በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የሕይወትን ትርጉም ማግኘት ችያለሁ

የሕይወትን ትርጉም ማግኘት ችያለሁ

የሕይወትን ትርጉም ማግኘት ችያለሁ

ጋስፓር ማርቲኔስ እንደተናገረው

ታሪኬን በአጭሩ ባወጋችሁ፣ እኔ ወደ ከተማ በመሄድ ሀብታም ለመሆን የበቃሁ ድሃ የገጠር ልጅ ነኝ። ይሁንና ከትረካው እንደምትረዱት ያከማቸሁት ሀብት መጀመሪያ ከጠበቅሁት የተለየ ነው።

በ1930ዎቹ አካባቢ በሰሜናዊ ስፔን በሚገኘው በሪኦሃ ግዛት እንኖር ነበር፤ ያደግሁት በገጠር ሲሆን አካባቢውም ጠፍ ነበር። አሥር ዓመት ሲሆነኝ ትምህርቴን ማቋረጥ ግድ ሆነብኝ፤ እርግጥ በወቅቱ ማንበብና መጻፍ ተምሬ ነበር። ከስድስት ወንድሞቼና እህቶቼ ጋር በመሆን በጎችን እናግድ ወይም አነስተኛ የሆነውን የእርሻ ቦታችንን እናለማ ነበር።

ድሆች መሆናችን ለቁሳዊ ነገሮች ከፍተኛ ቦታ እንድንሰጥ አድርጎን ነበር። ከእኛ የበለጠ ሀብት ባላቸው ሰዎች እንቀና ነበር። እንደዚያም ሆኖ በአንድ ወቅት ቄሱ በእሱ ሥር ካሉት “መንደሮች ሁሉ ይልቅ ሃይማኖተኛ የሆነው የእኛ መንደር እንደሆነ” ተናግሮ ነበር። ይህ ቄስ ከጊዜ በኋላ በርካታ ሰዎች የካቶሊክን ሃይማኖት እንደሚተዉ የሚያውቀው ነገር አልነበረም።

የተሻለ ነገር ለማግኘት የተደረገ ፍለጋ

መርሴዲስ የተባለች በእኛ መንደር ውስጥ የምትኖር አንዲት ወጣት አገባሁ። ብዙም ሳይቆይ ወንድ ልጅ ወለድን። በ1957 ሎግሮኞ ወደተባለው በአቅራቢያችን የሚገኝ ከተማ ተዛወርን፤ ውሎ አድሮ ሁሉም ቤተሰቦቼ ወደዚህ ከተማ መጡ። ብዙም ሳይቆይ ግን የሠለጠንኩበት ሙያ ስለሌለኝ ጥሩ ደመወዝ የሚያስገኝ ሥራ የመያዝ አጋጣሚዬ የመነመነ እንደሆነ ተገነዘብኩ። መመሪያ ለማግኘት ወደ የት ዞር ማለት እንዳለብኝ ግራ ገባኝ። መመሪያ ሊሆነኝ የሚችለው ነገር ምን እንደሆነ በትክክል ባላውቅም በአካባቢያችን በሚገኘው ቤተ መጻሕፍት ውስጥ የሚገኙትን መጻሕፍት ማገላበጥ ጀመርኩ።

ከጊዜ በኋላ በተልእኮ ትምህርት አማካኝነት የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት መከታተል እንደሚቻል የሚገልጽ የሬዲዮ ፕሮግራም እንዳለ ሰማሁ። ይህንን ትምህርት እንዳጠናቀቅሁ አንዳንድ የኢቫንጀሊካን ፕሮቴስታንቶች አነጋገሩኝ። ወደ አምልኮ ቦታቸው ለተወሰነ ጊዜ ያህል ከሄድኩ በኋላ በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ ትልቅ ቦታ ባላቸው ሰዎች መካከል ፉክክር እንዳለ ተመለከትኩ። ከዚያ በኋላ ተመልሼ አልሄድኩም፤ ሁሉም ሃይማኖቶች እንደዚህ እንደሆኑ ተሰማኝ።

ዓይኖቼ ተከፈቱ

በ1964 ኤኡሄኒዮ የተባለ ወጣት ወደ ቤታችን መጣ። ይህ ወጣት የይሖዋ ምሥክር ነበር፤ ስለዚህ ሃይማኖት ከዚያ በፊት ሰምቼ አላውቅም። ያም ቢሆን ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ለመወያየት በጣም እፈልግ ነበር። ስለ ቅዱሳን መጻሕፍት በቂ እውቀት እንዳለኝ አስብ ነበር። በተልዕኮ ትምህርት የተማርኳቸውን ጥቂት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች ተጠቅሜ ምላሽ ለመስጠት ሞከርኩ። አንዳንድ የፕሮቴስታንት መሠረተ ትምህርቶችን ደግፌ ለመከራከር ብሞክርም በውስጤ በእነዚህ ትምህርቶች አላምንም ነበር።

ከኤኡሄኒዮ ጋር ሁለት ጊዜ ረዘም ያለ ውይይት ካደረግን በኋላ ይህ ወጣት በአምላክ ቃል ጥሩ አድርጎ እንደሚጠቀም ተገነዘብኩ። ኤኡሄኒዮ የትምህርት ደረጃው ከእኔ ያነሰ ቢሆንም ጥቅሶችን እንዴት እንደሚያወጣና እንደሚያብራራ ስመለከት በጣም ተገረምኩ። ኤኡሄኒዮ የምንኖረው በመጨረሻው ዘመን እንደሆነና በቅርቡ የአምላክ መንግሥት ምድርን ገነት እንደሚያደርግ ከመጽሐፍ ቅዱስ አሳየኝ። ይህ ሐሳብ ትኩረቴን ሳበው።—መዝ. 37:11, 29፤ ኢሳ. 9:6, 7፤ ማቴ. 6:9, 10

ወዲያው መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት ጀመርኩ። የተማርኩት ነገር በሙሉ ማለት ይቻላል ለእኔ አዲስ ነበር፤ ትምህርቱ ልቤን ነካው። የወደፊት ሕይወቴ የተሻለ እንደሚሆን ስለተሰማኝ ሕይወት ትርጉም ያለው ሆነልኝ። የተሻለ ነገር ለማግኘት የማደርገው ፍለጋ አበቃ። ትልቅ ቦታ ላይ ለመድረስ የማደርገው ጥረት ትርጉም የለሽ እንደሆነና ከሥራ ጋር በተያያዘ ያሉብኝ ችግሮች ያን ያህል ሊያሳስቡኝ እንደማይገባ ተገነዘብኩ። ወደፊት ሕመምና ሞት እንኳ ሳይቀር የሚወገዱ ከሆነ ሌሎች ችግሮች በሙሉ እንደሚወገዱ ጥርጥር የለውም።—ኢሳ. 33:24፤ 35:5, 6፤ ራእይ 21:4

ብዙም ሳይቆይ የተማርኩትን ነገር ለዘመዶቼ መናገር ጀመርኩ፤ አምላክ ምድርን ወደ ገነትነት በመለወጥ ታማኝ የሆኑ የሰው ልጆች ለዘላለም እንዲኖሩባት ለማድረግ ቃል እንደገባ በጋለ ስሜት ነገርኳቸው።

ቤተሰቦቼ የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት ተቀበሉ

ብዙም ሳይቆይ የተወሰንን ሰዎች በየሳምንቱ እሁድ ከሰዓት በኋላ አጎቴ ቤት በመሰብሰብ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ስለሚገኙት ተስፋዎች ለመወያየት ተስማማን። በየሳምንቱ ለሁለት ወይም ለሦስት ሰዓት ያህል እንወያይ ነበር። ኤኡሄኒዮ ይህን ያህል ብዛት ያላቸው ዘመዶቼ መጽሐፍ ቅዱስን ለማጥናት ፍላጎት እንዳላቸው ሲመለከት እያንዳንዱን ቤተሰብ በግል ለማስጠናት ዝግጅት አደረገ።

ዱራንጎ በተባለች 120 ኪሎ ሜትር ርቃ በምትገኝ አነስተኛ ከተማ ውስጥ የሚኖሩ ሌሎች ዘመዶችም ነበሩኝ፤ በዚያች ከተማ ውስጥ አንድም የይሖዋ ምሥክር አልነበረም። በመሆኑም ከሦስት ወራት በኋላ አዲስ ስላገኘሁት እምነት ለዘመዶቼ ለመንገር የጥቂት ቀናት እረፍት ወስጄ ወደዚያች ከተማ ሄድኩ። በዚያ ወቅት አሥር ያህል የምንሆን ሰዎች በየቀኑ ማታ ማታ እንገናኝ የነበረ ሲሆን እኩለ ሌሊት ካለፈም በኋላ እንኳ እሰብክላቸው ነበር። ሁሉም በደስታ ያዳምጡኝ ነበር። እረፍቴ ሲያበቃ ጥቂት መጽሐፍ ቅዱሶችንና መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጽሑፎችን ትቼላቸው ሄድኩ። ከዚያ በኋላም ግንኙነታችን አልተቋረጠም።

የይሖዋ ምሥክሮች ከዚያ በፊት ወዳልተሰበከባት ወደ ዱራንጎ ሲሄዱ መጽሐፍ ቅዱስን ለማጥናት በጉጉት እየተጠባበቁ ያሉ 18 ሰዎች አገኙ። ወንድሞች እያንዳንዱን ቤተሰብ ለየብቻ መጽሐፍ ቅዱስ ለማስጠናት ዝግጅት አደረጉ።

እስከዚያ ጊዜ ድረስ መርሴዲስ እውነትን አልተቀበለችም ነበር፤ ይህም የሆነው የመጽሐፍ ቅዱስን ትምህርቶች ለመቀበል ስላልፈለገች ሳይሆን የሰው ፍርሃት ስለነበረባት ነው። በወቅቱ የይሖዋ ምሥክሮች ሥራ በስፔን ታግዶ ስለነበር መርሴዲስ ባለሥልጣናቱ ሁለት ልጆቻችንን ከትምህርት ቤት እንዳያባርሯቸውና ሁላችንም ከማኅበረሰቡ እንዳንገለል ትፈራ ነበር። ይሁን እንጂ ቤተሰቦቻችን በሙሉ የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት እየተቀበሉ እንደሆነ ስትመለከት እሷም ለማጥናት ፈለገች።

በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ 40 የቤተሰቤ አባላት ራሳቸውን ለአምላክ መወሰናቸውን ለማሳየት በመጠመቅ የይሖዋ ምሥክሮች ሆኑ። ቤተሰቦቼም በሕይወታቸው ውስጥ እንደ እኔ ዓይነት ግብ መከታተል ጀመሩ። በሕይወቴ ውስጥ ትርጉም ያለው ነገር እንዳከናወንኩ ተሰማኝ። እኔም ሆንኩ ቤተሰቦቼ የተትረፈረፈ መንፈሳዊ ሀብት በማግኘት ተባርከናል።

ዕድሜዬ እየገፋ ሲሄድ የበለጠ ሀብታም ሆንኩ

ከዚያ በኋላ በነበሩት 20 ዓመታት ትኩረት ያደረግኩት ሁለት ልጆቻችንን በማሳደግና ጉባኤያችንን በመርዳት ላይ ነበር። እኔና መርሴዲስ ወደ ሎግሮኞ ከተማ ስንሄድ 100,000 ያህል ነዋሪዎች ባሏት በዚህች ከተማ ውስጥ 20 የይሖዋ ምሥክሮች ብቻ ነበሩ። እኔም ብዙም ሳይቆይ በጉባኤ ውስጥ በርካታ ኃላፊነቶች ተሰጡኝ።

ሃምሳ ስድስት ዓመት ሲሆነኝ የምሠራበት ድርጅት ፋብሪካውን በድንገት ስለዘጋው ሥራ ፈታሁ። ከድሮም ጀምሮ በሙሉ ጊዜ አገልግሎት የመካፈል ከፍተኛ ፍላጎት ነበረኝ፤ ስለዚህ በዚህ አጋጣሚ በመጠቀም አቅኚ ሆኜ ማገልገል ጀመርኩ። የማገኘው የጡረታ ገንዘብ አነስተኛ በመሆኑ በዚያ መተዳደር ቀላል አልነበረም። መርሴዲስ የጽዳት ሥራ በማከናወን ቤተሰባችንን በገንዘብ ትደግፋለች። በዚህ መንገድ ቤተሰባችንን ማስተዳደር የቻልን ሲሆን መሠረታዊ የሆኑ ነገሮችን ፈጽሞ አጥተን አናውቅም። እስካሁን በአቅኚነት እያገለገልኩ ሲሆን መርሴዲስም አልፎ አልፎ ረዳት አቅኚ ሆና ታገለግላለች፤ መርሴዲስ በስብከቱ ሥራ መካፈል በጣም ያስደስታታል።

ከተወሰኑ ዓመታት በፊት መርሴዲስ፣ ሜርቼ ለተባለች በልጅነቷ መጽሐፍ ቅዱስን ታጠና ለነበረች አንዲት ወጣት አዘውትራ መጽሔቶችን ትሰጣት ነበር። ሜርቼ ጽሑፎቻችንን በጉጉት ታነባቸው ነበር፤ ይህች ሴት አሁንም ለመጽሐፍ ቅዱስ እውነት አድናቆት እንዳላት መርሴዲስ አስተዋለች። ከጊዜ በኋላ ሜርቼ መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት የጀመረች ሲሆን ጥሩ እድገት ታደርግ ነበር። ሆኖም ባለቤቷ ቢቴንቴ በጣም የሚጠጣ ከመሆኑም ሌላ ቋሚ ሥራ አልነበረውም። በዚህም ምክንያት ለቤተሰቡ የሚያስፈልገውን የገንዘብ ድጋፍ አያደርግም፤ በመጠጥ ሱሱ የተነሳ ትዳራቸው ሊፈርስ ተቃርቦ ነበር።

ባለቤቴ፣ ቢቴንቴ እኔን እንዲያናግረኝ ለሜርቼ ሐሳብ አቀረበችላት፤ እሱም ከጊዜ በኋላ አነጋገረኝ። ከቢቴንቴ ጋር በተደጋጋሚ ጊዜያት ከተገናኘን በኋላ መጽሐፍ ቅዱስን ለማጥናት ተስማማ። ቢቴንቴ በሕይወቱ ውስጥ ለውጥ በማድረግ ምንም ሳይጠጣ ለተወሰኑ ቀናት መቆየት ቻለ። ከዚያም ለአንድ ሳምንት ወይም ከዚያ ለሚበልጥ ጊዜ መጠጥ ሳይቀምስ መቆየት ጀመረ። በመጨረሻም ከናካቴው መጠጣቱን አቆመ። ቢቴንቴ ሙሉ በሙሉ እንደተለወጠ ከገጽታው መመልከት ይቻል ነበር። ቤተሰባቸው አንድነት ያለው ሆነ። ሚስቱንና ሴት ልጁን ጨምሮ መላው ቤተሰቡ አሁን በሚኖሩበት በካነሪ ደሴቶች ለሚገኘው ትንሽ ጉባኤ ጥሩ ድጋፍ ያደርጋሉ።

ያሳለፍኩትን ትርጉም ያለው ሕይወት መለስ ብሎ መመልከት

ከዓመታት በፊት የመጽሐፍ ቅዱስን ትምህርት ከተቀበሉት ዘመዶቼ መካከል አንዳንዶቹ በአሁኑ ጊዜ በሕይወት ባይኖሩም ቤተሰባችን አሁንም እያደገ ነው፤ አምላክም አትረፍርፎ ባርኮናል። (ምሳሌ 10:22) ከ40 ዓመታት በፊት መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት የጀመሩት ዘመዶቼ በሙሉ ማለት ይቻላል በአሁኑ ጊዜ ከልጆቻቸውና ከልጅ ልጆቻቸው ጋር ሆነው ይሖዋን በታማኝነት ማገልገላቸውን እንደቀጠሉ ስመለከት ከፍተኛ እርካታ ይሰማኛል!

በአሁኑ ጊዜ የይሖዋ ምሥክር የሆኑ እጅግ በጣም ብዙ ዘመዶች ያሉኝ ሲሆን ከእነዚህም አብዛኞቹ ሽማግሌ፣ የጉባኤ አገልጋይ እንዲሁም አቅኚ በመሆን ያገለግላሉ። የመጀመሪያ ልጄና ባለቤቱ በማድሪድ፣ ስፔን በሚገኘው የይሖዋ ምሥክሮች ቅርንጫፍ ቢሮ ውስጥ ያገለግላሉ። እውነትን በተቀበልኩበት ወቅት በስፔን የነበሩት የይሖዋ ምሥክሮች 3,000 ያህል ነበሩ። አሁን ቁጥራችን ከ100,000 በላይ ሆኗል። የሙሉ ጊዜ አገልግሎትን ከልቤ እወደዋለሁ፤ በአምላክ አገልግሎት ላሳለፍኩት ግሩም ሕይወት ይሖዋን በጣም አመሰግነዋለሁ። የትምህርት ደረጃዬ ዝቅተኛ ቢሆንም አልፎ አልፎ ተተኪ የወረዳ የበላይ ተመልካች ሆኜ ማገልገል ችያለሁ።

ከተወሰኑ ዓመታት በፊት፣ ያደግኩበት መንደር ነዋሪዎች በሙሉ ማለት ይቻላል አካባቢውን ለቅቀው መሄዳቸውን ሰማሁ። የመንደሯ ነዋሪዎች በሙሉ ድህነት ስለከፋባቸው የተሻለ ሕይወት ለማግኘት ሲሉ እርሻቸውንና ቤታቸውን ትተው ለመሄድ ተገድደዋል። ደስ የሚለው ነገር እኔን ጨምሮ ወደ ሌላ አካባቢ ከተሰደዱት ከእነዚህ ሰዎች መካከል አብዛኞቹ መንፈሳዊ ሀብት አግኝተዋል። ሕይወት ዓላማ እንዳለውና ይሖዋን ማገልገል ማሰብ ከምንችለው በላይ ከፍተኛ የሆነ ደስታ እንደሚያስገኝ ተገንዝበናል።

[በገጽ 32 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

በእውነት ውስጥ የሚገኙት የወንድም ማርቲኔስ ቤተሰቦች