በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ይሖዋ ‘ደኅንነትህ’ እንዲጠበቅ ይፈልጋል

ይሖዋ ‘ደኅንነትህ’ እንዲጠበቅ ይፈልጋል

ይሖዋ ‘ደኅንነትህ’ እንዲጠበቅ ይፈልጋል

ሪክ ውስጥ ታይቶ የማይታወቀው አደገኛ ሁኔታ በሚከሰትበት ጊዜ ሁሉን ቻይ የሆነው አምላክ ሕዝቦቹን ‘እንደሚጠብቅ’ ምንም ጥርጥር የለውም። (መዝ. 31:23) ለነገሩ ይሖዋ ምንጊዜም ሰዎች ከአደጋ እንዲጠበቁ ይፈልጋል። “የሕይወት ምንጭ [ከእሱ] ዘንድ” በመሆኑ መላውን የሰው ዘር ጥበቃ ሊደረግለት እንደሚገባና ውድ እንደሆነ አድርጎ ይመለከተዋል።—መዝ. 36:9

የጥንቶቹ የአምላክ አገልጋዮች ፈጣሪ ለሕይወት ያለው ዓይነት አመለካከት ነበራቸው። ያዕቆብና ቤተሰቡ ያደረጉትን አደገኛ ጉዞ “በደኅና” እንዳጠናቀቁ ዘፍጥረት 33:18 ይናገራል። ያዕቆብ በይሖዋ ጥበቃ ቢተማመንም አብረውት የሚጓዙትን ሁሉ ከአደጋ ለመጠበቅ እሱም የበኩሉን እርምጃ ወስዷል። (ዘፍ. 32:7, 8፤ 33:14, 15) አንተም የመጽሐፍ ቅዱስን መሠረታዊ ሥርዓቶች ሥራ ላይ በማዋል የራስህም ሆነ የሌሎች ደኅንነት ይበልጥ የተጠበቀ እንዲሆን ማድረግ ትችላለህ። በመንግሥት አዳራሽ ግንባታና በመሳሰሉት ሥራዎች እንዲሁም በአደጋ የተጎዱትን በመርዳት የሚካፈሉ ሰዎች ይህንን እንዴት ተግባራዊ ማድረግ እንደሚችሉ እስቲ እንመልከት።

ደኅንነትን መጠበቅ በሙሴ ሕግ ሥር የተሰጠው ቦታ

የአምላክ ሕዝቦች ራሳቸውን ከአደጋ ለመጠበቅ በሙሴ ሕግ ውስጥ የተሰጣቸውን መመሪያ እንዲከተሉ ይጠበቅባቸው ነበር። ለምሳሌ ያህል፣ አንድ እስራኤላዊ ቤት በሚሠራበት ጊዜ በጣሪያው ዙሪያ መከታ ማበጀት ነበረበት። አብዛኛውን ጊዜ እስራኤላውያን ጠፍጣፋ በሆነው የቤታቸው ጣሪያ ላይ ሆነው አንዳንድ ነገሮችን ያከናውኑ ስለነበር በጣሪያው ዙሪያ መከታ መደረጉ እንዳይወድቁ ይጠብቃቸው ነበር። (1 ሳሙ. 9:26፤ ማቴ. 24:17) ለደኅንነታቸው ሲባል የተሰጠው ይህ መመሪያ ተግባራዊ ሳይደረግ በመቅረቱ አደጋ ቢከሰት ይሖዋ የቤቱን ባለቤት ተጠያቂ ያደርገዋል።—ዘዳ. 22:8

በቤት እንስሳት አማካኝነት የሚደርስ ጉዳትን በተመለከተም ሕጉ ተፈጻሚነት ነበረው። አንድ በሬ አንድን ሰው በቀንዱ ወግቶ ቢገድል ባለቤቱ የሌሎች ሰዎችን ደኅንነት ለመጠበቅ ሲል በሬውን ማስወገድ ነበረበት። ባለቤቱ የበሬውን ሥጋ ሊበላው ወይም ለሌሎች ሊሸጠው ስለማይችል በሬውን መግደሉ ትልቅ ኪሳራ ይሆንበት ነበር። ይሁንና አንድ በሬ በሰው ላይ ጉዳት እንዳደረሰ እያወቀ ባለቤቱ ሳያስረው ቢቀርስ? ይህ በሬ በሌላ ጊዜ አንድ ሰው ቢገድል፣ በሬውም ሆነ ባለቤቱ ይገደሉ ነበር። ይህ ሕግ ማንኛውም ሰው ከእንስሶቹ ጋር በተያያዘ ግድ የለሽ እንዳይሆን ማስጠንቀቂያ ይሆን ነበር።—ዘፀ. 21:28, 29

ሕጉ እስራኤላውያን መሣሪያዎቻቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙባቸውም ያበረታታ ነበር። ብዙ እስራኤላውያን ለማገዶ የሚሆን እንጨት ለመቁረጥ መጥረቢያ ይጠቀሙ ነበር። አንድ ሰው መጥረቢያውን በሚሰነዝርበት ጊዜ ብረቱ ድንገት ከእጀታው ወልቆ በአካባቢው የነበረን ሰው በመምታት ቢገድል እንጨት ቆራጩ ወደ መማጸኛ ከተማ መሸሽ ነበረበት። ይህ ግለሰብ ሊቀ ካህናቱ እስኪሞት ድረስ በዚያ መቆየት ነበረበት፤ በመሆኑም ሳያስበው ሕይወት ያጠፋው ሰው ለዓመታት ከቤቱና ከቤተሰቡ ርቆ ሊቆይ ይችላል ማለት ነው። ይህ ዝግጅት ሕይወት በይሖዋ ዘንድ ቅዱስ መሆኑን ለሕዝቡ አስተምሯቸዋል። ሕይወትን በተመለከተ የአምላክ ዓይነት አመለካከት ያለው ሰው ለመሣሪያዎቹ ጥሩ ጥገና የሚያደርግ ከመሆኑም ሌላ አደጋ በማያስከትል መንገድ ይጠቀምባቸዋል።—ዘኍ. 35:25፤ ዘዳ. 19:4-6

ይሖዋ እንደነዚህ ያሉ ሕግጋትን መስጠቱ ሕዝቡ በቤታቸው ውስጥም ሆነ ከቤት ውጪ ሥራቸውን በሚያከናውኑበት ጊዜ ለደኅንነታቸው ጥንቃቄ እንዲያደርጉ የሚፈልግ መሆኑን በግልጽ ያሳያል። ሳያስቡትም እንኳ ቢሆን በሌሎች ላይ ጉዳት ያደረሱ ወይም ሕይወት ያጠፉ ሰዎች በእሱ ዘንድ ተጠያቂ ይሆኑ ነበር። ይሖዋ ደኅንነትን ስለመጠበቅ ያለው አመለካከት ዛሬም አልተለወጠም። (ሚል. 3:6) አሁንም ቢሆን ሰዎች በራሳቸውም ሆነ በሌሎች ላይ ጉዳት ላለማድረስ እንዲጠነቀቁ ይፈልጋል። በተለይ ደግሞ ለእውነተኛው አምልኮ እንዲውሉ የተወሰኑ ሕንፃዎችን በምንገነባበትም ሆነ በምንጠግንበት ጊዜ ይህን ማድረግ ይኖርብናል።

በግንባታ ሥራዎች ላይ ደኅንነትን መጠበቅ

የመንግሥት አዳራሾችንና ትላልቅ የመሰብሰቢያ አዳራሾችን እንዲሁም ቅርንጫፍ ቢሮዎችን መገንባትንና መጠገንን ትልቅ መብት እንደሆነ አድርገን እንመለከተዋለን። በአደጋ ምክንያት ቤት ንብረታቸውን ያጡ ሰዎችን መርዳትን በተመለከተም ተመሳሳይ ስሜት አለን። በማንኛውም ጊዜ ቢሆን ለምናከናውነው ሥራ የሚያስፈልገው ብቃት እንዲኖረን እንፈልጋለን፤ አለበለዚያ ቀላል የሚመስሉ ሥራዎችን በምናከናውንበት ጊዜ እንኳ በእኛም ሆነ በሌሎች ላይ ጉዳት ልናደርስ እንችላለን። (መክ. 10:9) በእርግጥም ጉዳት በማያስከትል መንገድ ሥራችንን የማከናወን ልማድ ካዳበርን አደጋዎችን ማስቀረት እንችላለን።

መጽሐፍ ቅዱስ “የጎልማሶች ክብር ብርታታቸው፣ የሽማግሌዎችም ሞገስ ሽበታቸው ነው” ይላል። (ምሳሌ 20:29) ከባድ የሆኑ ሥራዎችን ለማከናወን የወጣት ጉልበት ያስፈልጋል። በዕድሜ የገፉና በግንባታ ሥራ ልምድ ያካበቱ ሠራተኞች ደግሞ በእጃቸውም ሆነ በመሣሪያዎች በመጠቀም ጥቃቅን የሆኑ የማጠናቀቂያ ሥራዎችን ያከናውናሉ። እነዚህ በዕድሜ የገፉ ሰዎች ወጣት በነበሩበት ወቅት ከባድ ሥራዎችን ያከናውኑ ነበር። አዲስ ፈቃደኛ ሠራተኛ ከሆንክ ልምድ ያላቸው ሠራተኞች ሥራቸውን እንዴት እንደሚያከናውኑ ልብ ብለህ ተመልከት፤ እንዲሁም የሚሰጡህን መመሪያ ተከተል። ለመማር ፈቃደኛ ከሆንክ በግንባታ ሥራ ልምድ ያላቸው ወንድሞች ብዙ ነገሮች ያስተምሩሃል። የሚሰጡህ ሥልጠና፣ አደጋ ሊያስከትሉ የሚችሉ ቁሳቁሶችን ጉዳት በማያደርስ መልኩ መያዝ እንዲሁም ከባድ ነገሮችን በጥንቃቄ ማንሳት የምትችልበትን መንገድ ማስተማርን ይጨምራል። እንዲህ ዓይነት ሥልጠና ማግኘትህ ሥራህን ውጤታማ በሆነና ጉዳት በማያስከትል መንገድ እንዲሁም በደስታ ለማከናወን ያስችልሃል።

ግንባታ በሚካሄድባቸው ቦታዎች ላይ የሚሠሩ ሰዎች ምንጊዜም መዘናጋት የለባቸውም። እንዲህ ባሉ ቦታዎች ላይ በአጭር ጊዜ ውስጥ ብዙ ነገሮች ሊቀያየሩ ይችላሉ። ትናንት ምንም ያልነበረበት መሬት ዛሬ ተቆፍሮ ሊሆን ይችላል። በግንባታ ቡድኑ ውስጥ ያሉ ሌሎች ሰዎች አንድን መሰላል ወይም ጣውላ አሊያም የቀለም ቆርቆሮ ከተቀመጠበት አንስተው ሌላ ቦታ አድርገውት ሊሆን ይችላል። ነገሮችን አስተውለህ የማትንቀሳቀስ ከሆነ በቀላሉ ጉዳት ሊደርስብህ ይችላል። የጥንቃቄና የደኅንነት ደንቦች እንደሚገልጹት በግንባታ ቦታ ላይ ያሉ ሠራተኞች ራሳቸውን ከአደጋ ለመጠበቅ የሚረዱ ቁሳቁሶችን መጠቀም አለባቸው። በግንባታ ቦታ ላይ ስትሆን የዓይን መከላከያ መነጽር፣ ጠንካራ ቆብ እንዲሁም ለሥራ ተስማሚ የሆነ ጫማ ማድረግህ ከብዙ አደጋዎች ይጠብቅሃል። እርግጥ ነው፣ እነዚህ ቁሳቁሶች ከአደጋ ሊከላከሉልህ የሚችሉት በጥሩ ሁኔታ ላይ የሚገኙና የምትጠቀምባቸው ከሆነ ብቻ ነው።

አብዛኞቹ መሣሪያዎች ለመጠቀም ቀላል ቢመስሉም በእነዚህ መሣሪያዎች ጉዳት በማያስከትልና በተገቢ መንገድ ለመጠቀም ሥልጠናና ልምምድ ያስፈልጋል። በአንድ መሣሪያ መጠቀም ብትፈልግና ልምዱ ባይኖርህ ሥራውን ለሚቆጣጠረው ወንድም ሁኔታውን ንገረው። አስፈላጊውን ሥልጠና እንድታገኝ ዝግጅት ያደርግልሃል። ትሑት መሆን ወይም አቅምን ማወቅ አስፈላጊ ባሕርይ ነው። እንዲያውም በራስህም ሆነ በግንባታ ቦታ ላይ ባሉ ሌሎች ሰዎች ላይ ጉዳት እንዳታደርስ ይህን ባሕርይ ማዳበርህ የግድ ነው።—ምሳሌ 11:2

በግንባታ ሥራዎች ላይ ለሚያጋጥሙት ጉዳቶች ዋነኛው መንስኤ መውደቅ ነው። መሰላል ወይም ለመወጣጫ የሚያገለግሉ ከበሌቶዎች (scaffolding) ላይ ከመውጣትህ በፊት እነዚህ ነገሮች በደንብ መጥበቃቸውንና በጥሩ ይዞታ ላይ የሚገኙ መሆኑን አረጋግጥ። በከበሌቶዎች ላይ ሆነህ የምትሠራ ከሆነ ሰውነትህን አቅፎ የሚይዝና ከከበሌቶው ጋር የሚታሠር ቀበቶ ማድረግ እንዲሁም ጣሪያ ላይ ሆነህ የምትሠራ ከሆነ እንዳትወድቅ በጣሪያው ዙሪያ መከታ ማድረግ ያስፈልግህ ይሆናል። በከፍታ ቦታ ላይ መሥራትን በተመለከተ ጥያቄ ካለህ ሥራውን በበላይነት የሚቆጣጠረውን ወንድም ጠይቀው። *

በዓለም ዙሪያ የይሖዋ አገልጋዮች ቁጥር እየጨመረ በሄደ መጠን የመንግሥት አዳራሾችንና እውነተኛውን አምልኮ ለማስፋፋት የሚያገለግሉ ሌሎች ሕንፃዎችን መገንባት የግድ ይላል። የመንግሥት አዳራሾችንም ሆነ ሌሎች ተመሳሳይ ሕንፃዎችን የመገንባቱን ሥራ በበላይነት የሚቆጣጠሩት ወንድሞች በእነሱ ሥር ሆነው የሚያገለግሉትን የይሖዋ ውድ በጎች የመጠበቅ ኃላፊነት አለባቸው። (ኢሳ. 32:1, 2) በግንባታ ፕሮጀክቶች ላይ የሚሠሩትን ወንድሞችና እህቶች የመቆጣጠር ኃላፊነት ከተሰጠህ የሠራተኞቹን ደኅንነት መጠበቅ ትልቅ ቦታ እንደሚሰጠው ፈጽሞ አትዘንጋ። የሥራ አካባቢን በንጽሕና መያዝ እንዲሁም እንዳይዝረከረክ ማድረግ ያስፈልጋል። ጉዳት በማያስከትል መንገድ መሥራትን በተመለከተ ማሳሰቢያ የሚያስፈልጋቸው ካሉ በደግነት ሆኖም ጠንከር ባለ መንገድ ንገራቸው። ልጆች ወይም ልምድ የሌላቸው ሠራተኞች አደጋ ሊያስከትሉ ወደሚችሉ ቦታዎች እንዲጠጉ አትፍቀድ። ሠራተኞቹ ሊያጋጥማቸው የሚችለውን አደጋ አስቀድመህ በማሰብ ጉዳት በማያስከትል መንገድ ተጠንቅቀው እንዲሠሩ አሳስባቸው። ዓላማችን ምንም ጉዳት ሳይደርስ ሥራውን ማጠናቀቅ እንደሆነ አስታውስ።

ፍቅር የሚጫወተው ሚና

የመንግሥት አዳራሾችንና ለእውነተኛው አምልኮ የሚያገለግሉ ሌሎች ሕንፃዎችን መገንባት አደጋ ሊያስከትሉ በሚችሉ ሥራዎች መሳተፍን ይጠይቃል። በመሆኑም እንደነዚህ ባሉት ሥራዎች የሚካፈሉት ሰዎች ጠንቃቃ መሆን አለባቸው። የመጽሐፍ ቅዱስን መሠረታዊ ሥርዓቶች የምታከብር፣ ለሥራው የወጣውን መመሪያ የምትታዘዝ እንዲሁም በማመዛዘን ችሎታ የምትጠቀም ከሆነ ራስህን ብሎም አብረውህ የሚሠሩትን ሰዎች ከጉዳት ትጠብቃለህ።

ደኅንነትን ለመጠበቅ ከፍተኛ ቦታ እንድንሰጥ የሚያነሳሳን ዋነኛው ነገር ምንድን ነው? ፍቅር ነው። ለይሖዋ ያለን ፍቅር ልክ እንደ እሱ ሕይወትን ውድ አድርገን እንድንመለከት ይገፋፋናል። እንዲሁም ለሰዎች ያለን ፍቅር ግድ የለሾች በመሆን እነሱን ጉዳት ላይ ሊጥላቸው የሚችል ማንኛውንም ነገር ከማድረግ እንድንቆጠብ ያደርገናል። (ማቴ. 22:37-39) እንግዲያው ግንባታ በምናከናውንበት ጊዜ የሁሉም ሰው ‘ደኅንነት’ እንዲጠበቅ የተቻለንን ሁሉ እናድርግ።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.14 “መሰላል በምትጠቀምበት ጊዜ ራስህን ከአደጋ መጠበቅ የምትችለው እንዴት ነው?” የሚለውን በገጽ 30 ላይ የሚገኘውን ሣጥን ተመልከት።

[በገጽ 30 ላይ የሚገኝ ሣጥን/ሥዕል]

መሰላል በምትጠቀምበት ጊዜ ራስህን ከአደጋ መጠበቅ የምትችለው እንዴት ነው?

በቅርቡ በአንድ ዓመት ውስጥ በዩናይትድ ስቴትስ ከ160,000 የሚበልጡ ሠራተኞች ከመሰላል በመውደቃቸው ጉዳት ደርሶባቸዋል። ከዚህም በተጨማሪ 150 ገደማ የሚሆኑ ሰዎች ከመሰላል ላይ በመውደቃቸው ሕይወታቸውን አጥተዋል። የምትኖረውም ሆነ የምትሠራው የትም ይሁን የት መሰላል በምትጠቀምበት ጊዜ ራስህን ከአደጋ ለመጠበቅ የሚረዱህ አንዳንድ መመሪያዎች ከዚህ በታች ቀርበዋል።

◇ የሚነቃነቅ ወይም በትክክል የማይሠራ መሰላል አትጠቀም፤ እንዲህ ያለውን መሰላል ለማደስ ከመሞከር ይልቅ አስወግደው።

◇ ማንኛውም መሰላል ቢሆን የመሸከም አቅሙ ውስን መሆኑን አትዘንጋ። የምትይዛቸው መሣሪያዎችና ቁሳቁሶች ክብደት ከአንተ ክብደት ጋር ተዳምሮ ከመሰላሉ የመሸከም አቅም በላይ እንዳይሆን ተጠንቀቅ።

◇ መሰላሉን በደንብ እንዲረግጥ አድርገህ በማይሰምጥ ቦታ ላይ አቁመው። ከበሌቶ ላይ በተዘረጋ ጣውላ ወይም በባልዲዎች፣ ሣጥኖችና በመሳሰሉት አስተማማኝ ያልሆኑ ነገሮች ላይ መሰላሉን አታቁመው።

◇ መሰላል ላይ ስትወጣም ሆነ ስትወርድ ምንጊዜም ፊትህን ወደ መሰላሉ አዙር።

◇ ማንኛውንም መሰላል ስትጠቀም ከላይ ባሉት ሁለት የመጨረሻ ደረጃዎች ላይ አትቁም ወይም አትቀመጥ።

◇ ጣሪያ ወይም አንድ ከፍ ያለ ነገር ላይ ለመውጣት ወይም ከዚያ ላይ ለመውረድ በመሰላል በምትጠቀምበት ጊዜ መሰላልህ፣ ከሚያርፍበት ቦታ ወይም ከጣሪያው ጠርዝ ቢያንስ አንድ ሜትር መርዘም አለበት። መሰላሉ እንዳይንሸራተት እግሩን ከሆነ ነገር ጋር እሰረው ወይም እግሩ ሥር ማገጃ ጣውላ አድርግ። ይህን ማድረግ የማይቻል ከሆነ መሰላል ላይ ሆነህ በምትሠራበት ወቅት አንድ ሰው መሰላሉን እንዳይነቃነቅ አድርጎ እንዲይዝልህ አድርግ። መሰላሉ ወደ ጎን እንዳይንሸራተት የመሰላሉን የላይኛውን ጫፍ ከአንድ ነገር ጋር አጥብቀህ እሰረው።

◇ በመሰላሉ ደረጃ ላይ ጣውላ አጋድመህ እንደ ጠረጴዛ መጠቀም ተገቢ አይደለም።

◇ በመሰላል ላይ ሆነህ እየሠራህ አንድ ነገር ላይ ለመድረስ መንጠራራት መሰላሉ ሚዛኑን እንዳይጠብቅ ሊያደርገው ይችላል። በዚህ መንገድ መንጠራራት አደገኛ ስለሆነ እንዲህ ከማድረግ ተቆጠብ። መሰላሉን ወደምትሠራው ነገር ለማቅረብ በተደጋጋሚ ማስጠጋት ቢኖርብህም እንዲህ ማድረጉ የተሻለ ነው።

◇ በተዘጋ በር ፊት ለፊት በቆመ መሰላል ላይ ወጥተህ መሥራት ካለብህ በሩ ላይ ምልክት አንጠልጥል እንዲሁም በሩን ቆልፈው። በሩን መቆለፍ የማይቻል ከሆነ በዚያ በኩል የሚያልፉትን እንዲያስጠነቅቅልህ አንድ ሰው አቁም።

◇ መሰላሉ በአንድ ጊዜ ሁለት ሠራተኞች እንዲወጡበት ታስቦ የተሠራ እስካልሆነ ድረስ በአንድ መሰላል ላይ ከአንድ ሰው በላይ መውጣት የለበትም። *

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.33 በነሐሴ 1999 ንቁ! ከገጽ 20-22 ላይ በመሰላል መጠቀምን በተመለከተ ተጨማሪ ሐሳቦች ቀርበዋል።

[በገጽ 29 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

የሙሴ ሕግ ጠፍጣፋ በሆነ ጣሪያ ዙሪያ መከታ እንዲበጅ ያዝዝ ነበር