በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ታስታውሳለህ?

ታስታውሳለህ?

ታስታውሳለህ?

በቅርቡ የወጡትን የመጠበቂያ ግንብ እትሞች በደንብ አንብበሃቸዋል? እስቲ የሚከተሉትን ጥያቄዎች ለመመለስ ሞክር፦

• ኦሊቬታ ማን ነው? የእሱ ሥራ ትኩረታችንን የሚስበውስ ለምንድን ነው?

ፈረንሳዊው ፒየር ሮቤር የሚታወቀው በዚህ ስም ነበር። በ16ኛው መቶ ዘመን በተካሄደው የተሃድሶ እንቅስቃሴ ወቅት መጽሐፍ ቅዱስን ወደ ፈረንሳይኛ ቋንቋ ተርጉሟል። በትርጉም ሥራው ላይ “ቄስ” በሚለው ፋንታ “የበላይ ተመልካች” እንዲሁም “ቤተ ክርስቲያን” በሚለው ፋንታ “ጉባኤ” የሚለውን ስያሜ መጠቀም መርጧል። በአንዳንድ ቦታዎችም “ይሖዋ” የተባለውን የአምላክ ስም ተጠቅሟል።​—9/1 ገጽ 18-20

• አምላክ ለሌዋውያን ‘ድርሻችሁ እኔ ነኝ’ ሲል ምን ማለቱ ነበር?

ሌሎቹ የእስራኤል ነገዶች በሙሉ በዕጣ ከተከፋፈለው መሬት ድርሻቸውን ሲቀበሉ የሌዋውያኑ “ድርሻ” ግን ይሖዋ ነበር። (ዘኍ. 18:20) ሌዋውያኑ ልዩ የአገልግሎት መብት እንጂ ርስት አልተሰጣቸውም። ሆኖም የሚያስፈልጓቸውን ቁሳዊ ነገሮች ይሖዋ ያሟላላቸው ነበር። በዛሬው ጊዜም ከመንግሥቱ ጉዳዮች ጋር የተያያዙ ሥራዎችን የማከናወን መብት ያገኙ ክርስቲያኖች ይሖዋ የሚያስፈልጋቸውን ነገር እንደሚያሟላላቸው እርግጠኞች መሆን ይችላሉ።​—9/15 ገጽ 7-8, 13

• የጥንቷ ኢየሩሳሌም በባቢሎናውያን የጠፋችው መቼ እንደሆነ ማወቅ የምንችለው እንዴት ነው?

የጥንት ታሪክ ጸሐፊዎች የባቢሎን ነገሥታትንና የንግሥና ዘመናቸውን አስመልክቶ የሚሰጡት መረጃ የተምታታና እርስ በርሱ የሚጋጭ ነው። ያም ቢሆን ምሑራን ዳግማዊ ቂሮስ ባቢሎንን ድል ያደረገው በ539 ዓ.ዓ. እንደሆነ ይስማማሉ፤ ይህ ጊዜ ደግሞ በታሪክ ውስጥ ትልቅ ቦታ ያለው ዓመት ነው። አይሁዳውያን ነፃ ወጥተው ወደ ትውልድ አገራቸው የተመለሱት በ537 ዓ.ዓ. ነበር። መጽሐፍ ቅዱስ አይሁዳውያን በግዞት የቆዩት ለ70 ዓመታት እንደሆነ ይናገራል። በመሆኑም ኢየሩሳሌም የወደቀችው በ607 ዓ.ዓ. መሆን ይኖርበታል። (2 ዜና 36:21, 22፤ ኤር. 29:10፤ ዳን. 9:1, 2)​—10/1 ገጽ 26-31

• አንድ ክርስቲያን የሚመርጠው መዝናኛ ጠቃሚ መሆን አለመሆኑን ለመለየት ምን ሊረዳው ይችላል?

አንድ መዝናኛ ጠቃሚና በአምላክ ፊት ተቀባይነት ያለው መሆን አለመሆኑን ለመወሰን ራሳችንን እንዲህ ብለን መጠየቃችን ተገቢ ነው፦ መዝናኛው ምን ነገሮችን ያካትታል? የምዝናናው መቼ ነው? የምዝናናው ከእነማን ጋር ነው?​—10/15 ገጽ 9-12

• ፅንስ ማስወረድ ስህተት የሆነው ለምንድን ነው?

ሕይወት በአምላክ ፊት ቅዱስ ነው፤ አምላክ በማህፀን ውስጥ ያለን ፅንስ እንደ አንድ ሕያው አካል አድርጎ ይመለከተዋል። (መዝ. 139:16) ባልተወለደ ሕፃን ላይ ጉዳት የሚያደርስ ሰው ተጠያቂ እንደሚሆን በሕጉ ውስጥ መጠቀሱ ፅንስ ማስወረድ ሕይወት ከማጥፋት ተለይቶ እንደማይታይ ይጠቁማል። (ዘፀ. 21:22, 23)​—11/1 ገጽ 6

• በ⁠ምሳሌ 7:6-23 ላይ የሚገኘው ዘገባ የብልግና ምስሎችን ከማየት እንድንርቅ የሚረዳን እንዴት ነው?

ይህ ዘገባ የሥነ ምግባር ብልግና የምትፈጽም ሴት እንደምትኖርበት ወደሚታወቅ አካባቢ ስለሄደ አንድ ወጣት ይናገራል። እንዲሁም ከእሷ ጋር በተገናኘ ጊዜ በለሰለሰ አንደበቷ እንደተታለለ ዘገባው ይገልጻል። በዛሬው ጊዜም፣ የፆታ ስሜትን የሚቀሰቅሱ ፎቶዎችና ፊልሞች ከሚገኙባቸው የኢንተርኔት ድረ ገጾች መራቅ ይኖርብናል፤ በተጨማሪም እንዲህ ያሉ ምስሎች የሚታዩባቸውን ድረ ገጾች የመቃኘት ሐሳብ ገና ወደ አእምሯችን ሲመጣ በጸሎት የይሖዋን እርዳታ መጠየቃችን አስፈላጊ ነው።​—11/15 ገጽ 9-10

• ምድር በ2012 እንደማትጠፋ እንዴት ማወቅ እንችላለን?

የጥንቶቹ ማያዎች የቀን መቁጠሪያ የሚያበቃው በ2012 ስለሆነ አንዳንዶች በዚህ ዓመት የዓለም መጨረሻ ይሆናል ብለው ያስባሉ። ይሁንና ይሖዋ ምድርን የፈጠራት የሰው መኖሪያ እንድትሆን ስለሆነ ይህ ፈጽሞ ሊሆን የማይችል ነገር ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ምድር ለዘላለም ጸንታ እንደምትኖር ይናገራል። (መክ. 1:4፤ ኢሳ. 45:18)​—12/1 ገጽ 10

• ቅዱሳን መጻሕፍትን ከጻፉት መካከል በ33 ዓ.ም. በዋለው የጴንጤቆስጤ ዕለት የነበሩት የትኞቹ ናቸው?

ስድስቱ የክርስቲያን ግሪክኛ ቅዱሳን መጻሕፍት ጸሐፊዎች በቦታው ተገኝተው የነበረ ይመስላል። ሦስት ሐዋርያት ማለትም ማቴዎስ፣ ዮሐንስ እና ጴጥሮስ በቦታው ነበሩ። ሁለቱ የኢየሱስ ወንድሞችም ይኸውም ያዕቆብና ይሁዳ እዚያው ነበሩ። በተጨማሪም ወጣቱ ማርቆስ በዚያ ወቅት በቦታው ሳይኖር አልቀረም።​—12/1 ገጽ 22