በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ከንቱ ነገር ከማየት ዓይናችሁን መልሱ!

ከንቱ ነገር ከማየት ዓይናችሁን መልሱ!

ከንቱ ነገር ከማየት ዓይናችሁን መልሱ!

“ከንቱ ነገር ከማየት ዐይኖቼን መልስ፤ በራስህ መንገድ እንደ ገና ሕያው አድርገኝ።”—መዝ. 119:37

1. የማየት ችሎታችን ምን ያህል አስፈላጊ ነው?

የማየት ችሎታችን እንዴት ያለ ውድ ስጦታ ነው! ይህ ስጦታ በዙሪያችን ያሉት ነገሮች ትክክለኛ ገጽታ ቁልጭ ብሎ እንዲታየን እንዲሁም ቀለማቸውን እንድንለይ ያስችለናል። የማየት ችሎታችን የወዳጆቻችንን መልክ ወይም አደጋ ሊያስከትሉብን የሚችሉ ነገሮችን ለመለየት ያስችለናል። ይህ ውድ ስጦታ ውበትን ለማድነቅና አስገራሚ በሆኑት የፍጥረት ሥራዎች ለመደመም ብሎም የአምላክን መኖርና ክብሩን የሚያሳዩ ማስረጃዎችን ለመመልከት አስችሎናል። (መዝ. 8:3, 4፤ 19:1, 2፤ 104:24፤ ሮም 1:20) ዓይናችን ወደ አእምሯችን መረጃ የሚተላለፍበት ዋነኛ መንገድ እንደመሆኑ መጠን ስለ ይሖዋ እንድናውቅና በእሱ ላይ እምነት እንድናሳድር በመርዳት ረገድ ትልቅ ድርሻ አለው።—ኢያሱ 1:8፤ መዝ. 1:2, 3

2. በዓይናችን የምናየው ነገር ሊያሳስበን የሚገባው ለምንድን ነው? መዝሙራዊው ከዚህ ጋር በተያያዘ ካቀረበው ጸሎት ምን ትምህርት እናገኛለን?

2 ይሁንና የምናየው ነገር ጉዳት ሊያስከትልብንም ይችላል። የምናየው ነገር በአእምሯችን ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ ስለሚያሳድር በዓይናችን የሚገባው ነገር በልባችን ውስጥ አንድ ዓይነት ፍላጎት ወይም ምኞት እንዲጠነሰስ ሊያደርግ ወይም ቀድሞውኑም የነበረውን ምኞት ሊያባብሰው ይችላል። ሰይጣን ዲያብሎስ በሚገዛው እንዲሁም በሥነ ምግባር ባዘቀጠና የራሱን ፍላጎት ብቻ ለማርካት በሚሮጥ ዓለም ውስጥ ስለምንኖር ከትክክለኛው ጎዳና ስተን እንድንሄድ ሊያደርጉን የሚችሉ ምስሎችና ፕሮፖጋንዳዎች ይዥጎደጎዱብናል፤ እነዚህን ነገሮች የተመለከትናቸው ለቅጽበት ያህል ብቻ እንኳ ቢሆን ከፍተኛ ተጽዕኖ ያሳድሩብናል። (1 ዮሐ. 5:19) በመሆኑም መዝሙራዊው “ከንቱ ነገር ከማየት ዐይኖቼን መልስ፤ በራስህ መንገድ እንደ ገና ሕያው አድርገኝ” በማለት አምላክን መማጸኑ ምንም አያስገርምም።—መዝ. 119:37

ዓይናችን ሊያስተን የሚችለው እንዴት ነው?

3-5. በዓይን አምሮት መሸነፍ የሚያስከትለውን አደጋ የሚያሳዩ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሳሌዎች ተናገር።

3 የመጀመሪያዋ ሴት ሔዋን ምን እንዳጋጠማት እስቲ እንመልከት። ሰይጣን “መልካምና ክፉን ከሚያሳውቀው ዛፍ” ፍሬ ወስዳ ብትበላ ዓይኗ “እንደሚከፈት” ነገራት። ሔዋን ‘ዓይንሽ ይከፈታል’ የሚለው ሐሳብ ትኩረቷን ስቦት መሆን አለበት። ሔዋን ከተከለከለው ዛፍ ፍሬ የመብላት ፍላጎቷ የጨመረው “የዛፉ ፍሬ ለመብል መልካም፣ ለዐይን የሚያስደስትና ጥበብንም ለማግኘት የሚያጓጓ እንደ ሆነ ባየች ጊዜ” ነበር። ሔዋን የዛፉን ፍሬ በምኞት መመልከቷ የአምላክን ትእዛዝ ወደ መጣስ መራት። ባሏ አዳምም የአምላክን ትእዛዝ የጣሰ ሲሆን ይህም በሰው ዘሮች ሁሉ ላይ ከባድ ጉዳት አስከተለ።—ዘፍ. 2:17፤ 3:2-6፤ ሮም 5:12፤ ያዕ. 1:14, 15

4 በኖኅ ዘመንም አንዳንድ መላእክት የተመለከቱት ነገር ተጽዕኖ አሳድሮባቸው ነበር። ዘፍጥረት 6:2 ስለ እነዚህ መላእክት ሲናገር እንዲህ ይላል፦ “የእግዚአብሔር ወንዶች ልጆች የሰዎችን ሴቶች ልጆች ውብ ሆነው አዩአቸው፤ ከመካከላቸውም የመረጧቸውን አገቡ።” ዓመፀኞቹ መላእክት የሰውን ሴቶች ልጆች በፆታ ስሜት መመልከታቸው ከሰው ልጆች ጋር የፆታ ግንኙነት የመፈጸም ከተፈጥሮ ውጪ የሆነ ፍላጎት እንዲቀሰቀስባቸው አድርጓል፤ እነዚህ መላእክት ዓመፀኛ የሆኑ ልጆችን ወለዱ። በዚያ ወቅት የሰው ልጆች ክፋት እጅግ ከመብዛቱ የተነሳ አምላክ ከኖኅና ከቤተሰቡ በስተቀር መላውን የሰው ዘር አጠፋው።—ዘፍ. 6:4-7, 11, 12

5 ይህ ከሆነ ከበርካታ መቶ ዓመታት በኋላ አካን የተባለው እስራኤላዊ በምርኮ በተያዘችው በኢያሪኮ ከተማ ውስጥ ያያቸውን አንዳንድ ነገሮች ለማግኘት ዓይኑ በመቋመጡ ለመስረቅ ተነሳስቷል። ወደ ይሖዋ ግምጃ ቤት ከሚገቡት አንዳንድ ነገሮች ውጪ በዚያች ከተማ ውስጥ ያሉት ነገሮች በሙሉ መጥፋት እንዳለባቸው አምላክ ትእዛዝ ሰጥቶ ነበር። እስራኤላውያን በከተማዋ ውስጥ የሚገኙትን ነገሮች እንዳይመኙና እንዳይወስዱ ሲባል “እርም ከሆኑት ነገሮች” እንዲርቁ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸው ነበር። አካን ይህን ትእዛዝ በመጣሱ እስራኤላውያን በጋይ ከተማ ሽንፈት ያጋጠማቸው ሲሆን አንዳንዶቹም ሕይወታቸውን አጥተዋል። አካን ጉዳዩ በግልጽ እስኪታወቅ ድረስ ጥፋቱን አላመነም ነበር። አካን በተጋለጠ ጊዜ “[ዕቃዎቹን] አይቼ ጐመጀሁ፤ ወሰድኋቸውም” በማለት ተናገረ። አካን በዓይን አምሮት መሸነፉ እሱም ሆነ ‘የእሱ የሆነው ሁሉ’ እንዲጠፋ ምክንያት ሆኗል። (ኢያሱ 6:18, 19፤ 7:1-26) አካን እንዳይወስድ የተከለከለውን ነገር በልቡ ተመኘ።

ራስን የመግዛት አስፈላጊነት

6, 7. ሰይጣን እኛን ለማጥመድ በአብዛኛው የሚጠቀምበት “ዕቅድ” የትኛው ነው? የንግድ ማስታወቂያ አዘጋጆችስ ይህንን ዘዴ የሚጠቀሙበት እንዴት ነው?

6 በዛሬው ጊዜ ያሉ የሰው ልጆችም ሔዋን፣ ዓመፀኛ የሆኑት መላእክትና አካን ካጋጠማቸው ሁኔታ ጋር በሚመሳሰል መንገድ ፈተና እየደረሰባቸው ነው። ሰይጣን የሰው ልጆችን ለማሳሳት ከሚጠቀምባቸው ‘ዕቅዶች’ ሁሉ ከፍተኛ ኃይል ያለው “የዓይን አምሮት” ነው። (2 ቆሮ. 2:11፤ 1 ዮሐ. 2:16) በዘመናችን ያሉ የንግድ ማስታወቂያ አዘጋጆች ምንጊዜም ቢሆን ሰዎች በሚያዩት ነገር እንደሚማረኩ ጠንቅቀው ያውቃሉ። በአውሮፓ ታዋቂ የሆኑ አንድ የገበያ ጥናት ባለሙያ “ካሉን የስሜት ሕዋሳት ሁሉ የማየት ችሎታችንን ያህል የሚደልለን የለም” ብለዋል። “የማየት ችሎታችን አብዛኛውን ጊዜ ሌሎቹን የስሜት ሕዋሳቶቻችንን የሚቆጣጠር ሲሆን ትክክል እንደሆነ ከምናውቀው መንገድ በተቃራኒው እንድንሄድ የማድረግ ኃይል አለው።”

7 ከዚህ አንጻር የማስታወቂያ አዘጋጆች ለዓይን እጅግ በሚማርክና ዕቃዎቻቸውን ወይም የሚሰጡትን አገልግሎት ለማግኘት እንድንጓጓ በሚያደርግ መልኩ በብልሃት የተዘጋጁ ምስሎችን የሚያጎርፉብን መሆኑ ምንም አያስደንቅም! ማስታወቂያ በሰዎች ላይ ተጽዕኖ የሚያሳድረው እንዴት እንደሆነ ጥናት ያካሄዱ በዩናይትድ ስቴትስ የሚኖሩ አንድ ምሑር እንደገለጹት ከሆነ ማስታወቂያዎች “የሚዘጋጁት መረጃ ለማስተላለፍ ብቻ አይደለም። ከዚህ ይልቅ ዋነኛ ዓላማቸው በሰዎች ላይ አንድ ዓይነት ስሜት በማሳደር እርምጃ እንዲወስዱ ማነሳሳት ነው።” ይህን ለማሳካት ብዙውን ጊዜ ከሚሠራባቸው ዘዴዎች አንዱ የፆታ ስሜት በሚቀሰቅሱ ምስሎች መጠቀም ነው። እንግዲያው የምንመለከታቸውንም ሆነ ወደ አእምሯችንና ወደ ልባችን የምናስገባቸውን ነገሮች መቆጣጠራችን ምንኛ አስፈላጊ ነው!

8. ዓይናችንን የመቆጣጠር አስፈላጊነት በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ጎላ ተደርጎ የተገለጸው እንዴት ነው?

8 እውነተኛ ክርስቲያኖች በዓይን አምሮትና በሥጋ ምኞት እንዳይሸነፉ የሚከላከል ክትባት አልወሰዱም። በመሆኑም የአምላክ ቃል በምናያቸውና በምንመኛቸው ነገሮች ረገድ ራሳችንን እንድንገዛ ማበረታቻ ሰጥቶናል። (1 ቆሮ. 9:25, 27፤ 1 ዮሐንስ 2:15-17ን አንብብ።) ቅን ሰው የነበረው ኢዮብ፣ ዓይናችን አንድን ነገር እንድንመኝ የማድረግ ኃይል እንዳለው ተገንዝቦ ነበር። “ወደ ኰረዳዪቱ ላለመመልከት፣ ከዐይኔ ጋር ቃል ኪዳን ገብቻለሁ” በማለት ተናግሯል። (ኢዮብ 31:1) ኢዮብ ሴትን ሥነ ምግባር በጎደለው መንገድ መንካት ይቅርና እንዲህ ዓይነቱን ሐሳብ በአእምሮው እንኳ ላለማውጠንጠን ቆርጦ ነበር። ኢየሱስ አእምሯችን ሥነ ምግባር ከጎደላቸው ሐሳቦች የጸዳ መሆን እንዳለበት ጎላ አድርጎ ሲገልጽ እንዲህ ብሏል፦ “የፆታ ስሜቱ እስኪቀሰቀስ ድረስ አንዲትን ሴት በምኞት የሚመለከት ሁሉ በዚያን ጊዜ በልቡ ከእሷ ጋር አመንዝሯል።”—ማቴ. 5:28

ልንርቃቸው የሚገቡ ከንቱ ነገሮች

9. (ሀ) በተለይ ኢንተርኔት ስንጠቀም ጠንቃቆች መሆን የሚያስፈልገን ለምንድን ነው? (ለ) ለቅጽበት ያህል እንኳ የብልግና ምስሎችን መመልከት ምን ሊያስከትል ይችላል?

9 በዛሬው ጊዜ በተለይ በኢንተርኔት አማካኝነት የብልግና ምስሎችን ‘መመልከት’ የተለመደ ድርጊት እየሆነ መጥቷል። እንደነዚህ ያሉ ምስሎች ያሉባቸው ድረ ገጾች እኛ ባንፈልጋቸውም እነሱ ራሳቸው ሊመጡብን ይችላሉ። እንዴት? ማራኪ የሆነ ምስል የያዘ ማስታወቂያ በድንገት ኮምፒውተራችን ላይ ብቅ ይል ይሆናል። አሊያም ደግሞ ጤናማ የሚመስል መልእክት ይደርሰንና ስንከፍተው ግን የብልግና ምስል የያዘ ይሆናል፤ ፕሮግራሙ የተዘጋጀው ለማጥፋት በሚያስቸግር መንገድ ሊሆን ይችላል። አንድ ሰው ምስሉን ከማጥፋቱ በፊት ለቅጽበት እንኳ ቢመለከተው ምስሉ በአእምሮው ውስጥ መቀረጹ አይቀርም። የብልግና ምስሎችን ለአፍታ እንኳ መመልከት አብዛኛውን ጊዜ አሳዛኝ መዘዞች ያስከትላል። ግለሰቡን በሕሊና ወቀሳ እንዲሠቃይ የሚያደርገው ከመሆኑም ሌላ ወደ አእምሮው የገባውን መጥፎ ምስል ለማስወገድ ትግል ሊጠይቅበት ይችላል። ከዚህ የከፋው ደግሞ አንድ ሰው እንደነዚህ ያሉ ምስሎችን ሆን ብሎ ‘የሚመለከት’ ከሆነ በልቡ ውስጥ ያሉትን መጥፎ ምኞቶች ገና አልገደለም ማለት ነው።—ኤፌሶን 5:3, 4, 12ን አንብብ፤ ቆላ. 3:5, 6

10. በተለይ ልጆች ለብልግና ምስሎች የተጋለጡ የሆኑት ለምንድን ነው? እንዲህ ዓይነት ምስሎችን መመልከታቸውስ ምን ሊያስከትል ይችላል?

10 ልጆች በተፈጥሮ ያላቸው የማወቅ ጉጉት የብልግና ምስሎችን እንዲመለከቱ ሊያነሳሳቸው ይችላል። እንዲህ ዓይነት ምስሎችን መመልከታቸው ስለ ፆታ ግንኙነት ያላቸውን አመለካከት ሊያበላሸውና ዘላቂ የሆነ ጉዳት ሊያስከትልባቸው ይችላል። አንድ ሪፖርት እንደገለጸው ልጆች የብልግና ምስሎችን መመልከታቸው ከፆታ ግንኙነት ጋር በተያያዘ ተቀባይነት ስላለው ነገር የተዛባ አመለካከት እንዲኖራቸው አልፎ ተርፎም “ከሰዎች ጋር ጤናማና በፍቅር ላይ የተመሠረተ ግንኙነት ማዳበር እንዲያስቸግራቸው፣ ለሴቶች ተገቢ ያልሆነ አመለካከት እንዲያድርባቸው ብሎም የብልግና ምስሎችን የመመልከት ሱስ እንዲይዛቸው ሊያደርግ ይችላል፤ በዚህ ሱስ መጠመዳቸው ትምህርታቸውን የሚነካ ከመሆኑም ሌላ ከጓደኞቻቸውም ሆነ ከቤተሰቦቻቸው ጋር ባላቸው ግንኙነት ላይ ተጽዕኖ ይኖረዋል።” ወደፊት በትዳር ሕይወታቸው ላይ ደግሞ የከፋ መዘዝ ሊያስከትል ይችላል።

11. የብልግና ምስሎችን መመልከት ያለውን አደጋ የሚያሳይ ምሳሌ ተናገር።

11 አንድ ክርስቲያን እንዲህ ሲል ጽፏል፦ “የይሖዋ ምሥክር ከመሆኔ በፊት ከነበሩብኝ ሱሶች ሁሉ ለመተው በጣም የከበደኝ የብልግና ምስሎችን የማየት ሱስ ነበር። አሁንም እንኳ እነዚህ ምስሎች ባላሰብኩት ጊዜ ወደ አእምሮዬ ይመጣሉ፤ ምናልባትም እነዚህን ምስሎች የማስታውሰው አንድ ነገር ሲሸተኝ፣ አንዳንድ ሙዚቃዎችን ስሰማ፣ የሆነ ነገር ሳይ ወይም ሐሳቤ ሲበታተን ሊሆን ይችላል። ሁኔታውን ለማሸነፍ በየቀኑ ያልተቋረጠ ትግል ማድረግ ይጠይቃል።” ሌላም ወንድም ተመሳሳይ ነገር አጋጥሞታል። ትንሽ ልጅ ሳለ አማኝ ያልሆነው አባቱ ያመጣቸው የነበሩትን የብልግና ምስል ያለባቸው መጽሔቶች ወላጆቹ በማይኖሩበት ጊዜ ይመለከት ነበር። እንዲህ ሲል ጽፏል፦ “እነዚያ ምስሎች በልጅ አእምሮዬ ላይ መጥፎ ተጽዕኖ አሳድረዋል! ከ25 ዓመታት በኋላም እንኳ እነዚህ ምስሎች አሁንም ከአእምሮዬ አልተፋቁም። ለመርሳት ምንም ያህል ትግል ባደርግ ላጠፋቸው አልቻልኩም። ስለ ምስሎቹ ማሰቤን ያቆምኩ ቢሆንም ከአእምሮዬ ሊጠፉ ባለመቻላቸው የጥፋተኝነት ስሜት ይሰማኛል።” እንዲህ ያለው የስሜት ቀውስ ውስጥ ላለመግባት ከንቱ ነገሮችን ከመመልከት መቆጠብ ምንኛ ጥበብ ነው! አንድ ሰው እንዲህ ማድረግ የሚችለው እንዴት ነው? ‘ማንኛውንም አስተሳሰብ እየማረከ ለክርስቶስ እንዲታዘዝ ለማድረግ’ መጣር ይኖርበታል።—2 ቆሮ. 10:5

12, 13. ክርስቲያኖች ሊያዩዋቸው የማይገቡ ከንቱ ነገሮች የትኞቹ ናቸው? ለምንስ?

12 ሌላው ልናስወግደው የሚገባ “ክፉ” ወይም ከንቱ ነገር ደግሞ ፍቅረ ንዋይን አሊያም የመናፍስትነት ሥራን የሚያበረታታ ወይም ዓመፅ፣ ደም መፋሰስና ግድያ የሚታይበት መዝናኛ ነው። (መዝሙር 101:3ን አንብብ።) ይሖዋ ለክርስቲያን ወላጆች ከሰጣቸው ኃላፊነቶች አንዱ በቤታቸው ውስጥ ምን መታየት እንዳለበትና እንደሌለበት መምረጥ ነው። እርግጥ ነው፣ ማንኛውም እውነተኛ ክርስቲያን ሆን ብሎ በመናፍስታዊ ድርጊቶች አይካፈልም። ያም ሆኖ ወላጆች አስማታዊ ድርጊቶች በፊልም፣ በቴሌቪዥን፣ በቪዲዮ ጨዋታዎች፣ በሥዕል መልክ በሚዘጋጁ የቀልድ ጽሑፎችና በልጆች መጻሕፍት ላይ ስውር በሆነ መንገድ እንደሚቀርቡ መገንዘብ ይኖርባቸዋል።—ምሳሌ 22:5

13 ወጣቶችም ሆንን አዋቂዎች ዓመፅና አሰቃቂ ግድያ ሲፈጸም የሚያሳዩ የቪዲዮ ጨዋታዎችን በመጫወት መደሰት አይኖርብንም። (መዝሙር 11:5ን አንብብ።) ይሖዋ በሚጠላው በማንኛውም ድርጊት ላይ አእምሯችን እንዲያተኩር መፍቀድ የለብንም። ሰይጣን የሚፈልገው አስተሳሰባችንን ማበላሸት እንደሆነ አትዘንጋ። (2 ቆሮ. 11:3) ጤናማ እንደሆኑ የሚቆጠሩ መዝናኛዎችን በመመልከት ረጅም ሰዓት ማሳለፍም ቢሆን ለቤተሰብ አምልኮ፣ በየቀኑ ለምናደርገው የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብና ለስብሰባዎች ለመዘጋጀት የምናውለውን ጊዜ ሊሻማብን ይችላል።—ፊልጵ. 1:9, 10

የኢየሱስን ምሳሌ ተከተሉ

14, 15. ሰይጣን ለክርስቶስ ያቀረበለት ሦስተኛ ፈተና ትኩረታችንን የሚስበው ለምንድን ነው? ኢየሱስ ፈተናውን ሊቋቋም የቻለውስ እንዴት ነው?

14 የሚያሳዝነው በዚህ ክፉ ሥርዓት ውስጥ ስንኖር ከንቱ ነገር ከማየት ሙሉ በሙሉ መራቅ አንችልም። ኢየሱስም እንኳ እንዲህ ዓይነት ነገር ቀርቦለት ነበር። ኢየሱስ የአምላክን ፈቃድ ከመፈጸም ወደኋላ እንዲል ለማድረግ ሰይጣን ለሦስተኛ ጊዜ በሞከረበት ወቅት ኢየሱስን “በጣም ረጅም ወደሆነ ተራራ ወስዶ የዓለምን መንግሥታት ሁሉና ክብራቸውን አሳየው።” (ማቴ. 4:8) ሰይጣን እንዲህ ያደረገው ለምንድን ነው? የማየት ችሎታችን ያለውን ተጽዕኖ የማሳደር ኃይል ሊጠቀምበት ፈልጎ እንደሚሆን ምንም ጥርጥር የለውም። ኢየሱስ የሁሉንም የዓለም መንግሥታት ክብር መመልከቱ በዓለም ላይ ትልቅ ሥልጣን የማግኘት ምኞት እንዲያድርበት ሊያደርገው ይችል ነበር። ታዲያ ኢየሱስ ምን አደረገ?

15 ኢየሱስ በዚህ የሚያጓጓ ግብዣ ላይ ትኩረት አላደረገም። ልቡ መጥፎ ምኞቶችን እንዲያስተናግድ አልፈቀደም። ዲያብሎስ ያቀረበለትን ሐሳብ እንደማይቀበለው ከመግለጹ በፊት በጉዳዩ ላይ ማሰብ እንኳ አላስፈለገውም። ኢየሱስ መልስ የሰጠው ወዲያውኑ ነበር። “አንተ ሰይጣን፣ ከፊቴ ራቅ!” አለው። (ማቴ. 4:10) ኢየሱስ ከይሖዋ ጋር ባለው ዝምድና ላይ ትኩረት ያደረገ ሲሆን ከተፈጠረበት ዓላማ ማለትም የአምላክን ፈቃድ ከመፈጸም ጋር የሚስማማ መልስ ሰጥቷል። (ዕብ. 10:7) በመሆኑም ኢየሱስ፣ ሰይጣን የተጠቀመበትን የተንኮል ዘዴ ማክሸፍ ችሏል።

16. ሰይጣን የሚያቀርባቸውን ፈተናዎች በመቋቋም ረገድ ኢየሱስ ከተወው ምሳሌ ምን ትምህርት ማግኘት እንችላለን?

16 ኢየሱስ ከተወው ምሳሌ ብዙ ትምህርት ማግኘት እንችላለን። አንደኛ፣ ማንኛውም ሰው ሰይጣን ለሚያቀርባቸው ፈተናዎች የተጋለጠ ነው። (ማቴ. 24:24) ሁለተኛ፣ ዓይናችን ትኩረት የሚያደርግበት ነገር በልባችን ውስጥ ጥሩ ወይም መጥፎ ምኞት እንዲቀሰቀስ ሊያደርግ ይችላል። ሦስተኛ፣ ሰይጣን ከትክክለኛው ጎዳና ስተን እንድንሄድ በሚያደርገው ጥረት ‘የዓይን አምሮትን’ በተቻለው መጠን ይጠቀማል። (1 ጴጥ. 5:8) እንዲሁም አራተኛ፣ እኛም ሳንዘገይ እርምጃ ከወሰድን ሰይጣንን መቃወም እንችላለን።—ያዕ. 4:7፤ 1 ጴጥ. 2:21

ዓይናችሁ ምንጊዜም “አጥርቶ የሚያይ” ይሁን

17. ከንቱ ነገሮች እስኪያጋጥሙን ድረስ ከመጠበቅ ይልቅ ፈተና ሲያጋጥመን ምን እንደምናደርግ አስቀድመን መወሰናችን የጥበብ እርምጃ ነው የምንለው ለምንድን ነው?

17 ራሳችንን ለይሖዋ በወሰንበት ጊዜ የገባነው ቃል ከንቱ ከሆነ ነገር ለመራቅ ቁርጥ ውሳኔ ማድረግንም ይጨምራል። የአምላክን ፈቃድ ለመፈጸም ስዕለት ስንሳል “ቃልህን እጠብቅ ዘንድ፣ እግሬን ከክፉ መንገድ ሁሉ ከለከልሁ” በማለት የተናገረውን የመዝሙራዊውን ሐሳብ ተጋርተናል። (መዝ. 119:101) ከንቱ ነገሮች እስኪያጋጥሙን ድረስ ከመጠበቅ ይልቅ ለፈተናዎች የምንሰጠውን ምላሽ አስቀድመን መወሰናችን የጥበብ እርምጃ ነው። ቅዱሳን መጻሕፍት የሚያወግዟቸውን ጉዳዮች በተመለከተ ግልጽ ትምህርት ተሰጥቶናል። የሰይጣንን ዘዴዎች እናውቃቸዋለን። ኢየሱስ ድንጋዩን ዳቦ እንዲያደርገው ፈተና የቀረበለት ምን ጊዜ ነበር? አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ጾሞ ‘በተራበ’ ጊዜ ነበር። (ማቴ. 4:1-4) ሰይጣን የምንደክምበትንና ለፈተና በቀላሉ የምንሸነፍበትን ጊዜ ማወቅ ይችላል። በመሆኑም በዚህ ርዕስ ውስጥ ለተብራሩት ጉዳዮች አሁኑኑ ትኩረት ልንሰጣቸው ይገባል። ይህን ለማድረግ ዛሬ ነገ አትበሉ! ራሳችንን ለይሖዋ ስንወስን የገባነውን ቃል በየዕለቱ የምናስታውስ ከሆነ ከንቱ ከሆኑ ነገሮች ለመራቅ ቁርጥ ውሳኔ እናደርጋለን።—ምሳሌ 1:5፤ 19:20

18, 19. (ሀ) ‘አጥርቶ በሚያይ’ ዓይንና ‘በሚቅበዘበዝ’ ዓይን መካከል ያለውን ልዩነት ተናገር። (ለ) ምንጊዜም ጠቃሚ በሆኑ ነገሮች ላይ ትኩረት ማድረጋችን አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው? በዚህ ረገድ በፊልጵስዩስ 4:8 ላይ ምን ምክር ተሰጥቶናል?

18 ትኩረታችን እንዲሰረቅ የሚያደርጉ ዓይንን የሚማርኩ ነገሮች በየዕለቱ የሚያጋጥሙን ሲሆን ብዛትና ዓይነታቸውም በየጊዜው እየጨመረ ነው። በመሆኑም “አጥርቶ የሚያይ” ዓይን እንዲኖረን ኢየሱስ የሰጠውን ማሳሰቢያ መከተላችን ከምንጊዜው የበለጠ አስፈላጊ ነው። (ማቴ. 6:22, 23) “አጥርቶ የሚያይ” ዓይን መያዝ ሲባል ሙሉ በሙሉ በአንድ ዓላማ ይኸውም የአምላክን ፈቃድ በማድረግ ላይ ማተኮር ማለት ነው። በሌላ በኩል ግን “የሚቅበዘበዝ” ዓይን ተንኮለኛና የሚጎመጅ ከመሆኑም ሌላ ከንቱ በሆኑ ነገሮች ይማረካል።

19 የምናየው ነገር በአእምሯችን ላይ ተጽዕኖ እንደሚያሳድርና አእምሯችን ደግሞ በልባችን ላይ ተጽዕኖ እንደሚያሳድር አስታውሱ። በመሆኑም ጠቃሚ በሆኑ ነገሮች ላይ ትኩረት ማድረጋችን ምንኛ አስፈላጊ ነው! (ፊልጵስዩስ 4:8ን አንብብ።) እንግዲያው “ከንቱ ነገር ከማየት ዐይኖቼን መልስ” በማለት መዝሙራዊው ያቀረበውን ጸሎት ማስተጋባታችንን እንቀጥል። ከዚህ ጸሎት ጋር በሚስማማ መንገድ ለመመላለስ ጥረት ስናደርግ ይሖዋ “[በራሱ] መንገድ እንደ ገና ሕያው [እንደሚያደርገን]” እርግጠኞች መሆን እንችላለን።—መዝ. 119:37፤ ዕብ. 10:36

ከሚከተሉት ነገሮች ጋር በተያያዘ ምን ማስታወስ ይኖርብናል?

• በዓይናችን፣ በአእምሯችንና በልባችን መካከል ስላለው ግንኙነት

• የብልግና ምስሎችን መመልከት ስለሚያስከትላቸው አደጋዎች

• ምንጊዜም “አጥርቶ የሚያይ” ዓይን መያዝ ስላለው አስፈላጊነት

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 23 ላይ የሚገኙ ሥዕሎች]

ክርስቲያኖች የትኞቹን ከንቱ ነገሮች ከመመልከት መራቅ ይኖርባቸዋል?