በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ክርስቲያን ቤተሰቦች “ዝግጁ ሆናችሁ ጠብቁ”

ክርስቲያን ቤተሰቦች “ዝግጁ ሆናችሁ ጠብቁ”

ክርስቲያን ቤተሰቦች “ዝግጁ ሆናችሁ ጠብቁ”

“የሰው ልጅ ይመጣል ብላችሁ ባላሰባችሁት ሰዓት ስለሚመጣ ዝግጁ ሆናችሁ ጠብቁ።”​—ሉቃስ 12:40

1, 2. “ዝግጁ ሆናችሁ ጠብቁ” የሚለውን የኢየሱስ ማሳሰቢያ ልብ ማለታችን አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?

‘የሰው ልጅ⁠ በክብሩ በሚመጣበትና ሰዎችን አንዱን ከሌላው በሚለይበት’ ጊዜ አንተና ቤተሰብህ ምን ያጋጥማችሁ ይሆን? (ማቴ. 25:31, 32) ይህ የሚሆነው ባላሰብንበት ሰዓት በመሆኑ “ዝግጁ ሆናችሁ ጠብቁ” የሚለውን ኢየሱስ የሰጠውን ማሳሰቢያ ልብ ማለታችን ምንኛ አስፈላጊ ነው!​—ሉቃስ 12:40

2 የመጀመሪያው የጥናት ርዕስ፣ እያንዳንዱ የቤተሰብ አባል የራሱን ኃላፊነት በቁም ነገር በመመልከት መላው ቤተሰብ በመንፈሳዊ ነቅቶ እንዲኖር መርዳት የሚችለው እንዴት እንደሆነ አብራርቶ ነበር። እስቲ አሁን ደግሞ ለቤተሰባችን መንፈሳዊ ደኅንነት አስተዋጽኦ ማድረግ የምንችልባቸውን ሌሎች መንገዶች እንመልከት።

ዓይናችሁ ምንጊዜም “አጥርቶ የሚያይ” ይሁን

3, 4. (ሀ) ክርስቲያን ቤተሰቦች ምን እንዳይሆኑ መጠንቀቅ አለባቸው? (ለ) ዓይናችን “አጥርቶ የሚያይ” መሆን አለበት ሲባል ምን ማለት ነው?

3 ቤተሰቦች፣ ክርስቶስ በሚመጣበት ጊዜ ዝግጁ ሆነው መገኘት እንዲችሉ ከእውነተኛው አምልኮ ጋር ለተያያዙ ጉዳዮች ትኩረት እንዳይሰጡ እንቅፋት የሚሆኑባቸውን ነገሮች ማስወገድ አለባቸው። ትኩረት የሚከፋፍሉ ነገሮች ከይሖዋ አገልግሎት እንዳያርቋቸው መጠንቀቅ ይኖርባቸዋል። ጥቂት የማይባሉ ቤተሰቦች በፍቅረ ንዋይ ወጥመድ ወድቀዋል፤ በመሆኑም ኢየሱስ ዓይናችን “አጥርቶ የሚያይ” እንዲሆን ስለማድረግ የሰጠውን ምክር ልብ ማለታችን አስፈላጊ ነው። (ማቴዎስ 6:22, 23አንብብ።) መብራት መንገዳችን በደንብ እንዲታየንና ሳንደናቀፍ መራመድ እንድንችል እንደሚረዳን ሁሉ በምሳሌያዊ ‘የልባችን ዓይኖች’ በመጠቀም የምናስገባው የእውቀት ብርሃንም ነገሮች ፍንትው ብለው እንዲታዩን ይረዳናል፤ ይህም ሳንደናቀፍ እንድንመላለስ ያስችለናል።​—ኤፌ. 1:18

4 ዓይናችን አጥርቶ ማየት እንዲችል ጤናማ መሆንና በሚያየው ነገር ላይ ትኩረት ማድረግ መቻል አለበት። ከልባችን ዓይን ጋር በተያያዘም ሁኔታው ተመሳሳይ ነው። ምሳሌያዊ ዓይናችን አጥርቶ የሚያይ መሆን አለበት ሲባል በአንድ ዓላማ ላይ ብቻ ያተኮረ ይሆናል ማለት ነው። በቁሳዊ ነገሮች ላይ ያተኮረ ሕይወት ከመምራት እንዲሁም የቤተሰባችንን ሥጋዊ ፍላጎት ብቻ በማሟላት ከመጠመድ ይልቅ ዓይናችን ምንጊዜም በመንፈሳዊ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ይሆናል። (ማቴ. 6:33) እንዲህ ሲባል ባሉን መሠረታዊ ነገሮች ረክተን በመኖር በሕይወታችን ውስጥ ለአምላክ አገልግሎት የመጀመሪያውን ቦታ እንሰጣለን ማለት ነው።​—ዕብ. 13:5

5. በአሥራዎቹ ዕድሜ ላይ የምትገኝ አንዲት ወጣት ‘ዓይኗ’ አምላክን በማገልገል ላይ ያተኮረ መሆኑን ያሳየችው እንዴት ነው?

5 ልጆች ዓይናቸው አጥርቶ የሚያይ እንዲሆን ማሠልጠን እንዴት ያለ ግሩም ውጤት ያስገኛል! በኢትዮጵያ የምትኖር በአሥራዎቹ ዕድሜ ላይ የምትገኝ የአንዲት ወጣትን ምሳሌ እንመልከት። የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቷን ስታጠናቅቅ በጣም ጥሩ ውጤት ስላመጣች የነፃ ትምህርት ዕድል አገኘች። ይሁንና ዓይኗ ያተኮረው ይሖዋን በማገልገል ላይ ስለነበር ይህን ዕድል ሳትቀበል ቀረች። ከዚያ ብዙም ሳይቆይ በወር 3,000 ዩሮ (ከ67,000 ብር በላይ) ክፍያ ያለው ሥራ አገኘች፤ ይህ በምትኖርበት አገር አብዛኛው ሰው ከሚያገኘው ደሞዝ አንጻር በጣም ከፍተኛ ነው። ያም ሆኖ የዚህች ወጣት “ዓይን” ያተኮረው በአቅኚነት አገልግሎት ላይ ነበር። ይህን ሥራ ላለመቀበል ስትወስን ወላጆቿን ማማከር አላስፈለጋትም። ወላጆቿ ልጃቸው የወሰደችውን እርምጃ ሲያውቁ ምን ተሰማቸው? በጣም የተደሰቱ ከመሆኑም ሌላ እንደሚኮሩባት ገለጹላት!

6, 7. በየትኛው ወጥመድ እንዳንወድቅ ‘መጠንቀቅ’ አለብን?

6 በ⁠ማቴዎስ 6:22, 23 ላይ ተመዝግቦ የሚገኘው ኢየሱስ የተናገረው ነገር ከስግብግብነት እንድንርቅ የሚያስጠነቅቅ ሐሳብ ያስተላልፋል። ኢየሱስ “አጥርቶ የሚያይ” ዓይንን ያነጻጸረው አጥርቶ ከማያይ ጋር ሳይሆን ‘ከሚቅበዘበዝ’ ዓይን ጋር ነው። መጽሐፍ ቅዱስ መጀመሪያ በተጻፈበት ቋንቋ “የሚቅበዘበዝ” ተብሎ የተተረጎመው ቃል “ክፉ” የሚል ቀጥተኛ ትርጉም አለው። ‘ክፉ ዓይን’ ሲባል የሚጎመጅ ወይም የሚስገበገብ ዓይንን ያመለክታል። (ማቴ. 6:23የግርጌ ማስታወሻ) ታዲያ ይሖዋ መጎምጀትን ወይም ስግብግብነትን እንዴት ይመለከተዋል? መጽሐፍ ቅዱስ “ዝሙትና ማንኛውም ዓይነት ርኩሰት ወይም ስግብግብነት በመካከላችሁ ከቶ አይነሳ” ይላል።​—ኤፌ. 5:3

7 ሌሎች ስግብግብ እንደሆኑ ለማስተዋል ጊዜ ባይወስድብንም እኛ ራሳችን እንዲህ ያለ ባሕርይ እንዳለን ማስተዋል ግን ቀላል አይደለም። በመሆኑም “ተጠንቀቁ፤ ከመጎምጀትም ሁሉ ተጠበቁ” የሚለውን የኢየሱስን ምክር መከተል የጥበብ አካሄድ ነው። (ሉቃስ 12:15) ይህም ልባችን በምን ላይ እንዳተኮረ ለማወቅ ራሳችንን መመርመርን ይጠይቃል። ክርስቲያን ቤተሰቦች በመዝናኛ እንዲሁም ቁሳዊ ነገሮችን በመግዛት ስለሚያጠፉት ጊዜና ገንዘብ በቁም ነገር ማሰብ አለባቸው።

8. የተለያዩ ነገሮችን ከመግዛት ጋር በተያያዘ “ተጠንቀቁ” የሚለውን ምክር ተግባራዊ ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው?

8 አንድ ነገር ለመግዛት ስትነሱ አቅሜ ይፈቅዳል አይፈቅድም የሚለውን ከማሰብ ባለፈ ግምት ውስጥ ልታስገቡት የሚገባ ነገር አለ። እንደሚከተሉት ያሉ ጉዳዮችን ቆም ብላችሁ አስቡባቸው፦ ‘ይህን ዕቃ ያን ያህል እንጠቀምበታለን? ዕቃውን በጥሩ ሁኔታ ለመያዝ የሚያስፈልገውን ሁሉ ለማድረግ ጊዜ ይኖረናል? አጠቃቀሙን በሚገባ ለመረዳትስ ምን ያህል ጊዜ ይፈጅብናል?’ እናንተ ወጣቶች፣ በማስታወቂያ ላይ በሚታዩ ዓለም የሚያቀርባቸው የተለያዩ ነገሮች ተታልላችሁ ውድ የሆኑ ልብሶችን ወይም ሌሎች ዕቃዎችን እንዲገዙላችሁ ወላጆቻችሁን አትወትውቱ። ራስን የመግዛት ባሕርይ አዳብሩ። በተጨማሪም ያሰባችሁትን ዕቃ መግዛታችሁ ቤተሰባችሁ የሰው ልጅ በሚመጣበት ጊዜ ዝግጁ በመሆኑ ላይ ምን ተጽዕኖ እንደሚያሳድር ቆም ብላችሁ አስቡ። ይሖዋ “ፈጽሞ አልተውህም፣ በምንም ዓይነት አልጥልህም” ብሎ በገባው ቃል ላይ እምነት ይኑራችሁ።​—ዕብ. 13:5

መንፈሳዊ ግቦች ላይ ለመድረስ ጥረት አድርጉ

9. ቤተሰቦች መንፈሳዊ ግቦችን መከታተላቸው ምን ጥቅም ያስገኝላቸዋል?

9 የቤተሰብ አባላት እምነታቸውን ማጠናከርና ለመላው ቤተሰብ መንፈሳዊ ደኅንነት አስተዋጽኦ ማበርከት የሚችሉበት ሌላው መንገድ ደግሞ መንፈሳዊ ግቦችን ማውጣትና እነዚህ ግቦች ላይ ለመድረስ ጥረት ማድረግ ነው። ቤተሰቦች እንዲህ ማድረጋቸው ይሖዋን ለማስደሰት ያላቸውን ፍላጎት ምን ያህል እያሳኩ እንደሆነ ለመገምገም እንዲሁም በሕይወታቸው ውስጥ ትልቅ ቦታ ሊሰጣቸው የሚገቡ ነገሮች የትኞቹ እንደሆኑ ለመወሰን ያስችላቸዋል።​—ፊልጵስዩስ 1:10ን አንብብ።

10, 11. በቤተሰብ ደረጃ የትኞቹ መንፈሳዊ ግቦች ላይ ለመድረስ ጥረት እያደረጋችሁ ነው? ወደፊትስ ምን ግቦች ለማውጣት አስባችኋል?

10 እያንዳንዱ የቤተሰብ አባል ሊደርስባቸው የሚችል ምክንያታዊ የሆኑ ቀለል ያሉ ግቦችን እንኳ ማውጣት ከፍተኛ ጥቅም ያስገኛል። በየቀኑ በዕለቱ ጥቅስ ላይ መወያየትን እንደ ምሳሌ እንውሰድ። አንድ የቤተሰብ ራስ፣ የቤተሰቡ አባላት የሚሰጧቸውን ሐሳቦች ማዳመጡ መንፈሳዊነታቸው ምን ደረጃ ላይ እንዳለ ለማስተዋል ይረዳዋል። በቤተሰብ ደረጃ መጽሐፍ ቅዱስን አዘውትሮ የማንበብ ግብ ማውጣት፣ ልጆች የንባብ ችሎታቸውን እንዲያሻሽሉና የመጽሐፍ ቅዱስ እውቀታቸው እንዲዳብር የሚያስችል ግሩም አጋጣሚ ይፈጥራል። (መዝ. 1:1, 2) የጸሎታችንን ይዘት ማሻሻልንስ ግባችን ልናደርገው አይገባም? የመንፈስ ፍሬ ገጽታዎችን ይበልጥ ለማፍራት መጣርም ልናወጣቸው ከምንችላቸው ግሩም ግቦች መካከል አንዱ ነው። (ገላ. 5:22, 23) በአገልግሎት የምናገኛቸውን ሰዎች ስሜት መረዳትን በተመለከተስ ምን ማለት ይቻላል? በቤተሰብ ደረጃ ይህን ለማድረግ መጣር ልጆች ርኅራኄን እንዲያዳብሩ የሚረዳቸው ከመሆኑም ሌላ የዘወትር አቅኚ፣ ልዩ አቅኚ ወይም ሚስዮናዊ የመሆን ፍላጎት እንዲያድርባቸው ሊያደርግ ይችላል።

11 አንተም ሆንክ የቤተሰብህ አባላት የትኞቹ ግቦች ላይ ለመድረስ ጥረት ማድረግ እንደምትችሉ ለምን ቆም ብለህ አታስብም? ቤተሰባችሁ በአገልግሎት የበለጠ ጊዜ ለማሳለፍ ግብ ማውጣት ይችል ይሆን? በስልክ፣ በመንገድ ላይ ወይም በንግድ ቦታዎች በመመሥከር ረገድ ፍርሃታችሁን ለማሸነፍ ጥረት ማድረግ ትችሉ ይሆን? የመንግሥቱ አስፋፊዎች ይበልጥ ወደሚያስፈልጉባቸው ቦታዎች ሄዶ ስለ ማገልገልስ አስባችሁበት ታውቃላችሁ? አንድ የቤተሰባችሁ አባል ምሥራቹን ለሌላ አገር ሰዎች ለማካፈል ሲል አዲስ ቋንቋ መማር ይችል ይሆን?

12. የቤተሰብ ራሶች ቤተሰባቸው በመንፈሳዊ እድገት እንዲያደርግ ለመርዳት ምን ማድረግ ይችላሉ?

12 የቤተሰብ ራስ እንደመሆንህ መጠን ቤተሰብህ በየትኞቹ አቅጣጫዎች መንፈሳዊ እድገት ማድረግ እንደሚችል ለይተህ እወቅ። ከዚያም ይህን ለማሳካት የሚያስችሏችሁን ግቦች አውጣ። በቤተሰብ ደረጃ የምታወጧቸው ግቦች ምክንያታዊ እንዲሁም ሁኔታችሁንና አቅማችሁን ያገናዘቡ ብሎም ልትደርሱባቸው የምትችሉ ሊሆኑ ይገባል። (ምሳሌ 13:12) እርግጥ ነው፣ ጠቃሚ የሆነ ግብ ላይ ለመድረስ ጊዜ ይጠይቃል። በመሆኑም ቴሌቪዥን ለመመልከት ከምታጠፉት ሰዓት ላይ ጊዜ በመግዛት ለመንፈሳዊ እንቅስቃሴዎች አውሉት። (ኤፌ. 5:15, 16) ለቤተሰባችሁ ያወጣችኋቸው ግቦች ላይ ለመድረስ ተግታችሁ ሥሩ። (ገላ. 6:9) መንፈሳዊ ግቦች ላይ ለመድረስ የሚጣጣር ቤተሰብ እድገቱ “በሁሉም ሰዎች ዘንድ በግልጽ [ይታያል]።”​—1 ጢሞ. 4:15

የቤተሰብ አምልኮ የምታደርጉበት ቋሚ ምሽት ይኑራችሁ

13. በሳምንታዊ የጉባኤ ስብሰባ ፕሮግራሞች ላይ ምን ለውጥ ተደርጓል? የትኞቹን ጥያቄዎች ልናስብባቸው ይገባል?

13 ቤተሰቦች የሰው ልጅ በሚመጣበት ጊዜ ‘ዝግጁ ሆነው እንዲጠብቁ’ ከሚረዷቸው ግሩም ዝግጅቶች አንዱ ከጥር 1, 2009 ጀምሮ በሳምንታዊ የስብሰባ ፕሮግራሞች ላይ የተደረገው ትልቅ ለውጥ ነው። ቀደም ሲል የጉባኤ የመጽሐፍ ጥናት ተብሎ ይጠራ የነበረው ስብሰባ ራሱን ችሎ መደረጉ ቀርቶ ከቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤትና ከአገልግሎት ስብሰባ ጋር አንድ ላይ እንዲካሄድ መደረጉ አንድ ትርፍ ቀን እንድናገኝ አስችሎናል። ይህ ማስተካከያ የተደረገው ክርስቲያን ቤተሰቦች በየሳምንቱ ለቤተሰብ አምልኮ የሚሆን አንድ ምሽት በመመደብ መንፈሳዊነታቸውን እንዲያጠናክሩ አጋጣሚ ለመስጠት ታስቦ ነው። ይህ ለውጥ ከተደረገ የተወሰነ ጊዜ ስላለፈ እንደሚከተለው ብለን ራሳችንን መጠየቅ እንችላለን፦ ‘ለቤተሰብ አምልኮ ወይም ለግል ጥናት እንድናውለው የተሰጠንን ጊዜ በአግባቡ እየተጠቀምኩበት ነው? ይህ ዝግጅት የተደረገበት ዓላማ ግቡን እንዲመታ በማድረግ ረገድ ተሳክቶልኛል?’

14. (ሀ) የቤተሰብ አምልኮ ወይም የግል ጥናት በቋሚነት የምናደርግበት ዋነኛ ዓላማ ምንድን ነው? (ለ) ለጥናት የሚሆን አንድ ምሽት መመደባችን በጣም አስፈላጊ ነው የምንለው ለምንድን ነው?

14 የቤተሰብ አምልኮ ወይም የግል ጥናት በቋሚነት የምናደርግበት ዋነኛ ዓላማ ወደ ይሖዋ ይበልጥ መቅረብ ነው። (ያዕ. 4:8) መጽሐፍ ቅዱስን አዘውትረን ለማጥናት ጊዜ ስንመድብና ስለ ፈጣሪያችን ያለንን እውቀት ስናሳድግ ከእሱ ጋር ያለን ዝምድና ይጠናከራል። ወደ ይሖዋ ይበልጥ በተጠጋን መጠን እሱን ‘በሙሉ ልባችን፣ በሙሉ ነፍሳችን፣ በሙሉ አእምሯችንና በሙሉ ኃይላችን’ ለመውደድ እንነሳሳለን። (ማር. 12:30) አምላክን ለመውደድና እሱን ለመምሰል እንደምንጓጓ ምንም ጥርጥር የለውም። (ኤፌ. 5:1) እንግዲያው አስቀድሞ የተነገረውን “ታላቅ መከራ” መምጣት በምንጠባበቅበት በአሁኑ ጊዜ፣ ሁሉም የቤተሰብ አባላት በመንፈሳዊ ‘ዝግጁ ሆነው ለመጠበቅ’ እንዲችሉ ለመርዳት ቁልፉ ቋሚ የቤተሰብ አምልኮ ማድረግ ነው። (ማቴ. 24:21) እንዲህ ማድረጋችን ለመዳን ወሳኝ ነው።

15. የቤተሰብ አምልኮ ዝግጅት የቤተሰብ አባላት አንዳቸው ለሌላው በሚኖራቸው አመለካከት ላይ ምን ለውጥ ያመጣል?

15 የቤተሰብ አምልኮ ዝግጅት ሌላም ዓላማ አለው፤ ይኸውም ቤተሰቡ እርስ በርስ እንዲቀራረብ ይረዳል። ቤተሰቦች መንፈሳዊ ነገሮችን አንስተው በመወያየት በየሳምንቱ አብረው ጊዜ ማሳለፋቸው አንዳቸው ለሌላው በሚኖራቸው አመለካከት ላይ ትልቅ ለውጥ ያመጣል። ባለትዳሮች አብረው ሲያጠኑ ያገኟቸውን ውድ መንፈሳዊ ዕንቁዎች በተመለከተ የትዳር ጓደኛቸው የተሰማውን ደስታ ሲገልጽ መስማታቸው በመካከላቸው ልዩ ቅርርብ እንደሚፈጥር ምንም ጥርጥር የለውም! (መክብብ 4:12ን አንብብ።) ወላጆችና ልጆች አብረው ይሖዋን ሲያመልኩ “ፍጹም የሆነ የአንድነት ማሰሪያ” በሆነው ፍቅር ላይ የተመሠረተ አንድነት ይኖራቸዋል።​—ቆላ. 3:14

16. ሦስት እህቶች መጽሐፍ ቅዱስን ለማጥናት አንድ ምሽት በመመደባቸው እንዴት እንደተጠቀሙ ተናገር።

16 ሦስት እህቶች ለመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት የሚሆን አንድ ምሽት እንድንመድብ በተደረገው ዝግጅት እንዴት እንደተጠቀሙ እንመልከት። መበለት የሆኑት እነዚህ በዕድሜ የገፉ እህቶች የሥጋ ዝምድና ባይኖራቸውም ለረጅም ዓመታት የዘለቀ ወዳጅነት ነበራቸው፤ የሚኖሩትም በአንድ ከተማ ውስጥ ነው። እነዚህ የሚዋደዱ ጓደኛሞች አብረው የበለጠ ጊዜ ለማሳለፍ እንዲሁም በማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ብቻ ከማተኮር ይልቅ እግረ መንገዳቸውን መንፈሳዊ ጥቅም ለማግኘት ስለፈለጉ አንድ ምሽት ላይ እየተገናኙ መጽሐፍ ቅዱስን ለማጥናት ወሰኑ። በዚህም መሠረት ስለ አምላክ መንግሥት ‘የተሟላ ምሥክርነት መስጠት’ * የተባለውን መጽሐፍ ማጥናት ጀመሩ። ከእነዚህ እህቶች አንደኛዋ እንዲህ ብለዋል፦ “አብረን የምናሳልፈው ጊዜ በጣም ስለሚያስደስተን ብዙ ጊዜ ጥናታችን ከአንድ ሰዓት በላይ ይወስዳል። በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበሩ ወንድሞቻችን የነበሩበትን ሁኔታ በዓይነ ሕሊናችን ለመሳል እንሞክራለን፤ እንዲሁም እኛ እንደ እነሱ ዓይነት ሁኔታ ቢያጋጥመን ምን እናደርግ እንደነበር እንወያያለን። ከዚያም ከውይይታችን ያገኘናቸውን ነጥቦች በአገልግሎት ላይ ተግባራዊ ለማድረግ እንሞክራለን። ይህም የመንግሥቱን ምሥራች የመስበኩና ደቀ መዛሙርት የማድረጉ ሥራ ከምንጊዜውም ይበልጥ አስደሳችና ፍሬያማ እንዲሆንልን ረድቶናል።” ይህ ዝግጅት የእነዚህን ሦስት ጓደኛሞች መንፈሳዊ እውቀት ያሳደገላቸው ከመሆኑም ሌላ እርስ በርስ ይበልጥ እንዲቀራረቡ አድርጓቸዋል። “ይህን ዝግጅት በጣም ወደነዋል” ብለዋል።

17. ለቤተሰብ አምልኳችሁ መሳካት የትኞቹ ነገሮች አስተዋጽኦ ያደርጋሉ?

17 አንተስ? ለቤተሰብ አምልኮ ወይም ለግል ጥናት አንድ ምሽት እንድንመድብ ከተደረገው ዝግጅት ምን ያህል እየተጠቀምክ ነው? ፕሮግራማችን ያዝ ለቀቅ ዓይነት ከሆነ ይህ ዝግጅት የታለመለትን ግብ ሊመታ አይችልም። እያንዳንዱ የቤተሰብ አባል ለጥናት በተመደበው ጊዜ ዝግጁ ሆኖ መገኘት ይኖርበታል። ጥቃቅን ጉዳዮች የአምልኮ ምሽታችሁን እንዲያስተጓጉሉባችሁ መፍቀድ የለባችሁም። ከዚህም በተጨማሪ ለማጥናት የምትመርጡት ጽሑፍ ቤተሰቡ በዕለታዊ ሕይወቱ የሚጠቀምበት ሊሆን ይገባል። የጥናት ፕሮግራማችሁ አስደሳች እንዲሆን ምን ማድረግ ትችላላችሁ? ውጤታማ የሆኑ የማስተማሪያ ዘዴዎችን ተጠቀሙ፤ እንዲሁም በምታጠኑበት ጊዜ ዘና ያለ ሆኖም አክብሮት የተሞላበት ሁኔታ እንዲኖር አድርጉ።​—ያዕ. 3:18 *

‘ነቅታችሁ ኑሩ’ እንዲሁም “ዝግጁ ሆናችሁ ጠብቁ”

18, 19. አንተም ሆነ ቤተሰብህ የሰው ልጅ የሚመጣበት ጊዜ እንደቀረበ ማወቃችሁ ምን እንድታደርጉ ሊያነሳሳችሁ ይገባል?

18 እየተባባሰ የመጣው የዓለማችን ሁኔታ፣ ከ1914 ጀምሮ የሰይጣን ክፉ ዓለም በመጨረሻዎቹ ቀናት ውስጥ እንዳለ በማያሻማ ሁኔታ ያሳያል። አርማጌዶን የሚመጣበት ጊዜ ሩቅ አይደለም። በቅርቡ የሰው ልጅ ፈሪሃ አምላክ በሌላቸው ሰዎች ላይ የይሖዋን ፍርድ ለማስፈጸም ይመጣል። (መዝ. 37:10፤ ምሳሌ 2:21, 22) ይህን ማወቃችሁ አንተንም ሆነ ቤተሰብህን ለተግባር ሊያነሳሳችሁ አይገባም?

19 ኢየሱስ “ዓይንህ አጥርቶ የሚያይ” እንዲሆን የሰጠውን ምክር ተግባራዊ እያደረግህ ነው? በዓለም ላይ ያሉ ሰዎች ሀብት፣ ዝና ወይም ሥልጣን ለማግኘት ሲሮጡ ይታያል፤ የአንተ ቤተሰብስ መንፈሳዊ ግቦች ላይ ለመድረስ ጥረት እያደረገ ነው? የቤተሰብ አምልኮ ወይም የግል ጥናት የምታደርጉበት ምሽት እንድትመድቡ በተደረገው ዝግጅት እየተጠቀማችሁበት ነው? ይህ ዝግጅት የተደረገበት ዓላማ ግቡን እንዲመታ በማድረግ ረገድ እየተሳካላችሁ ነው? ባለፈው የጥናት ርዕስ ላይ እንደተብራራው ባል፣ ሚስት ወይም ልጅ በመሆናችሁ የተጣለባችሁን ቅዱስ ጽሑፋዊ ኃላፊነት እየተወጣችሁና በዚህም መላው ቤተሰብ ‘ነቅቶ እንዲኖር’ አስተዋጽኦ እያበረከታችሁ ነው? (1 ተሰ. 5:6) እንዲህ የምታደርጉ ከሆነ የሰው ልጅ በሚመጣበት ጊዜ “ዝግጁ ሆናችሁ [መጠበቅ]” ትችላላችሁ።

[የግርጌ ማስታወሻዎች]

^ አን.16 በአማርኛ አይገኝም።

^ አን.17 በቤተሰብ አምልኮ ፕሮግራማችሁ ላይ ምን ማጥናት እንደምትችሉ እንዲሁም ጥናቱ ተግባራዊ ሊሆኑ የሚችሉ ነጥቦችን ያካተተና አስደሳች እንዲሆን ምን ማድረግ እንደምትችሉ ሐሳብ ለማግኘት የጥቅምት 15, 2009 መጠበቂያ ግንብ ከገጽ 29-31 ተመልከቱ።

ምን ትምህርት አግኝተሃል?

• ክርስቲያን ቤተሰቦች ዓይናቸው ምንጊዜም “አጥርቶ የሚያይ” እንዲሆን ማድረጋቸው ‘ዝግጁ ሆነው እንዲጠብቁ’ የሚረዳቸው እንዴት ነው?

• ክርስቲያን ቤተሰቦች መንፈሳዊ ግቦች ማውጣታቸውና ግባቸው ላይ ለመድረስ ጥረት ማድረጋቸው ‘ዝግጁ ሆነው እንዲጠብቁ’ የሚረዳቸው እንዴት ነው?

• ክርስቲያን ቤተሰቦች የቤተሰብ አምልኮ የሚያደርጉበት ቋሚ ምሽት እንዲኖር ማድረጋቸው ‘ዝግጁ ሆነው እንዲጠብቁ’ የሚረዳቸው እንዴት ነው?

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 13 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

‘ዓይናችን አጥርቶ የሚያይ’ መሆኑ በዓለም ላይ የሚታዩትን ትኩረት የሚከፋፍሉ ነገሮች ለማስወገድ ያነሳሳናል