድ ሼፈር “ሁሉን ነገር መረዳት ትችሉ ይሆን?” በሚል ርዕስ ቀጣዩን ንግግር አቀረበ። ወንድም ሼፈር ተማሪዎቹ፣ ይሖዋን መፈለጋቸውን ከቀጠሉ እንዲሁም ‘የታማኝና ልባም ባሪያን’ መመሪያ በትሕትና ከታዘዙ ሚስዮናውያን ሆነው ለማገልገል የሚያስፈልጋቸውን ‘ሁሉ ማስተዋል’ ወይም መረዳት እንደሚችሉ ገለጸላቸው።—ምሳሌ 28:5 የ1954 ትርጉምማቴ. 24:45

ቀጥሎም የበላይ አካል አባል የሆነው ወንድም ጆን ባር “ምንም ነገር ከአምላክ ፍቅር እንዲለያችሁ አትፍቀዱ” የሚል ርዕስ ያለው ንግግር አቀረበ። ወንድም ባር፣ አዲሶቹ ሚስዮናውያን በሚመደቡበት ቦታ የሚያጋጥማቸውን ሁኔታ በተመለከተ ተመራቂዎቹና ወላጆቻቸው የሚኖራቸውን ስጋት የሚያስወግድ አባታዊ ማበረታቻ ሰጥቷል። ወንድም ባር “በአምላክ ፍቅር ውስጥ መሆን ስጋት የሌለበት የተረጋጋ ሕይወት ለመምራት ያስችለናል” ብሏል። ሚስዮናውያኑ ራሳቸውን ከአምላክ ካልለዩ በቀር ማንኛውም ነገር ከይሖዋ ፍቅር ሊለያቸው አይችልም።

ቲኦክራሲያዊ ትምህርት ቤቶችን በሚከታተለው ክፍል ውስጥ የሚሠራው ወንድም ሳም ሮበርሰን፣ አድማጮቹ “የክት ልብሳቸውን” እንዲለብሱ አበረታቷቸዋል። ተመራቂዎቹ ኢየሱስ ያከናወናቸውን ነገሮች በማጥናትና ያወቁትን ነገር በሕይወታቸው ውስጥ ተግባራዊ በማድረግ “ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን [መልበስ]” ይችላሉ። (ሮም 13:14) ቀጥሎ ደግሞ ቲኦክራሲያዊ ትምህርት ቤቶችን የሚከታተለው ክፍል የበላይ ተመልካች የሆነው ወንድም ዊልያም ሳሙኤልሰን፣ አንድን ሰው የሚያስከብረው ምን እንደሆነ አብራራ። አንድን ሰው የተከበረ እንዲሆን የሚያደርገው ሰዎች ለእሱ ያላቸው አመለካከት ሳይሆን ግለሰቡ በአምላክ ዘንድ ያለው ስም ነው።

የጊልያድ ትምህርት ቤት መምህር የሆነው ወንድም ማይክል በርኔት፣ ተማሪዎቹ በአገልግሎት ላይ ስላገኟቸው ተሞክሮዎች ቃለ መጠይቅ አደረገላቸው። ተማሪዎቹ በፓተርሰን፣ ኒው ዮርክ ባለው የጊልያድ ትምህርት ቤት በነበሩበት ወቅት አብዛኞቹ እንዲያገለግሉ የተመደቡት በተደጋጋሚ ጊዜያት በተሸፈኑ ክልሎች ውስጥ ቢሆንም ፍላጎት ያላቸው ሰዎችን አግኝተዋል። በአውራጃ ስብሰባ ጽሕፈት ቤት ውስጥ የሚያገለግለው ወንድም ጄራልድ ግሪዝል በቅርንጫፍ ቢሮ ኮሚቴ አባላት ትምህርት ቤት እየተካፈሉ ካሉ ሦስት ወንድሞች ጋር ቃለ ምልልስ አደረገ። እነዚህ ወንድሞች የሰጡት ሐሳብ የጊልያድ ተመራቂዎች በሚመደቡባቸው አገሮች ለሚያጋጥማቸው ሁኔታ እንዲዘጋጁ ረድቷቸዋል።

“የኤርምያስን ምሳሌ ኮርጁ” የሚለውን ንግግር ያቀረበው የበላይ አካል አባልና የጊልያድ ትምህርት ቤት የ42ኛው ክፍል ተመራቂ የሆነው ወንድም ዴቪድ ስፕሌን ነበር። ኤርምያስ የተሰጠውን ተልዕኮ ለመቀበል ብቃት እንደሌለው ተሰምቶት የነበረ ቢሆንም ይሖዋ አበረታትቶታል። (ኤር. 1:7, 8) አምላክ አዲሶቹን ሚስዮናውያንም እንዲሁ ያበረታታቸዋል። ወንድም ስፕሌን እንደሚከተለው በማለት ተናግሯል፦ “በእናንተና በአንድ ሰው መካከል አለመግባባት ሲፈጠር ይህ ግለሰብ ካሉት ባሕርያት ውስጥ በጣም የምትወዷቸውን አሥር ባሕርያት ጻፉ። አሥር ባሕርያት መጻፍ ካልቻላችሁ ግለሰቡን በደንብ አታውቁትም ማለት ነው።”

ኤርምያስ የራሱን ጥቅም መሥዋዕት ያደርግ ነበር። አገልግሎቱን ለማቆም ሲያስብ ስለ ጉዳዩ ወደ ይሖዋ የጸለየ ሲሆን ይሖዋም አልተወውም። (ኤር. 20:11) ወንድም ስፕሌን እንዲህ ብሏል፦ “ተስፋ የመቁረጥ ስሜት ሲሰማችሁ ያሳሰባችሁን ነገር ለይሖዋ ንገሩት። ይሖዋ እንዴት እንደሚረዳችሁ ስትመለከቱ መደነቃችሁ አይቀርም።”

በምረቃ ፕሮግራሙ መደምደሚያ ላይ ሊቀ መንበሩ፣ ተመራቂዎቹ እምነት የሚጣልባቸው ሰዎች ለመሆን የሚረዷቸውን በርካታ ነጥቦች እንደተማሩ ተናገረ። ተመራቂዎቹ እምነት የሚጣልባቸው መሆናቸው በተመደቡበት ቦታ ሲያገለግሉ መልእክታቸው ተቀባይነት እንዲኖረው አስተዋጽኦ ያደርጋል።—ኢሳ. 43:8-12

[በገጽ 22 ላይ የሚገኝ ሣጥን]

ተማሪዎቹን የሚመለከት አኃዛዊ መረጃ

ተማሪዎቹ የተውጣጡባቸው አገሮች ብዛት፦ 6

የተመደቡባቸው አገሮች ብዛት፦ 21

የተማሪዎቹ ብዛት፦ 56

አማካይ ዕድሜ፦ 32.9

በእውነት ውስጥ የቆዩባቸው ዓመታት በአማካይ፦ 17.4

በሙሉ ጊዜ አገልግሎት የቆዩባቸው ዓመታት በአማካይ፦ 13

[በገጽ 23 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

የጊልያድ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ቤት የ125ኛው ክፍል ተመራቂዎች

ከዚህ በታች ባለው ዝርዝር ለእያንዳንዱ ረድፍ ቁጥር የተሰጠው ከፊት ወደኋላ ሲሆን ስሞቹ የሰፈሩት ከግራ ወደ ቀኝ ነው።

(1) ኤጂ ሆጅሰን፣ አና ዎል፣ ክሪስቲና በርንስ፣ ማሪያ ሆርቴላኖ፣ ሌስሊ ኒውመን፣ አና ዲካሶ (2) ጄኒፈር ጄንኪንስ፣ ታምዌላ ጃርዝምስኪ፣ ናንሲ ሜንዴዝ፣ ቪየና ኮሮና፣ ለይላ ካናሊታ (3) ሂዘር ፍራየር፣ ሜላኒ ሳቨጅ፣ ኪም ቲድዌል፣ ኒኪያ ኤሪክሰን፣ ኤስተር ዳይክ፣ ሬቤካ ማክቤዝ (4) ላሊ ፔሬዝ፣ ሊሳ ፑዝ፣ አምበር ስኪድሞር፣ ቤሊንዳ ያንግ፣ ኒኮል ማክብራይድ፣ ፓውላ ሮንደን፣ ኤሪካ ጉድመን (5) ሚሻ በርንስ፣ ጄሲካ ፈርግሰን፣ ናታሻ ፒርሰን፣ ሊሳ ቻፕማን፣ ጄኒፈር ዎርድል፣ ማይክል ካናሊታ (6) ፓብሎ ፔሬዝ፣ ዳንየል ዲካሶ፣ ታይሰን ያንግ፣ ዴቪድ ሮንደን፣ ጋርዝ ጉድመን፣ ማይክል ጄንኪንስ፣ ጎርደን ዳይክ (7) ማሪዮ ኮሮና፣ ራየን ዎል፣ ጅስኮት ፑዝ፣ ፍሎርያን ሜንዴዝ፣ ስኮት ጃርዝምስኪ፣ ቶም ሳቨጅ (8) ክርስቲያን ኒውመን፣ ዶናልድ ፈርግሰን፣ ድሩ ስኪድሞር፣ ታይሰን ኤሪክሰን፣ ጃቮን ማክብራይድ፣ ማርክ ፒርሰን፣ ማቲው ቻፕማን (9) ኬሪ ሆጅሰን፣ አልስተር ዎርድል፣ አዳም ማክቤዝ፣ ትሬቨር ቲድዌል፣ ጆሹዋ ፍራየር፣ ጆናታን ሆርቴላኖ