በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

በዚህ ክፉ ዓለም ውስጥ “ጊዜያዊ ነዋሪ” ሆኖ መኖር

በዚህ ክፉ ዓለም ውስጥ “ጊዜያዊ ነዋሪ” ሆኖ መኖር

በዚህ ክፉ ዓለም ውስጥ “ጊዜያዊ ነዋሪ” ሆኖ መኖር

“እነዚህ ሁሉ . . . በምድሩም ላይ እንግዶችና ጊዜያዊ ነዋሪዎች መሆናቸውን በይፋ ተናገሩ።”​—ዕብ. 11:13

1. ኢየሱስ፣ እውነተኛ ተከታዮቹ ከዚህ ዓለም ጋር በተያያዘ ሊኖራቸው የሚገባውን አቋም በተመለከተ ምን ብሏል?

ኢየሱስ ስለ ደቀ መዛሙርቱ ሲናገር “በዓለም ውስጥ ናቸው” ብሏል። ይሁን እንጂ አክሎ “እኔ የዓለም ክፍል እንዳልሆንኩ ሁሉ እነሱም የዓለም ክፍል [አይደሉም]” በማለት ተናግሯል። (ዮሐ. 17:11, 14) ኢየሱስ ይህን ሲል እውነተኛ ተከታዮቹ ሰይጣን አምላኩ ከሆነለት ‘ከዚህ ሥርዓት’ ጋር በተያያዘ ሊኖራቸው የሚገባውን አቋም በግልጽ መናገሩ ነበር። (2 ቆሮ. 4:4) ምንም እንኳ የሚኖሩት በዚህ ክፉ ዓለም ውስጥ ቢሆንም የዚህ ዓለም ክፍል መሆን የለባቸውም። በዚህ ሥርዓት ውስጥ ያሉበት ሁኔታ “መጻተኞችና ጊዜያዊ ነዋሪዎች” ከሆኑ ሰዎች ጋር ይመሳሰላል።​—1 ጴጥ. 2:11

እንደ “ጊዜያዊ ነዋሪ” ሆነው ኖረዋል

2, 3. ሄኖክ፣ ኖኅ እንዲሁም አብርሃምና ሣራ የኖሩት እንደ “እንግዶችና ጊዜያዊ ነዋሪዎች” ነው ሊባል የሚችለው እንዴት ነው?

2 ከጥንት ጀምሮ፣ ታማኝ የይሖዋ አገልጋዮች አምላካዊ ፍርሃት ከሌለው ዓለም የተለዩ በመሆናቸው ይታወቁ ነበር። ከጥፋት ውኃ በፊት የነበሩት ሄኖክና ኖኅ ‘አካሄዳቸውን ከእግዚአብሔር ጋር አድርገዋል።’ (ዘፍ. 5:22-24፤ 6:9) ሁለቱም ቢሆኑ ይሖዋ ክፉ በሆነው የሰይጣን ዓለም ላይ የሚያመጣውን ፍርድ በድፍረት ሰብከዋል። (2 ጴጥሮስ 2:5ን እና ይሁዳ 14, 15ን አንብብ።) አምላካዊ ፍርሃት በሌለው ዓለም ውስጥ አካሄዳቸውን ከአምላክ ጋር በማድረጋቸው ሄኖክ “አምላክን በሚገባ ደስ” እንዳሰኘ ሲነገርለት ኖኅ ደግሞ “ከበደል የራቀ ሰው” እንደነበር ተመሥክሮለታል።​—ዕብ. 11:5፤ ዘፍ. 6:9

3 አብርሃምና ሣራ፣ አምላክ ባቀረበላቸው ግብዣ መሠረት በከለዳውያን ምድር በምትገኘው በዑር የነበራቸውን ምቾት ያለው ኑሮ ትተው በባዕድ አገር የዘላን ዓይነት ሕይወት ለመኖር ፈቃደኞች ሆነዋል። (ዘፍ. 11:27, 28፤ 12:1) ሐዋርያው ጳውሎስ እነሱን በማስመልከት እንዲህ በማለት ጽፏል፦ “አብርሃም በተጠራ ጊዜ ወደፊት ርስት አድርጎ እንዲወስደው ወደተወሰነለት ስፍራ ለመሄድ በመነሳት በእምነት ታዘዘ፤ ወዴት እንደሚሄድ ባያውቅም ይኖርበት የነበረውን ስፍራ ለቆ ወጣ። በባዕድ አገር እንዳለ እንደ መጻተኛ በተስፋይቱ ምድር በእምነት ተቀመጠ፤ ከእሱ ጋር የዚሁ ተስፋ ቃል ወራሾች ከሆኑት ከይስሐቅና ከያዕቆብ ጋርም በድንኳን ኖረ።” (ዕብ. 11:8, 9) ጳውሎስ እነዚህን ስለመሳሰሉ ታማኝ የይሖዋ አገልጋዮች አስመልክቶ እንዲህ ብሏል፦ “እነዚህ ሁሉ የተስፋውን ቃል ፍጻሜ ባያገኙም እምነታቸውን እንደጠበቁ ሞቱ፤ ሆኖም ከሩቅ አይተው በደስታ ተቀበሉት፤ በምድሩም ላይ እንግዶችና ጊዜያዊ ነዋሪዎች መሆናቸውን በይፋ ተናገሩ።”​—ዕብ. 11:13

ለእስራኤላውያን የተሰጠ ማስጠንቀቂያ

4. እስራኤላውያን ወደ አገራቸው ከመግባታቸው በፊት ምን ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸው ነበር?

4 የአብርሃም ዝርያ የሆኑት እስራኤላውያን ቁጥራቸው እየበዛ ሄዶ የራሳቸው የሆነ አገርና መተዳደሪያ ሕግ ያላቸው ብሔር ሆኑ። (ዘፍ. 48:4፤ ዘዳ. 6:1) ያም ሆኖ እስራኤላውያን፣ የሚኖሩባት ምድር ንብረትነቷ የይሖዋ መሆኑን ፈጽሞ መዘንጋት አልነበረባቸውም። (ዘሌ. 25:23) ምክንያቱም እስራኤላውያን የባለንብረቱን ፍላጎት የማክበር ግዴታ እንዳለበት ተከራይ ነበሩ። ከዚህም በላይ ሰው “በእንጀራ ብቻ እንደማይኖር” ማስታወስ ይኖርባቸው ነበር፤ እንዲሁም ቁሳዊ ብልጽግና ይሖዋን እንዲረሱ ሊያደርጋቸው አይገባም ነበር። (ዘዳ. 8:1-3) እስራኤላውያን ወደ አገራቸው ከመግባታቸው በፊት እንዲህ የሚል ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸው ነበር፦ “አምላክህ እግዚአብሔር ለአንተ ለመስጠት ለአባቶችህ ለአብርሃም፣ ለይስሐቅና ለያዕቆብ ወደ ማለላቸው ምድር ሲያስገባህ፣ በዚያም ያልሠራሃቸውን ታላላቅና ያማሩ ከተሞችን፣ የራስህ ባልነበሩ መልካም ነገሮች ሁሉ የተሞሉ ቤቶችን ያልቈፈርሃቸውን የውሃ ጕድጓዶች፣ ያልተከልሃቸውን የወይን ተክሎችና የወይራ ዛፎች ሲሰጥህና በልተህም ስትጠግብ፣ ከባርነት ምድር ከግብፅ ያወጣህን እግዚአብሔርን እንዳትረሳ ተጠንቀቅ!”​—ዘዳ. 6:10-12

5. ይሖዋ እስራኤላውያንን የተዋቸው ለምንድን ነው? በእነሱ ፋንታ ተቀባይነት ያገኘው አዲሱ ብሔር የትኛው ነው?

5 ይህ ማስጠንቀቂያ መሰጠቱ ተገቢ ነበር። እስራኤላውያን ወደ ተስፋይቱ ምድር ከገቡ በኋላ የፈጸሙት ነገር ምን ያህል አሳፋሪ እንደነበር በነህምያ ዘመን የነበሩ አንዳንድ ሌዋውያን ተናግረዋል። እስራኤላውያን በተመቻቹ ቤቶች ውስጥ መኖር ሲጀምሩ እንዲሁም የተትረፈረፈ ምግብና ወይን ሲያገኙ “እስኪጠግቡ በሉ፤ ወፈሩም።” በኋላም በይሖዋ ላይ ያመፁ ሲሆን ይባስ ብሎም አምላክ እነሱን ለማስጠንቀቅ የላካቸውን ነቢያት ገደሉ። (ነህምያ 9:25-27ን አንብብ፤ ሆሴዕ 13:6-9) እምነት የለሾቹ አይሁዳውያን በሮም አገዛዝ ሥር በነበሩበት ወቅትም ተስፋ የተደረገበትን መሲሕ እስከ መግደል ደርሰዋል! በመሆኑም ይሖዋ እነሱን በመተው አዲሱን ብሔር ማለትም መንፈሳዊ እስራኤላውያንን እንደ ሕዝቡ አድርጎ ተቀበለ።​—ማቴ. 21:43፤ ሥራ 7:51, 52፤ ገላ. 6:16

‘የዓለም ክፍል አይደሉም’

6, 7. (ሀ) ኢየሱስ፣ ተከታዮቹ ከዚህ ዓለም ጋር በተያያዘ ሊኖራቸው የሚገባውን አቋም አስመልክቶ የተናገረውን ሐሳብ የምትረዳው እንዴት ነው? (ለ) እውነተኛ ክርስቲያኖች የሰይጣን ሥርዓት ክፍል መሆን የሌለባቸው ለምንድን ነው?

6 በዚህ ርዕስ መግቢያ ላይ እንደተመለከትነው የክርስቲያን ጉባኤ ራስ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ፣ ተከታዮቹ የሰይጣን ክፉ ሥርዓት ከሆነው ከዚህ ዓለም መለየት እንዳለባቸው በግልጽ ተናግሯል። ኢየሱስ ከመሞቱ ጥቂት ቀደም ብሎም ለደቀ መዛሙርቱ እንዲህ ብሏቸው ነበር፦ “የዓለም ክፍል ብትሆኑ ኖሮ ዓለም የራሱ የሆነውን በወደደ ነበር። አሁን ግን እኔ ከዓለም መረጥኳችሁ እንጂ የዓለም ክፍል ስላልሆናችሁ ከዚህ የተነሳ ዓለም ይጠላችኋል።”​—ዮሐ. 15:19

7 ክርስትና እየተስፋፋ ሲመጣ ክርስቲያኖች የዓለምን ልማዶች በመከተልና የእሱ ክፍል በመሆን ከዓለም ጋር ተስማምተው መኖር ይጀምሩ ይሆን? በፍጹም። የሚኖሩት የትም ይሁን የት ራሳቸውን ከሰይጣን ሥርዓት መለየት ነበረባቸው። ሐዋርያው ጴጥሮስ፣ ክርስቶስ ከሞተ ከ30 ዓመታት ገደማ በኋላ በተለያዩ የሮም ግዛቶች ውስጥ ለሚኖሩ ክርስቲያኖች በጻፈው ደብዳቤ ላይ እንዲህ ብሎ ነበር፦ “የተወደዳችሁ ወንድሞች፣ መጻተኞችና ጊዜያዊ ነዋሪዎች እንደመሆናችሁ መጠን ከነፍስ ጋር ከሚዋጉት ሥጋዊ ምኞቶች ምንጊዜም እንድትርቁ አሳስባችኋለሁ። . . . በአሕዛብ መካከል መልካም ምግባር ይዛችሁ ኑሩ።”​—1 ጴጥ. 1:1፤ 2:11, 12

8. አንድ የታሪክ ምሑር የጥንቶቹ ክርስቲያኖች ከዓለም ጋር ስለነበራቸው ግንኙነት ምን ብለዋል?

8 ኬኔት ስኮት ላቱሬቴ የተባሉ አንድ የታሪክ ምሑር በሮም ግዛቶች የነበሩ የጥንቶቹ ክርስቲያኖች፣ አኗኗራቸው እንደ “መጻተኞችና ጊዜያዊ ነዋሪዎች” እንደነበር ሲያረጋግጡ እንዲህ ብለዋል፦ “በመጀመሪያዎቹ ሦስት መቶ ዘመናት ክርስቲያኖች ብዙውን ጊዜ ያለማቋረጥ ከባድ ስደት ይደርስባቸው እንደነበር ከማንም የተሰወረ አይደለም። . . . የተለያየ የሐሰት ክስ ይሰነዘርባቸው ነበር። ክርስቲያኖች በአረማዊ በዓላት ላይ ባለመካፈላቸው ምክንያት አምላክ የለሾች ተብለዋል። በአብዛኞቹ ማኅበራዊ ጉዳዮች ማለትም በአረማዊ ክብረ በዓላት ላይ እንዲሁም አረማዊ እምነቶች፣ ልማዶችና ሥነ ምግባር የጎደላቸው ድርጊቶች የሞሉበት እንደሆነ አድርገው በሚያስቧቸው ሕዝባዊ የመዝናኛ ዝግጅቶች ላይ ባለመሳተፋቸው የሰውን ዘር እንደሚጠሉ ተደርገው ይቆጠሩ ነበር።”

በዓለም ሙሉ በሙሉ አለመጠቀም

9. እውነተኛ ክርስቲያኖች እንደመሆናችን መጠን ‘የሰውን ዘር እንደማንጠላ’ የምናሳየው እንዴት ነው?

9 በዛሬ ጊዜ ያለው ሁኔታስ ምን ይመስላል? ‘አሁን ያለውን ክፉ ሥርዓት’ በተመለከተ ያለን አቋም ከጥንቶቹ ክርስቲያኖች የተለየ አይደለም። (ገላ. 1:4) በዚህ የተነሳ ብዙዎች በተሳሳተ መንገድ ይረዱናል እንዲያውም አንዳንዶች ይጠሉናል። ይሁንና እነሱ እንደሚያስቡት እኛ ‘የሰውን ዘር እንደማንጠላ’ የታወቀ ነው። ለሰዎች ካለን ፍቅር የተነሳ ከቤት ወደ ቤት በመሄድ ‘የአምላክን መንግሥት ምሥራች’ በቤት ውስጥ ላለ ለእያንዳንዱ ሰው ለማዳረስ ጥረት እናደርጋለን። (ማቴ. 22:39፤ 24:14) ይህን የምናደርገው በክርስቶስ የሚመራው የይሖዋ መንግሥት በቅርቡ ፍጹም ያልሆነውን ሰብዓዊ አገዛዝ አስወግዶ በምትኩ ጽድቅ የሰፈነበት አዲስ ሥርዓት እንደሚያመጣ ጠንካራ እምነት ስላለን ነው።​—ዳን. 2:44፤ 2 ጴጥ. 3:13

10, 11. (ሀ) በተወሰነ መጠን በዓለም መጠቀም የምንችለው እንዴት ነው? (ለ) ንቁ የሆኑ ክርስቲያኖች በዓለም ሙሉ በሙሉ ከመጠቀም የሚርቁባቸው አንዳንድ መንገዶች የትኞቹ ናቸው?

10 ይህ ሥርዓት በቅርቡ ከሕልውና ውጪ መሆኑ አይቀሬ ነው፤ በመሆኑም እኛ የይሖዋ አገልጋዮች ሊጠፋ በተቃረበው በዚህ ዓለም ውስጥ የተደላደለ ኑሮ በመምራት ጊዜያችንን ማባከን እንደሌለብን እንረዳለን። ሐዋርያው ጳውሎስ እንዲህ በማለት የሰጠውን ማሳሰቢያ በሥራ ላይ እናውላለን፦ “ወንድሞች፣ የቀረው ጊዜ አጭር መሆኑን ልነግራችሁ እወዳለሁ። ስለዚህ . . . የሚገዙም ምንም እንደሌላቸው እንዲሁም በዓለም የሚጠቀሙ ሙሉ በሙሉ እንደማይጠቀሙበት ይሁኑ፤ ምክንያቱም የዚህ ዓለም ትእይንት እየተለዋወጠ ነው።” (1 ቆሮ. 7:29-31) በአሁኑ ጊዜ ያሉ ክርስቲያኖች በዓለም እየተጠቀሙ ያሉት እንዴት ነው? ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችንና የመገናኛ አውታሮችን በመጠቀም የመጽሐፍ ቅዱስን መልእክት በመቶዎች በሚቆጠሩ ቋንቋዎች በዓለም ዙሪያ እንዲሰራጭ በማድረግ ነው። ለመኖር የሚያስፈልጓቸውን ነገሮች ለማግኘት በተወሰነ መጠን በዓለም ይጠቀማሉ። ዓለም የሚያቀርባቸውን አንዳንድ አስፈላጊ የሆኑ ቁሳቁሶች ይገዛሉ፤ በሚሰጣቸው አገልግሎቶችም ይጠቀማሉ። ያም ሆኖ ለቁሳዊ ነገሮችና ለሥራ ተገቢውን ቦታ በመስጠት በዓለም ሙሉ በሙሉ ከመጠቀም እንደሚርቁ ያሳያሉ።​—1 ጢሞቴዎስ 6:9, 10ን አንብብ።

11 ንቁ የሆኑ ክርስቲያኖች ከከፍተኛ ትምህርት ጋር በተያያዘም በዓለም ሙሉ በሙሉ ከመጠቀም ይርቃሉ። በዚህ ዓለም ውስጥ ያሉ ብዙ ሰዎች ትልቅ ቦታ ላይ ለመድረስና የተደላደለ ሕይወት ለመምራት ከፍተኛ ትምህርት የግድ አስፈላጊ እንደሆነ ይሰማቸዋል። እኛ ክርስቲያኖች ግን ጊዜያዊ ነዋሪዎች እንደመሆናችን መጠን ግባችን ከዚህ የተለየ ነው። ‘ለራሳችን ታላቅ ነገር ከመሻት’ እንርቃለን። (ኤር. 45:5፤ ሮም 12:16) የኢየሱስ ተከታዮች በመሆናችን እንደሚከተለው በማለት የሰጠንን ማስጠንቀቂያ ተግባራዊ ለማድረግ እንጥራለን፦ “አንድ ሰው ሀብታም ቢሆንም እንኳ ሕይወቱ በንብረቱ ላይ የተመካ ስላልሆነ ተጠንቀቁ፤ ከመጎምጀትም ሁሉ ተጠበቁ።” (ሉቃስ 12:15) በዚህም የተነሳ ወጣት ክርስቲያኖች መንፈሳዊ ግቦችን እንዲያወጡ በሌላ አባባል በአንድ በኩል ይሖዋን ‘በሙሉ ልብ፣ በሙሉ ነፍስ፣ በሙሉ ኃይልና በሙሉ አእምሮ’ እያገለገሉ በሌላ በኩል ደግሞ መሠረታዊ ፍላጎታቸውን ለማሟላት የሚያስችላቸውን ያህል ብቻ ሰብዓዊ ትምህርት እንዲከታተሉ ይበረታታሉ። (ሉቃስ 10:27) እንዲህ የሚያደርጉ ከሆነ ‘በአምላክ ዘንድ ሀብታም’ መሆን ይችላሉ።​—ሉቃስ 12:21፤ ማቴዎስ 6:19-21ን አንብብ።

ስለ ኑሮ በመጨነቅ ሸክም እንዳይበዛባችሁ ተጠንቀቁ

12, 13. ኢየሱስ በ⁠ማቴዎስ 6:31-33 ላይ የሰጠውን ማሳሰቢያ መከተላችን ከዓለም የሚለየን እንዴት ነው?

12 የይሖዋ አገልጋዮች ለቁሳዊ ነገር ያላቸው አመለካከት በዓለም ላይ ከሚገኙ ሰዎች የተለየ ነው። በዚህ ረገድ ኢየሱስ ለተከታዮቹ እንዲህ ብሏቸው ነበር፦ “‘ምን እንበላለን?’ ወይም ‘ምን እንጠጣለን?’ ወይም ደግሞ ‘ምን እንለብሳለን?’ ብላችሁ ፈጽሞ አትጨነቁ። እነዚህ ነገሮች ሁሉ አሕዛብ አጥብቀው የሚፈልጓቸው ናቸው። በሰማይ የሚኖረው አባታችሁ እነዚህ ሁሉ እንደሚያስፈልጓችሁ ያውቃል። እንግዲያው ከሁሉ አስቀድማችሁ የአምላክን መንግሥትና ጽድቅ መፈለጋችሁን ቀጥሉ፤ እነዚህም ነገሮች ሁሉ ይሰጧችኋል።” (ማቴ. 6:31-33) በርካታ የእምነት ባልንጀሮቻችን በሰማይ የሚገኘው አባታችን የሚያስፈልጓቸውን ነገሮች እንደሚያሟላላቸው በራሳቸው ሕይወት አይተዋል።

13 “ባለው ነገር ለሚረካ ሰው ለአምላክ ማደር ትልቅ ትርፍ ያስገኛል።” (1 ጢሞ. 6:6) ዛሬ በዓለም ላይ ያሉ ሰዎች ያላቸው አመለካከት ከዚህ ፍጹም የተለየ ነው። ለምሳሌ ያህል፣ ወጣቶች ትዳር ሲመሠርቱ አብዛኞቹ በአንድ ጊዜ ‘ሁሉም ነገር’ ማለትም የተሟላ ቤት ወይም አፓርታማ፣ ጥሩ መኪና እንዲሁም አዲስ የመጡ የኤሌክትሮኒክ ዕቃዎች እንዲኖሯቸው ይፈልጋሉ። ይሁንና በዚህ ዓለም ላይ እንደ ጊዜያዊ ነዋሪዎች የሆኑት ክርስቲያኖች ምክንያታዊ ያልሆነ ነገር አይመኙም፤ እንዲሁም ከአቅማቸው በላይ የሆነ ነገር ለመግዛት አይሞክሩም። ብዙዎች፣ ቀናተኛ የመንግሥቱ አስፋፊዎች ለመሆን የሚያስፈልጋቸውን ተጨማሪ ጊዜና ጉልበት ለማግኘት ሲሉ በቁሳዊ ነገሮች ረገድ በምቾት ለመኖር የሚያስችሏቸውን አንዳንድ አጋጣሚዎች መተዋቸው በእርግጥም የሚያስመሰግናቸው ነው። ሌሎች ደግሞ አቅኚ፣ ቤቴላዊ፣ ተጓዥ የበላይ ተመልካች ወይም ሚስዮናዊ ሆነው ያገለግላሉ። የእምነት ባልንጀሮቻችን በሙሉ ልባቸው ለይሖዋ የሚያቀርቡትን አገልግሎት ሁላችንም እጅግ እናደንቃለን!

14. ኢየሱስ ስለ ዘሪው ከተናገረው ምሳሌ ምን ትምህርት ማግኘት እንችላለን?

14 ኢየሱስ ስለ ዘሪው በተናገረው ምሳሌ ላይ “የዚህ ሥርዓት ጭንቀት እንዲሁም ሀብት ያለው የማታለል ኃይል” በልባችን ውስጥ ያለውን የአምላክ ቃል ሊያንቀውና ፍሬ እንዳናፈራ ሊያደርገን እንደሚችል ገልጿል። (ማቴ. 13:22) በዚህ ሥርዓት ውስጥ እንደ ጊዜያዊ ነዋሪ በመሆን ባለን ረክተን መኖራችን በዚህ ወጥመድ እንዳንወድቅ ይጠብቀናል። እንዲሁም፣ ዓይናችን “አጥርቶ የሚያይ” ወይም “በአንድ ነገር ላይ ያተኮረ” እንዲሆን ይኸውም በሕይወታችን ውስጥ ለአምላክ መንግሥትና ከመንግሥቱ ጋር ለተያያዙ ጉዳዮች ቅድሚያ እንድንሰጥ ያስችለናል።​—ማቴ. 6:22 የግርጌ ማስታወሻ

‘ዓለም በማለፍ ላይ ነው’

15. እውነተኛ ክርስቲያኖች ለዚህ ዓለም በሚኖራቸው አመለካከት ላይ በጎ ተጽዕኖ የሚያሳድረው የትኛው የሐዋርያው ዮሐንስ አነጋገር ነው?

15 እኛ እውነተኛ ክርስቲያኖች ራሳችንን እንደ “መጻተኞችና ጊዜያዊ ነዋሪዎች” አድርገን የምንቆጥርበት ዋነኛው ምክንያት ይህ ዓለም ሊጠፋ የቀረው ጊዜ አጭር እንደሆነ እርግጠኞች መሆናችን ነው። (1 ጴጥ. 2:11፤ 2 ጴጥ. 3:7) እንዲህ ዓይነት አመለካከት ያለን መሆኑ በሕይወታችን ውስጥ በምናደርገው ምርጫ እንዲሁም በምኞታችንና በፍላጎታችን ላይ በጎ ተጽዕኖ ያሳድራል። ሐዋርያው ዮሐንስ የእምነት ባልንጀሮቹ ዓለምንም ሆነ በዓለም ውስጥ ያሉትን ነገሮች እንዳይወዱ ምክር ሰጥቷቸዋል፤ ምክንያቱም “ዓለምም ሆነ ምኞቱ በማለፍ ላይ ናቸው፤ የአምላክን ፈቃድ የሚያደርግ ግን ለዘላለም ይኖራል።”​—1 ዮሐ. 2:15-17

16. የተለየን ሕዝብ እንድንሆን የተመረጥን መሆናችንን ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው?

16 እስራኤላውያን፣ ይሖዋን ቢታዘዙ ኖሮ ‘ከአሕዛብ ሁሉ የተወደደ የአምላክ ርስት እንደሚሆኑ’ ቃል ተገብቶላቸው ነበር። (ዘፀ. 19:5) ታማኝ በነበሩበት ወቅት በአምልኳቸውም ሆነ በአኗኗራቸው ከሌሎች ብሔራት ይለዩ ነበር። በተመሳሳይም በዛሬው ጊዜ ይሖዋ ከሰይጣን ዓለም ፍጹም የተለየ ሕዝብ ለራሱ መርጧል። ይህን ሕዝብ አስመልክቶ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ “አምላካዊ ያልሆነ ምግባርንና ዓለማዊ ምኞቶችን ክደን አሁን ባለው በዚህ ሥርዓት ውስጥ ጤናማ አስተሳሰብ በመያዝ፣ በጽድቅና ለአምላክ በማደር [እንኑር]፤ . . . በዚህ ሁኔታ አስደሳች የሆነውን ተስፋና የታላቁን አምላክ እንዲሁም የአዳኛችንን የክርስቶስ ኢየሱስን ክብራማ መገለጥ እንጠባበቃለን፤ ክርስቶስ እኛን ከማንኛውም ዓይነት ዓመፅ ለማዳንና ለመልካም ሥራ የሚቀና የእሱ ብቻ የሆነ ሕዝብ ለራሱ ለማንጻት ራሱን ለእኛ ሰጥቷል።” (ቲቶ 2:11-14) ይህ “ሕዝብ” ቅቡዓን ክርስቲያኖችንና እነሱን የሚደግፉ የኢየሱስ ንብረት የሆኑትን በሚሊዮን የሚቆጠሩ “ሌሎች በጎች” ያቀፈ ነው።​—ዮሐ. 10:16

17. ቅቡዓን ክርስቲያኖችም ሆኑ ሌሎች በጎች በዚህ ክፉ ዓለም ውስጥ እንደ ጊዜያዊ ነዋሪዎች ሆነው በመኖራቸው ፈጽሞ የማይቆጩት ለምንድን ነው?

17 ቅቡዓን ክርስቲያኖች፣ ከክርስቶስ ጋር በሰማይ የመግዛት ‘አስደሳች ተስፋ’ አላቸው። (ራእይ 5:10) በሌላ በኩል ደግሞ ሌሎች በጎች በምድር ላይ ለዘላለም የመኖር ተስፋቸው ፍጻሜ ሲያገኝ በዚህ ክፉ ዓለም ውስጥ ጊዜያዊ ነዋሪዎች ሆነው መኖራቸው ያከትማል። የሚያማምሩ ቤቶች እንዲሁም የተትረፈረፈ ምግብና መጠጥ ይኖራቸዋል። (መዝ. 37:10, 11፤ ኢሳ. 25:6፤ 65:21, 22) ከእስራኤላውያን በተለየ እነዚህ ሕዝቦች ይህን ሁሉ ያገኙት “የምድር ሁሉ አምላክ” ከሆነው ከይሖዋ እንደሆነ ፈጽሞ አይረሱም። (ኢሳ. 54:5) ቅቡዓን ክርስቲያኖችም ሆኑ ሌሎች በጎች በዚህ ክፉ ዓለም ውስጥ እንደ ጊዜያዊ ነዋሪዎች ሆነው በመኖራቸው ፈጽሞ አይቆጩም።

ምን ብለህ ትመልሳለህ?

• የጥንቶቹ ታማኝ የአምላክ አገልጋዮች እንደ ጊዜያዊ ነዋሪዎች ሆነው የኖሩት በምን መንገድ ነው?

• የጥንቶቹ ክርስቲያኖች በዓለም ውስጥ ሲመላለሱ ምን ዓይነት ምግባር ያንጸባርቁ ነበር?

• እውነተኛ ክርስቲያኖች በተወሰነ መጠን በዓለም የሚጠቀሙት እንዴት ነው?

• በዚህ ክፉ ዓለም ውስጥ እንደ ጊዜያዊ ነዋሪዎች ሆነን በመኖራችን ፈጽሞ የማንቆጨው ለምንድን ነው?

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 18 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

የጥንቶቹ ክርስቲያኖች ዓመፅና የሥነ ምግባር ብልግና ከሚንጸባረቅባቸው መዝናኛዎች ርቀዋል