በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ኢየሱስ ያስተማራቸው ነገሮች ደስታ የሚያስገኙት እንዴት ነው?

ኢየሱስ ያስተማራቸው ነገሮች ደስታ የሚያስገኙት እንዴት ነው?

ኢየሱስ ያስተማራቸው ነገሮች ደስታ የሚያስገኙት እንዴት ነው?

“[ኢየሱስ] ወደ ተራራ ወጣ፤ . . . በኋላም ደቀ መዛሙርቱ ወደ እሱ መጡ፤ . . . [እሱም] ያስተምራቸው ጀመር።”—ማቴ. 5:1, 2

1, 2. (ሀ) ኢየሱስ በተራራ ላይ ሆኖ ሲሰብክ የነበረው ሁኔታ ምን ይመስል ነበር? (ለ) ኢየሱስ የተራራ ስብከቱን የጀመረው ምን በመግለጽ ነበር?

ወቅቱ 31 ከክርስቶስ ልደት በኋላ ነው፤ ኢየሱስ በገሊላ እየተዘዋወረ መስበኩን ለተወሰነ ጊዜ አቋርጦ የፋሲካን በዓል ለማክበር ወደ ኢየሩሳሌም ሄደ። (ዮሐ. 5:1) ወደ ገሊላ ከተመለሰ በኋላ 12ቱን ሐዋርያት ለመምረጥ አምላክ መመሪያ እንዲሰጠው ሌሊቱን ሙሉ ሲጸልይ አደረ። በቀጣዩ ቀን ኢየሱስ ሕመምተኞችን ሲፈውስ ብዙ ሰዎች ወደ እሱ መጡ። ከዚያም ደቀ መዛሙርቱና ሌሎች ሰዎች በዙሪያው ሲሰበሰቡ አንድ ተራራ ላይ ተቀምጦ ያስተምራቸው ጀመር።—ማቴ. 4:23 እስከ 5:2፤ ሉቃስ 6:12-19

2 ኢየሱስ የተራራ ስብከቱን የጀመረው ደስታ የሚገኘው ከአምላክ ጋር ጥሩ ዝምድና በመመሥረት እንደሆነ በመግለጽ ነው። (ማቴዎስ 5:1-12ን አንብብ።) ደስታ የሚለው ቃል ‘ፍስሃ፣ ሐሴት’ የሚል ፍቺ ተሰጥቶታል። ኢየሱስ ደስታ እንደሚያስገኙ የገለጻቸው ዘጠኝ ነጥቦች ክርስቲያኖች ደስተኛ የሚሆኑበትን ምክንያት ያጎላሉ፤ እነዚህ ነጥቦች ከዛሬ 2,000 ዓመት በፊት እንደነበሩት ሁሉ ዛሬም ጠቃሚ ናቸው። እስቲ ኢየሱስ ያስተማራቸውን ነገሮች አንድ በአንድ እንመልከት።

“በመንፈሳዊ ድሆች መሆናቸውን የሚያውቁ”

3. በመንፈሳዊ ድሆች መሆናችንን ማወቅ ሲባል ምን ማለት ነው?

3 “በመንፈሳዊ ድሆች መሆናቸውን የሚያውቁ ደስተኞች ናቸው፤ መንግሥተ ሰማያት የእነሱ ነውና።” (ማቴ. 5:3) “በመንፈሳዊ ድሆች መሆናቸውን የሚያውቁ” ሰዎች የአምላክ መመሪያና ምሕረት እንደሚያስፈልጋቸው ይገነዘባሉ።

4, 5. (ሀ) በመንፈሳዊ ድሆች መሆናቸውን የሚያውቁ ሰዎች ደስተኞች ናቸው የምንለው ለምንድን ነው? (ለ) መንፈሳዊ ፍላጎታችንን ማርካት የምንችለው እንዴት ነው?

4 በመንፈሳዊ ድሆች መሆናቸውን የሚያውቁ ሰዎች “መንግሥተ ሰማያት የእነሱ [በመሆኑ]” ደስተኞች ናቸው። የመጀመሪያዎቹ የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት ኢየሱስ መሲሕ መሆኑን መቀበላቸው በሰማይ ባለው የአምላክ መንግሥት ከእሱ ጋር የመግዛት አጋጣሚ ከፍቶላቸዋል። (ሉቃስ 22:28-30) ተስፋችን ከክርስቶስ ጋር በሰማይ መግዛትም ይሁን በአምላክ መንግሥት ሥር በምድር ላይ በገነት ለዘላለም መኖር፣ በመንፈሳዊ ድሆች እንደሆንንና የአምላክ መመሪያ እንደሚያስፈልገን የምንገነዘብ ከሆነ ደስተኞች መሆን እንችላለን።

5 በመንፈሳዊ ድሆች መሆናቸውን የሚያውቁት ሁሉም ሰዎች አይደሉም፤ ብዙ ሰዎች እምነት የሌላቸው ከመሆኑም ሌላ ቅዱስ ነገሮችን አያደንቁም። (2 ተሰ. 3:1, 2፤ ዕብ. 12:16) መንፈሳዊ ፍላጎታችንን ለማርካት ከሚረዱን መንገዶች አንዳንዶቹ መጽሐፍ ቅዱስን በትጋት ማጥናት፣ ደቀ መዛሙርት በማድረጉ ሥራ በቅንዓት መካፈል እንዲሁም በክርስቲያናዊ ስብሰባዎች ላይ አዘውትሮ መገኘት ናቸው።—ማቴ. 28:19, 20፤ ዕብ. 10:23-25

የሚያዝኑ “ደስተኞች” ናቸው

6. “የሚያዝኑ” የተባሉት እነማን ናቸው? “ደስተኞች” እንዲሆኑ ያስቻላቸውስ ምንድን ነው?

6 “የሚያዝኑ ደስተኞች ናቸው፤ መጽናኛ ያገኛሉና።” (ማቴ. 5:4) “የሚያዝኑ” የተባሉት ሰዎች “በመንፈሳዊ ድሆች መሆናቸውን የሚያውቁ” ከተባሉት ጋር ተመሳሳይ አመለካከት አላቸው። እነዚህ ሰዎች የሚያዝኑት በኑሯቸው ስለሚማረሩ አይደለም። የሚያዝኑት ኃጢአተኛ በመሆናቸውና የሰው ዘር ፍጽምና የጎደለው መሆኑ ባስከተላቸው ችግሮች የተነሳ ነው። እነዚህ ሰዎች “ደስተኞች” እንዲሆኑ ያስቻላቸው ምንድን ነው? በአምላክና በክርስቶስ እንደሚያምኑ በተግባር ስለሚያሳዩ እንዲሁም ከይሖዋ ጋር ጥሩ ዝምድና መመሥረታቸው ስለሚያጽናናቸው ነው።—ዮሐ. 3:36

7. ስለ ሰይጣን ዓለም ምን አመለካከት ሊኖረን ይገባል?

7 የሰይጣን ዓለም በክፋት የተሞላ በመሆኑ ታዝናለህ? ይህ ዓለም ሊሰጠን የሚችለውን ነገር በተመለከተ ምን ይሰማሃል? ሐዋርያው ዮሐንስ እንዲህ ሲል ጽፏል፦ “በዓለም ያለው ነገር ሁሉ ይኸውም የሥጋ ምኞት፣ የዓይን አምሮትና ኑሮዬ ይታይልኝ የሚል መንፈስ . . . ከአብ የሚመነጭ አይደለም።” (1 ዮሐ. 2:16) ይሁንና ‘የዓለም መንፈስ’ ማለትም ከአምላክ የራቀውን የሰው ዘር ማኅበረሰብ የሚቆጣጠረው ኃይል መንፈሳዊነታችንን እያዳከመው እንደሆነ ከተሰማን ምን ማድረግ ይኖርብናል? ሁኔታችን እንዲህ ከሆነ አጥብቀን መጸለይ፣ የአምላክን ቃል ማጥናትና የሽማግሌዎችን እርዳታ መጠየቅ ይኖርብናል። የሚረብሸን ነገር ምንም ይሁን ምን ወደ ይሖዋ ስንቀርብ ‘መጽናናት’ እንችላለን።—1 ቆሮ. 2:12፤ መዝ. 119:52፤ ያዕ. 5:14, 15

“ገሮች” ምንኛ ደስተኞች ናቸው!

8, 9. ገር መሆን ሲባል ምን ማለት ነው? ገሮች ደስተኞች እንደሆኑ የተገለጸውስ ለምንድን ነው?

8 “ገሮች ደስተኞች ናቸው፤ ምድርን ይወርሳሉና።” (ማቴ. 5:5) “ገርነት” ወይም የዋህነት የድክመት ምልክት አይደለም፤ አሊያም ለይስሙላ ገር መሆንን አያመለክትም። (1 ጢሞ. 6:11) ገሮች ከሆንን የይሖዋን ፈቃድ በመፈጸምና አመራሩን በመቀበል የዋህ መሆናችንን እናሳያለን። በተጨማሪም ገርነት ከእምነት ባልንጀሮቻችንም ሆነ ከሌሎች ጋር ባለን ግንኙነት ይታያል። እንዲህ ያለው የየዋህነት ዝንባሌ ሐዋርያው ጳውሎስ ከሰጠው ምክር ጋር ይስማማል።—ሮም 12:17-19ን አንብብ።

9 ታዲያ “ገሮች ደስተኞች ናቸው” የተባለው ለምንድን ነው? ገር የሆነው ኢየሱስ እንደተናገረው ‘ምድርን ስለሚወርሱ’ ነው። በዋነኝነት ምድርን የሚወርሰው ኢየሱስ ነው። (መዝ. 2:8፤ ማቴ. 11:29፤ ዕብ. 2:8, 9) ‘ከክርስቶስ ጋር የሚወርሱት’ ገር የሆኑ ክርስቲያኖችም ከእሱ ጋር ምድርን ይወርሳሉ። (ሮም 8:16, 17) በምድር ላይ የሚኖሩት የኢየሱስ መንግሥት ተገዢዎች የሆኑ በርካታ ገር ሰዎች ደግሞ የዘላለም ሕይወት ያገኛሉ።—መዝ. 37:10, 11

10. ገር አለመሆን በጉባኤ ውስጥ ልናገኝ የምንችለውን የአገልግሎት መብት የሚያሳጣን እንዴት ነው? ከሌሎች ጋር ያለንን ግንኙነትስ የሚነካው እንዴት ነው?

10 እንደ ኢየሱስ ሁሉ እኛም ገሮች ልንሆን ይገባል። ይሁን እንጂ የጠበኝነት ዝንባሌ ካለን ምን ማድረግ ይኖርብናል? ቁጣና ጥላቻ የሚንጸባረቅበት እንዲህ ያለው ዝንባሌ ሰዎች እንዲርቁን ሊያደርግ ይችላል። በጉባኤ ውስጥ ኃላፊነት እንዲኖራቸው የሚፈልጉ ወንድሞች እንዲህ ዓይነት ዝንባሌ ካላቸው ኃላፊነት ለመቀበል ብቁ አይሆኑም። (1 ጢሞ. 3:1, 3) ቲቶ በቀርጤስ የሚኖሩ ክርስቲያኖችን “ጠበኞች እንዳይሆኑ፣ ምክንያታዊ እንዲሆኑና ለሰው ሁሉ ገርነትን ሁሉ እንዲያሳዩ” መምከሩን እንዲቀጥል ጳውሎስ አሳስቦታል። (ቲቶ 3:1, 2) በእርግጥም እንዲህ ዓይነት ገርነት የሚያሳይ ሰው ለሌሎች በረከት ነው!

“ጽድቅን” ይራባሉ

11-13. (ሀ) ጽድቅን መራብና መጠማት ሲባል ምን ማለት ነው? (ለ) ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ ሰዎች ‘የሚጠግቡት’ እንዴት ነው?

11 “ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ ደስተኞች ናቸው፤ ይጠግባሉና።” (ማቴ. 5:6) እዚህ ላይ ኢየሱስ “ጽድቅ” ሲል ከአምላክ ፈቃድና ትእዛዝ ጋር የሚስማማ አካሄድ በመከተል ትክክል የሆነውን ነገር ማድረግን ማመልከቱ ነበር። መዝሙራዊው ጽድቅ የሚንጸባረቅባቸውን የአምላክ ደንቦች ‘በመናፈቅ፣ እጅግ እንደዛለ’ ተናግሯል። (መዝ. 119:20) ጽድቅን እጅግ ከፍ አድርገን በመመልከት ጽድቅን እንራባለን ወይም እንጠማለን?

12 ኢየሱስ ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ ሰዎች ‘ስለሚጠግቡ’ ወይም ስለሚረኩ ደስተኞች እንደሚሆኑ ተናግሯል። በ33 ከክርስቶስ ልደት በኋላ በተከበረው የጴንጤቆስጤ በዓል ላይ የይሖዋ ቅዱስ መንፈስ “ስለ ጽድቅ . . . ለዓለም አሳማኝ ማስረጃ [ማቅረብ]” ስለጀመረ ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ መርካት ችለዋል። (ዮሐ. 16:8) አምላክ፣ ሰዎች የክርስቲያን ግሪክኛ ቅዱሳን መጻሕፍትን እንዲጽፉ በመንፈስ ቅዱስ የመራቸው ሲሆን እነዚህ መጻሕፍት “በጽድቅ ለመምከር” በጣም ጠቃሚ ናቸው። (2 ጢሞ. 3:16) በተጨማሪም የአምላክ መንፈስ “እንደ አምላክ ፈቃድ የተፈጠረውንና ከእውነተኛ ጽድቅ  . . ጋር የሚስማማውን አዲሱን ስብዕና መልበስ” እንድንችል ይረዳናል። (ኤፌ. 4:24) ንስሐ የሚገቡና በኢየሱስ ቤዛዊ መሥዋዕት አማካኝነት ኃጢአታቸው ይቅር እንዲባልላቸው የሚፈልጉ ሰዎች በአምላክ ፊት ጻድቅ ተደርገው መታየት የሚችሉ መሆናቸውን ማወቁ የሚያጽናና አይደለም?—ሮም 3:23, 24ን አንብብ።

13 ተስፋችን በምድር ላይ መኖር ከሆነ ለጽድቅ ያለን ረሃብና ጥማት ሙሉ በሙሉ የሚረካው ጽድቅ በሰፈነበት ምድር ላይ የዘላለም ሕይወት ስናገኝ ነው። እስከዚያው ድረስ ግን ከይሖዋ መመሪያዎች ጋር በሚስማማ መንገድ ለመኖር ቁርጥ ውሳኔ እናድርግ። ኢየሱስ “ከሁሉ አስቀድማችሁ የአምላክን መንግሥትና ጽድቅ መፈለጋችሁን ቀጥሉ” ብሏል። (ማቴ. 6:33) ይህም የአምላክ ሥራ የበዛልን እንድንሆንና ልባችን በደስታ እንዲሞላ ያደርጋል።—1 ቆሮ. 15:58

“መሐሪዎች” ደስተኞች የሆኑበት ምክንያት

14, 15. ምሕረት ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው? “መሐሪዎች” ደስተኞች እንደሆኑ የተገለጸው ለምንድን ነው?

14 “መሐሪዎች ደስተኞች ናቸው፤ ምሕረት ይደረግላቸዋልና።” (ማቴ. 5:7) “መሐሪዎች” ለሌሎች ይራራሉ እንዲሁም ያዝናሉ። ኢየሱስ ለታመሙ ሰዎች ያዝን ስለነበር በተአምራዊ መንገድ ፈውሷቸዋል። (ማቴ. 14:14) ይሖዋ ንስሐ ለሚገቡ ሰዎች ምሕረት በማሳየት ይቅር እንደሚላቸው ሁሉ ሰዎችም የበደሏቸውን ይቅር በማለት ምሕረት ማሳየት ይችላሉ። (ዘፀ. 34:6, 7፤ መዝ. 103:10) ከላይ እንደተገለጸው የበደሉንን ይቅር በማለት እንዲሁም ደግነት በሚንጸባረቅበት ንግግርና ድርጊት የተቸገሩ ሰዎች እረፍት እንዲያገኙ በመርዳት ምሕረት ማሳየት እንችላለን። የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት ለሌሎች ማካፈል ምሕረት ማሳየት የሚቻልበት ግሩም መንገድ ነው። ኢየሱስ በዙሪያው ለተሰበሰቡት ሰዎች ስላዘነላቸው ‘ብዙ ነገር እንዳስተማራቸው’ መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል።—ማር. 6:34

15 ኢየሱስ “መሐሪዎች ደስተኞች ናቸው፤ ምሕረት ይደረግላቸዋልና” ሲል ከተናገረው ሐሳብ ጋር ለመስማማት የሚያበቃ ምክንያት አለን። ለሌሎች ምሕረት የምናሳይ ከሆነ እነሱም በምላሹ እንዲሁ ያደርጉልናል። ለሌሎች ምሕረት ካሳየን በአምላክ ፊት ለፍርድ በምንቀርብበት ጊዜ እሱም ምሕረት ሊያደርግልን ይችላል። (ያዕ. 2:13) ኃጢአታቸው ይቅር የሚባልላቸውና የዘላለም ሕይወት የሚያገኙት መሐሪ የሆኑ ሰዎች ብቻ ናቸው።—ማቴ. 6:15

“ልባቸው ንጹሕ የሆነ” ደስተኞች የሆኑበት ምክንያት

16. ‘ልበ ንጹሕ’ መሆን ሲባል ምን ማለት ነው? ልባቸው ንጹሕ የሆነ ሰዎች ‘አምላክን የሚያዩት’ እንዴት ነው?

16 “ልባቸው ንጹሕ የሆነ ደስተኞች ናቸው፤ አምላክን ያያሉና።” (ማቴ. 5:8) ‘ልባችን ንጹሕ’ ከሆነ የምንወደው ነገር፣ ፍላጎታችንና ዝንባሌያችን ንጹሕ ይሆናል። እንዲሁም “ከንጹሕ ልብ . . . የሚመነጭ ፍቅር” ይኖረናል። (1 ጢሞ. 1:5) ውስጣችን ንጹሕ በመሆኑ ‘አምላክን እናየዋለን።’ እርግጥ ነው፣ “ማንም [አምላክን] አይቶ መኖር ስለማይችል” ይሖዋን ቃል በቃል እናየዋለን ማለት አይደለም። (ዘፀ. 33:20) ኢየሱስ የአምላክን ባሕርያት ፍጹም በሆነ መንገድ ስላንጸባረቀ “እኔን ያየ አብንም አይቷል” ብሎ መናገር ችሏል፤ በመሆኑም አምላክን ማየት የምንችልበት አንዱ መንገድ ኢየሱስን በማየት ነው። (ዮሐ. 14:7-9) በምድር ላይ የምንገኝ የይሖዋ አምላኪዎች እንደመሆናችን መጠን ‘አምላክን ማየት’ የምንችለው ለእኛ ሲል ያደረጋቸውን ነገሮች በመመልከትም ጭምር ነው። (ኢዮብ 42:5) ቅቡዓን ክርስቲያኖች ትንሣኤ አግኝተው መንፈሳዊ ሕይወት ሲሰጣቸው በሰማይ ያለውን አባታቸውን ቃል በቃል ያዩታል።—1 ዮሐ. 3:2

17. ልባችን ንጹሕ መሆኑ ምን እንድናደርግ ያነሳሳናል?

17 ንጹሕ ልብ ያለው ሰው በሥነ ምግባርም ሆነ በመንፈሳዊ ሁኔታ ንጹሕ ስለሆነ በይሖዋ ፊት ርኩስ በሆኑ ነገሮች ላይ አያውጠነጥንም። (1 ዜና 28:9፤ ኢሳ. 52:11) ልባችን ንጹሕ ከሆነ የምንናገረውም ሆነ የምናደርገው ነገር ንጹሕ ይሆናል፤ እንዲሁም ለይሖዋ የምናቀርበው አገልግሎት የይስሙላ አይሆንም።

“ሰላም ፈጣሪዎች” የአምላክ ልጆች ይሆናሉ

18, 19. “ሰላም ፈጣሪ” የሆኑ ሰዎች ምን ያደርጋሉ?

18 “ሰላም ፈጣሪዎች ደስተኞች ናቸው፤ ‘የአምላክ ልጆች’ ይባላሉና።” (ማቴ. 5:9) “ሰላም ፈጣሪዎች” በሥራቸው ተለይተው ይታወቃሉ። ኢየሱስ ከላይ ያለውን ሲናገር ያሰባቸው ዓይነት ሰዎች ከሆንን ሰላም ፈጣሪዎች እንሆናለን፤ እንዲሁም ‘በማንም ላይ በክፉ ፋንታ ክፉ አንመልስም።’ ከዚህ በተቃራኒ ‘ለሌሎች ሰዎች ምንጊዜም መልካም የሆነውን ነገር ለማድረግ እንጣጣራለን።’—1 ተሰ. 5:15

19 “ሰላም ፈጣሪዎች” ከተባሉት መካከል ለመሆን ሰላም እንዲኖር የምንጥር ሰዎች መሆን አለብን። “ሰላም ፈጣሪ” የሆኑ ሰዎች ‘የቅርብ ወዳጆችን የሚለያይ’ ምንም ነገር አያደርጉም። (ምሳሌ 16:28) ሰላም ፈጣሪዎች በመሆን “ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ለመኖር” የሚያስፈልገውን ሁሉ እናደርጋለን።—ዕብ. 12:14

20. በአሁኑ ጊዜ “የአምላክ ልጆች” የሚባሉት እነማን ናቸው? ወደፊት እነማንም ጭምር የአምላክ ልጆች ይሆናሉ?

20 ሰላም ፈጣሪ የሆኑ ሰዎች ‘“የአምላክ ልጆች” ስለሚባሉ’ ደስተኞች ናቸው። ይሖዋ፣ ታማኝ የሆኑ ቅቡዓን ክርስቲያኖችን እንደ ልጆቹ አድርጎ ስለተቀበላቸው “የአምላክ ልጆች” ናቸው። እነዚህ ክርስቲያኖች በክርስቶስ እንደሚያምኑ በተግባር ስለሚያሳዩ እንዲሁም “የፍቅርና የሰላም አምላክ” የሆነውን ይሖዋን በሙሉ ልባቸው ስለሚያመልኩት በአሁኑ ጊዜም ቢሆን ከይሖዋ ጋር የአባትና የልጅ ያህል የጠበቀ ወዳጅነት አላቸው። (2 ቆሮ. 13:11፤ ዮሐ. 1:12) ሰላም ፈጣሪ የሆኑትን የኢየሱስ “ሌሎች በጎች” በተመለከተስ ምን ማለት ይቻላል? ኢየሱስ ለሺህ ዓመት በሚገዛበት ወቅት ለበጎቹ “የዘላለም አባት” ይሆንላቸዋል፤ ሺህ ዓመቱ ሲያበቃ ግን ኢየሱስ ራሱን ለይሖዋ የሚያስገዛ ሲሆን በጎቹም ሙሉ በሙሉ የአምላክ ልጆች ይሆናሉ።—ዮሐ. 10:16፤ ኢሳ. 9:6፤ ሮም 8:21፤ 1 ቆሮ. 15:27, 28

21. “በመንፈስ የምንኖር ከሆነ” ምን እናደርጋለን?

21 “በመንፈስ የምንኖር ከሆነ” ሰላም ፈጣሪ መሆናችን በግልጽ ይታያል። ‘በመካከላችን የፉክክር መንፈስ አናነሳሳም’ ወይም ‘አንዳችን ሌላውን ለጥል አናነሳሳም።’ (ገላ. 5:22-26የ1980 ትርጉም) ከዚህ በተቃራኒ “ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ለመኖር” እንጥራለን።—ሮም 12:18

ስደት ቢደርስባቸውም ደስተኞች ናቸው!

22-24. (ሀ) ለጽድቅ ሲሉ የሚሰደዱ ሰዎች ደስተኞች እንዲሆኑ ያስቻላቸው ምንድን ነው? (ለ) በሚቀጥሉት ሁለት የጥናት ርዕሶች ውስጥ ምን እንመረምራለን?

22 “ለጽድቅ ሲሉ ስደት የሚደርስባቸው ደስተኞች ናቸው፤ መንግሥተ ሰማያት የእነሱ ነውና።” (ማቴ. 5:10) ኢየሱስ ይህንን ሐሳብ የበለጠ ሲያብራራው እንዲህ ብሏል፦ “በእኔ ምክንያት ሰዎች ሲነቅፏችሁ፣ ስደት ሲያደርሱባችሁና ክፉውን ሁሉ በውሸት ሲያስወሩባችሁ ደስተኞች ናችሁ። በሰማያት ያለው ሽልማታችሁ ታላቅ ስለሆነ ሐሴት አድርጉ፣ በደስታም ፈንጥዙ፤ ከእናንተ በፊት የነበሩትን ነቢያት እንደዚሁ ስደት አድርሰውባቸው ነበርና።”ማቴ. 5:11, 12

23 በጥንት ዘመን እንደነበሩት የአምላክ ነቢያት ሁሉ በዛሬው ጊዜ ያሉ ክርስቲያኖችም “ለጽድቅ ሲሉ” ሊነቀፉና ሊሰደዱ እንዲሁም የውሸት ወሬ ሊወራባቸው እንደሚችል ያውቃሉ። ሆኖም እንዲህ ያሉትን ፈተናዎች ተቋቁመን በታማኝነት ከጸናን ይሖዋን እንደምናስደስተውና እንደምናስከብረው ስለምናውቅ እርካታ እናገኛለን። (1 ጴጥ. 2:19-21) የሚደርስብን መከራ፣ አሁንም ሆነ ወደፊት ይሖዋን በማገልገል የምናገኘውን ደስታ ሊቀንስብን አይችልም። ፈተናዎች፣ በሰማይ ባለው መንግሥት ከክርስቶስ ጋር መግዛትም ሆነ የዚህ መንግሥት ምድራዊ ተገዢዎች በመሆን የዘላለም ሕይወት ማግኘት የሚያመጣውን ደስታም ሊቀንሱት አይችሉም። እነዚህ በረከቶች የአምላክን ሞገስ እንዳገኘን የሚያሳዩ ከመሆናቸውም ሌላ የደግነቱና የልግስናው መግለጫዎች ናቸው።

24 ከተራራው ስብከት መማር የምንችላቸው ሌሎች ብዙ ነገሮችም አሉ። በቀጣዮቹ ሁለት የጥናት ርዕሶች ውስጥ በርካታ ትምህርቶች ይብራራሉ። ኢየሱስ ያስተማራቸውን ነገሮች እንዴት ተግባራዊ ማድረግ እንደምንችል እንመለከታለን።

ምን ብለህ ትመልሳለህ?

• “በመንፈሳዊ ድሆች መሆናቸውን የሚያውቁ” ሰዎች ደስተኞች እንደሆኑ የተገለጸው ለምንድን ነው?

• “ገሮች” ደስተኞች እንዲሆኑ ያስቻላቸው ምንድን ነው?

• ክርስቲያኖች ስደት ቢደርስባቸውም ደስተኞች መሆን የቻሉት ለምንድን ነው?

• ኢየሱስ ደስታ እንደሚያስገኙ ከገለጻቸው ነጥቦች መካከል አንተን የማረከህ የትኛው ነው?

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 7 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ኢየሱስ ደስታ እንደሚያስገኙ የገለጻቸው ዘጠኝ ነጥቦች ከዛሬ 2,000 ዓመት ገደማ በፊት እንደነበሩት ሁሉ ዛሬም ጠቃሚ ናቸው

[በገጽ 8 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት ለሌሎች ማካፈል ምሕረት ማሳየት የሚቻልበት ግሩም መንገድ ነው