በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

በጉባኤያችሁ ውስጥ ጥሩ መንፈስ እንዲሰፍን አድርጉ

በጉባኤያችሁ ውስጥ ጥሩ መንፈስ እንዲሰፍን አድርጉ

በጉባኤያችሁ ውስጥ ጥሩ መንፈስ እንዲሰፍን አድርጉ

“የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ ከምታሳዩት መንፈስ ጋር ይሁን።”​—ፊልጵ. 4:23

በጉባኤ ውስጥ ጤናማ መንፈስ እንዲኖር ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው?

ከወንድሞቻችን ጋር አብረን በምንሆንበት ጊዜ

በአገልግሎት ቀናተኛ በመሆን

ከባድ ኃጢአቶችን ለሽማግሌዎች በመናገር

1. የፊልጵስዩስና የትያጥሮን ጉባኤዎች የተመሰገኑት ለምንድን ነው?

በመጀመሪያው መቶ ዘመን በፊልጵስዩስ ይኖሩ የነበሩ ክርስቲያኖች በቁሳዊ ረገድ ድሆች ነበሩ። ያም ሆኖ በልግስናቸውና ለእምነት ባልንጀሮቻቸው ባላቸው ጥልቅ ፍቅር ይታወቁ ነበር። (ፊልጵ. 1:3-5, 9፤ 4:15, 16) በመሆኑም ሐዋርያው ጳውሎስ በመንፈስ መሪነት የጻፈላቸውን ደብዳቤ ሲደመድም “የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ ከምታሳዩት መንፈስ ጋር ይሁን” ብሏቸዋል። (ፊልጵ. 4:23) በትያጥሮን ጉባኤ የሚገኙ ክርስቲያኖችም ተመሳሳይ መንፈስ በማሳየታቸው ክብር የተጎናጸፈው ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲህ ብሏቸዋል፦ “ሥራህን፣ ፍቅርህን፣ እምነትህን፣ አገልግሎትህንና ጽናትህን አውቃለሁ፤ ደግሞም ከቀድሞው ሥራህ ይልቅ የአሁኑ እንደሚበልጥ አውቃለሁ።”​—ራእይ 2:19

2. ጉባኤያችን ከሚያንጸባርቀው መንፈስ ጋር በተያያዘ ምን ድርሻ ይኖረናል?

2 በዛሬው ጊዜ ያሉ ሁሉም የይሖዋ ምሥክሮች ጉባኤዎችም የራሳቸው የሆነ የሚያንጸባርቁት መንፈስ ወይም ተለይተው የሚታወቁበት ነገር አላቸው። አንዳንድ ጉባኤዎች ይበልጥ የሚታወቁት በሚያሳዩት ፍቅርና የወዳጅነት መንፈስ ነው። ሌሎች ደግሞ የስብከቱን ሥራ በቅንዓት በመደገፍና ለሙሉ ጊዜ አገልግሎት ከፍተኛ ቦታ በመስጠት ተለይተው ይታወቃሉ። እኛም በግለሰብ ደረጃ ጥሩ መንፈስ ካለን ለጉባኤው አንድነት አስተዋጽኦ እናደርጋለን፤ ከዚህም በላይ የጉባኤው መንፈሳዊነት ይጠናከራል። (1 ቆሮ. 1:10) በተቃራኒው ደግሞ መጥፎ መንፈስ የምናንጸባርቅ ከሆነ የጉባኤው አባላት በመንፈሳዊ ድብታ እንዲይዛቸው ወይም ለብ ያሉ እንዲሆኑ ተጽዕኖ ልናደርግ እንችላለን፤ ይባስ ብሎም በጉባኤ ውስጥ የሚፈጸሙ ኃጢአቶችን በቸልታ የማለፍ ዝንባሌ እንዲስፋፋ እናደርግ ይሆናል። (1 ቆሮ. 5:1፤ ራእይ 3:15, 16) ታዲያ የጉባኤያችሁ መንፈስ ምን ይመስላል? በጉባኤያችሁ ውስጥ ጥሩ መንፈስ እንዲሰፍን በግለሰብ ደረጃ አስተዋጽኦ ማበርከት የምትችሉትስ እንዴት ነው?

ጥሩ መንፈስ እንዲሰፍን ማድረግ

3, 4. ይሖዋን “በታላቅ ጉባኤ መካከል” ማወደስ የምንችለው እንዴት ነው?

3 መዝሙራዊው “በታላቅ ጉባኤ መካከል አመሰግንሃለሁ፤ ብዙ ሕዝብ በተሰበሰበበትም አወድስሃለሁ” በማለት ለአምላክ ዘምሯል። (መዝ. 35:18) መዝሙራዊው ከሌሎች የአምላክ አገልጋዮች ጋር በሚሆንበት ጊዜ ይሖዋን ያወድስ ነበር። እኛም የመጠበቂያ ግንብ ጥናትን ጨምሮ በየሳምንቱ በምናደርጋቸው ስብሰባዎች ላይ ሐሳብ በመስጠት እምነታችንን እና ቅንዓታችንን ማሳየት እንችላለን። በመሆኑም ሁላችንም ራሳችንን እንዲህ ብለን መጠየቃችን አስፈላጊ ነው፦ ‘በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ ተሳትፎ የማድረግ መብቴን ሙሉ በሙሉ እየተጠቀምኩበት ነው? ለጉባኤ ስብሰባዎች በደንብ እዘጋጃለሁ? እንዲሁም የምሰጣቸው ሐሳቦች በደንብ የታሰበባቸው ናቸው? የቤተሰብ ራስ እንደመሆኔ መጠን ልጆቼ በጉባኤ ላይ ሐሳብ መስጠት እንዲችሉ አስቀድሜ አዘጋጃቸዋለሁ? በራሳቸው አባባል እንዲመልሱስ አሠለጥናቸዋለሁ?’

4 መዝሙራዊው ዳዊት ጽኑ ልብ መያዝን ለይሖዋ ከምናቀርበው ዝማሬ ጋር አያይዞ ገልጾታል። ዳዊት “አምላክ ሆይ፣ ልቤ ጽኑ ነው። እዘምራለሁ፣ የውዳሴ መዝሙርም አቀርባለሁ” በማለት ዘምሯል። (መዝ. 57:7 NW) በክርስቲያናዊ ስብሰባዎቻችን ላይ የሚዘመሩት መዝሙሮች በጽኑ ልብ ለይሖዋ ‘እንድንዘምርና የውዳሴ መዝሙር እንድናቀርብ’ ጥሩ አጋጣሚ ይከፍቱልናል። ታዲያ አንዳንዶቹን መዝሙሮች በደንብ የማናውቃቸው ከሆነ በቤተሰብ አምልኳችን ወቅት ለምን አንለማመዳቸውም? በሕይወት እስካለን ድረስ ለይሖዋ ለመዘመርና ለእሱ የውዳሴ መዝሙር ለማቅረብ ቁርጥ ውሳኔ እናድርግ።​—መዝ. 104:33

5, 6. ለሌሎች የልግስናና የእንግዳ ተቀባይነት መንፈስ ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው? ይህስ በጉባኤ ውስጥ ምን ዓይነት መንፈስ እንዲሰፍን ያደርጋል?

5 በጉባኤ ውስጥ ፍቅር እንዲሰፍን የምናደርግበት ሌላው መንገድ ለወንድሞቻችንና ለእህቶቻችን የእንግዳ ተቀባይነት መንፈስ ማሳየት ነው። ጳውሎስ ለዕብራውያን ክርስቲያኖች በጻፈው ደብዳቤ የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ “እርስ በርሳችሁ እንደ ወንድማማች ተዋደዱ። እንግዶችን መቀበል አትርሱ” የሚል ማሳሰቢያ ሰጥቷቸው ነበር። (ዕብ. 13:1, 2) ተጓዥ የበላይ ተመልካቾችንና ሚስቶቻቸውን ወይም በጉባኤያችን ውስጥ ያሉ የሙሉ ጊዜ አገልጋዮችን ምግብ መጋበዝ የእንግዳ ተቀባይነት መንፈስ ከምናሳይባቸው ግሩም መንገዶች አንዱ ነው። አልፎ አልፎ አብረውን ቢመገቡ ወይም በቤተሰብ አምልኮ ፕሮግራማችን ላይ ቢገኙ ሊጠቀሙ የሚችሉ መበለቶችን፣ በነጠላ ወላጅ የሚተዳደሩ ቤተሰቦችን ወይም ሌሎች ሰዎችን ለማሰብ ሞክሩ።

6 ጢሞቴዎስ ለጉባኤው አባላት የሚከተለውን ማሳሰቢያ እንዲሰጥ ጳውሎስ ነግሮት ነበር፦ “መልካም ነገር እንዲያደርጉ፣ በመልካም ሥራዎች ባለጸጋ እንዲሆኑ እንዲሁም ለጋሶችና ለማካፈል ፈቃደኞች እንዲሆኑ እዘዛቸው፤ እውነተኛ የሆነውን ሕይወት አጥብቀው መያዝ ይችሉ ዘንድ በዚህ መንገድ ለራሳቸው ውድ ሀብት ማከማቸታቸውን ይኸውም ለወደፊቱ ጊዜ የሚሆን መልካም መሠረት መጣላቸውን ይቀጥሉ።” (1 ጢሞ. 6:17-19) ጳውሎስ ይህን መመሪያ የሰጠው የእምነት ባልንጀሮቹ የልግስና መንፈስ እንዲያዳብሩ ፈልጎ ነው። ኑሮ ከባድ በሚሆንበት ጊዜም እንኳ የልግስና መንፈስ ማሳየት እንችላለን። ይህን ከምናሳይባቸው መንገዶች አንዱ አገልግሎት ስንወጣ እንዲሁም ወደ ስብሰባዎች ስንሄድና ስንመለስ እርዳታ የሚያስፈልጋቸውን ወንድሞች በመኪናችን መውሰድ ነው። እንዲህ ያለ ደግነት የተደረገላቸው ወንድሞችስ ምን ዓይነት መንፈስ ሊኖራቸው ይገባል? አድናቆታቸውን የሚገልጹ አልፎ ተርፎም ከዕለት ወደ ዕለት እየጨመረ ያለውን የነዳጅ ዋጋ ከግምት በማስገባት አቅማቸው የሚፈቅደውን ያህል መዋጮ የሚያደርጉ ከሆነ በጉባኤው ውስጥ ጥሩ መንፈስ እንዲሰፍን አስተዋጽኦ ያደርጋሉ። በተጨማሪም ከመንፈሳዊ ወንድሞቻችንና እህቶቻችን ጋር ሰፋ ያለ ጊዜ በማሳለፍ እንደሚፈለጉና እንደሚወደዱ እንዲሰማቸው ማድረግ እንችላለን። በመሆኑም “በእምነት ለሚዛመዱን ሰዎች” መልካም ነገሮችን ለማድረግ የምንተጋ እንዲሁም ጊዜያችንን እና ያለንን ነገር ለማካፈል ፈቃደኞች ከሆንን ለእነሱ ያለን ፍቅር እየጨመረ እንዲሄድ ማድረግ ብቻ ሳይሆን በጉባኤያችን ውስጥ ሞቅ ያለና ጥሩ መንፈስ እንዲሰፍንም እናደርጋለን።​—ገላ. 6:10

7. የሌሎችን ሚስጥር መጠበቅ በጉባኤ ውስጥ ጥሩ መንፈስ እንዲሰፍን አስተዋጽኦ የሚያደርገው እንዴት ነው?

7 ለእምነት ባልንጀሮቻችን ያለን ፍቅር ይበልጥ እንዲዳብር የሚያደርጉ ሌሎች ምክንያቶችም አሉ፤ ይኸውም ጥሩ ወዳጅ መሆን እና ሚስጥር መጠበቅ ናቸው። (ምሳሌ 18:24ን አንብብ።) እውነተኛ ወዳጅ የሌሎችን ሚስጥር ይጠብቃል። ወንድሞቻችን የውስጣቸውን አውጥተው የሚነግሩንን ሚስጥር ለሌሎች እንደማናወጣባቸው ሲረዱ በመካከላችን ያለው ፍቅር ይበልጥ እየተጠናከረ ይሄዳል። በመሆኑም የሚነገረውን በሚስጥር የሚይዝና እምነት የሚጣልበት ወዳጅ በመሆን በጉባኤ ውስጥ ፍቅርና ቤተሰባዊ መንፈስ እንዲሰፍን እናድርግ።​—ምሳሌ 20:19

በአገልግሎት ቀናተኛ ሁኑ

8. የሎዶቂያ ክርስቲያኖች ምን ምክር ተሰጥቷቸዋል? ለምንስ?

8 ኢየሱስ በሎዶቅያ ለሚገኘው ጉባኤ እንዲህ ብሏል፦ “ሥራህን አውቃለሁ፤ ወይ ቀዝቃዛ ወይ ትኩስ አይደለህም። ቀዝቃዛ ወይም ደግሞ ትኩስ ብትሆን ደስ ባለኝ ነበር። በመሆኑም ለብ ያልክ እንጂ ትኩስም ሆነ ቀዝቃዛ ስላልሆንክ ከአፌ አውጥቼ ልተፋህ ነው።” (ራእይ 3:15, 16) የሎዶቅያ ክርስቲያኖች የአገልግሎት ቅንዓታቸው ቀንሶ ነበር። ይህም እርስ በርስ ያላቸውን ግንኙነት ጭምር እንደነካባቸው ምንም ጥርጥር የለውም። በመሆኑም ኢየሱስ እንዲህ የሚል ፍቅራዊ ማሳሰቢያ ሰጥቷቸዋል፦ “እኔ የምወዳቸውን ሁሉ እገሥጻለሁ እንዲሁም እቀጣለሁ። ስለዚህ ቀናተኛ ሁን፣ ንስሐም ግባ።”​—ራእይ 3:19

9. ለአገልግሎት ያለን አመለካከት በጉባኤው ላይ ምን ተጽዕኖ ያሳድራል?

9 በጉባኤ ውስጥ ጤናማና ጥሩ መንፈስ እንዲሰፍን ለማድረግ የአገልግሎት ቅንዓታችንን አስመልክቶ በቁም ነገር ልናስብበት ይገባል። ጉባኤዎች የተደራጁበት አንደኛው ዓላማ በክልላችን ውስጥ ያሉ በግ መሰል ሰዎችን ለመፈለግና እነሱን በመንፈሳዊ ለማነጽ ነው። በመሆኑም ልክ እንደ ኢየሱስ፣ ደቀ መዛሙርት በማድረጉ ሥራ በቅንዓት መካፈል ይኖርብናል። (ማቴ. 28:19, 20፤ ሉቃስ 4:43) ለአገልግሎት ያለንን ቅንዓት እያሳደግን በሄድን ቁጥር “ከአምላክ ጋር አብረን የምንሠራ” እንደመሆናችን በመካከላችን ያለው አንድነት ይበልጥ እየተጠናከረ ይሄዳል። (1 ቆሮ. 3:9) የእምነት ባልንጀሮቻችን በመስክ አገልግሎት ላይ ስለ እምነታቸው ሲያስረዱና ለመንፈሳዊ ነገሮች ያላቸውን አድናቆት ሲገልጹ ስንመለከት ለእነሱ ያለን ፍቅርና አክብሮት ይጨምራል። ከዚህም በላይ ‘ተስማምተን’ ወይም ተደጋግፈን የምናገለግል ከሆነ በጉባኤው ውስጥ አንድነት እንዲኖር አስተዋጽኦ እናደርጋለን።​—ሶፎንያስ 3:9ን አንብብ።

10. አገልግሎታችንን ለማሻሻል ጥረት ማድረጋችን በሌሎች የጉባኤው አባላት ላይ ምን ተጽዕኖ ያሳድራል?

10 አገልግሎታችንን ለማሻሻል ጥረት ማድረጋችንም በሌሎች ላይ በጎ ተጽዕኖ ያሳድራል። በአገልግሎት ላይ ለምናገኛቸው ሰዎች አሳቢነት ለማሳየትና ልባቸውን ለመንካት ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ ጥረት የምናደርግ ከሆነ ለአገልግሎት ያለን ቅንዓት ይጨምራል። (ማቴ. 9:36, 37) ቅንዓታችን ወደ ሌሎች የእምነት ባልንጀሮቻችንም ሊተላለፍ ይችላል። ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን ለስብከት በሚያሰማራቸው ጊዜ በተናጠል እንዲሄዱ ከማድረግ ይልቅ ሁለት ሁለት አድርጎ ልኳቸዋል። (ሉቃስ 10:1) እንዲህ ማድረጉ ማበረታቻና ሥልጠና ለማግኘት ብቻ ሳይሆን ለአገልግሎት ያላቸውን ቅንዓት ይበልጥ ለማቀጣጠል ረድቷቸዋል። ቀናተኛ ከሆኑ የመንግሥቱ አስፋፊዎች ጋር አብሮ ማገልገል አያስደስትም? ቅንዓታቸው እኛም በስብከቱ ሥራ ይበልጥ ተሳትፎ እንድናደርግ ያበረታታናል።​—ሮም 1:12

ከማጉረምረም መንፈስና ኃጢአትን ከመደበቅ ተቆጠቡ

11. በሙሴ ዘመን የነበሩ አንዳንድ እስራኤላውያን ምን ዓይነት መንፈስ አዳብረው ነበር? ይህስ ምን አስከትሎባቸዋል?

11 እስራኤላውያን እንደ አንድ ብሔር ከተደራጁ ከጥቂት ሳምንታት በኋላ፣ ባገኙት ነገር የማይረኩና አጉረምራሚዎች መሆን ጀመሩ። ይህ ደግሞ በይሖዋና የእሱ ተወካይ በሆኑት ላይ እንዲያምፁ አድርጓቸዋል። (ዘፀ. 16:1, 2) ከግብፅ ከወጡት እስራኤላውያን መካከል ወደ ተስፋይቱ ምድር የገቡት በጣም ጥቂት ናቸው። ሙሴም እንኳ የእስራኤል ሕዝብ መጥፎ መንፈስ ባሳየበት ወቅት የሰጠው ምላሽ ወደ ተስፋይቱ ምድር እንዳይገባ አድርጎታል! (ዘዳ. 32:48-52) ታዲያ እንዲህ ዓይነት መንፈስ እንዳይጠናወተን ምን ማድረግ እንችላለን?

12. የማጉረምረም መንፈስ በውስጣችን እንዳያቆጠቁጥ መጠንቀቅ የምንችለው እንዴት ነው?

12 የማጉረምረም መንፈስ በውስጣችን እንዳያቆጠቁጥ መጠንቀቅ ይኖርብናል። የትሕትና ባሕርይ ማዳበራችንና ለሥልጣን አክብሮት ማሳየታችን ጠቃሚ መሆኑ ባይካድም ከእነማን ጋር ጊዜ እንደምናሳልፍ ቆም ብለን ማሰባችንም አስፈላጊ ነው። የመዝናኛ ምርጫችን ጥሩ ካልሆነ ወይም በሥራ አሊያም በትምህርት ቤት ከምናገኛቸው ለጽድቅ መሠረታዊ ሥርዓቶች ደንታ ከሌላቸው ሰዎች ጋር ሳያስፈልግ ጊዜ የምናሳልፍ ከሆነ ውጤቱ አሳዛኝ ይሆናል። በመሆኑም አፍራሽ አስተሳሰብን ወይም በራስ የመመራት መንፈስን ከሚያንጸባርቁ ሰዎች ጋር ባለን ግንኙነት ረገድ ገደብ ማበጀታችን የጥበብ አካሄድ ነው።​—ምሳሌ 13:20

13. ጎጂ ተጽዕኖ ሊያሳድር የሚችለው የማጉረምረም ባሕርይ መንፈሳዊ ጉዳት የሚያስከትሉ ምን ሌሎች ችግሮች በጉባኤ ውስጥ እንዲፈጠሩ ሊያደርግ ይችላል?

13 ጎጂ ተጽዕኖ ሊያሳድር የሚችለው ይህ የማጉረምረም ባሕርይ መንፈሳዊ ጉዳት የሚያስከትሉ ሌላ ዓይነት ችግሮች እንዲፈጠሩ ሊያደርግ ይችላል። ለምሳሌ ያህል፣ ማጉረምረም የጉባኤውን ሰላምና አንድነት ሊያደፈርስ ይችላል። ከዚህም በተጨማሪ ስለ እምነት ባልንጀሮቻችን አሉታዊ ወሬ መንዛታችን የእነሱን ስሜት የሚጎዳ ከመሆኑም ሌላ እንደ ስም ማጥፋትና መሳደብ ያሉ ኃጢአቶችን ወደ መፈጸም ሊመራን ይችላል። (ዘሌ. 19:16፤ 1 ቆሮ. 5:11) በመጀመሪያው መቶ ዘመን በሚገኘው ጉባኤ ውስጥ ያሉ አንዳንድ አጉረምራሚ ክርስቲያኖች ‘ጌትነትን ይንቁ እንዲሁም የተከበሩትን ይሳደቡ’ ነበር። (ይሁዳ 8, 16) በጉባኤ ውስጥ ኃላፊነት ባላቸው ወንድሞች ማጉረምረም በይሖዋ ዘንድ ተቀባይነት እንደማይኖረው ግልጽ ነው።

14, 15. (ሀ) ኃጢአቶችን ችላ ብሎ ማለፍ በጉባኤው ላይ ምን ተጽዕኖ ሊያሳድር ይችላል? (ለ) አንድ ሰው በድብቅ ኃጢአት እየፈጸመ እንደሆነ ብናውቅ ምን ማድረግ ይኖርብናል?

14 አንድ ሰው በድብቅ ኃጢአት እንደሚፈጽም ምናልባትም ከልክ በላይ አልኮል እንደሚጠጣ ወይም የብልግና ምስሎችን እንደሚመለከት አሊያም ሥነ ምግባር የጎደለው አካሄድ እንደሚከተል ብናውቅ ምን እናደርጋለን? (ኤፌ. 5:11, 12) ከባድ ኃጢአቶችን አይተን እንዳላየን የምናልፍ ከሆነ የይሖዋ መንፈስ በጉባኤ ውስጥ እንደ ልብ አይሠራም፤ እንዲሁም የጉባኤው ሰላም ይደፈርሳል። (ገላ. 5:19-23) የጥንቶቹ የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ጉባኤውን ከመጥፎ ድርጊቶች እንዳነጹ ሁሉ በዛሬው ጊዜ ያሉ የአምላክ አገልጋዮችም በመካከላቸው ያለውን ጤናማና ጥሩ መንፈስ ለመጠበቅ ሲሉ ማንኛውንም በካይ ተጽዕኖ ከጉባኤው ማስወገድ ይኖርባቸዋል። አንተስ የጉባኤውን ሰላም ለመጠበቅ ምን አስተዋጽኦ ማበርከት ትችላለህ?

15 ቀደም ሲል እንደተመለከትነው፣ በአንዳንድ ጉዳዮች ረገድ በተለይ ደግሞ ወንድሞቻችን እምነት ጥለውብን የውስጥ ስሜታቸውንና ሐሳባቸውን ሲያካፍሉን ሚስጥራቸውን መጠበቃችን አስፈላጊ ነው። የሌላን ሰው ሚስጥር ማውጣት ከባድ ስህተት ከመሆኑም በላይ በጣም ጎጂ ነው! ያም ሆኖ ከባድ ኃጢአት በሚፈጸምበት ጊዜ እንዲህ ያሉ ጉዳዮችን እንዲመለከቱ ቅዱስ ጽሑፋዊ ኃላፊነት ለተሰጣቸው ወንድሞች ማለትም ለጉባኤ ሽማግሌዎች ሊነገራቸው ይገባል። (ዘሌዋውያን 5:1ን አንብብ።) እንግዲያው አንድ ክርስቲያን እንዲህ ያለ ኃጢአት እንደፈጸመ ካወቅን ወደ ሽማግሌዎች ቀርቦ እርዳታ እንዲያገኝ ማበረታታት ይኖርብናል። (ያዕ. 5:13-15) ይሁንና ግለሰቡ ምክንያታዊ በሆነ የጊዜ ገደብ ውስጥ ካልተናገረ ጉዳዩን እኛ ራሳችን ለሽማግሌዎች መናገር ይኖርብናል።

16. ከባድ ኃጢአቶችን ለሽማግሌዎች መንገር የጉባኤው መንፈስ እንዲጠበቅ የሚያደርገው እንዴት ነው?

16 የክርስቲያን ጉባኤ መንፈሳዊ ጥበቃ የምናገኝበት ቦታ ነው፤ በመሆኑም ከባድ ኃጢአት ሲፈጸም በመናገር ይህን ቦታ መጠበቅ ይኖርብናል። ሽማግሌዎች ኃጢአት የሠራው ሰው ወደ አእምሮው እንዲመለስ ከረዱትና ግለሰቡም የተሰጠውን ምክርና ተግሣጽ ተቀብሎ ንስሐ ከገባ አደጋ ላይ ወድቆ የነበረው የጉባኤው መንፈስ ይታደሳል። ይሁንና ከባድ ኃጢአት የሚፈጽመው ግለሰብ ንስሐ ለመግባትና ሽማግሌዎች የሚሰጡትን ፍቅራዊ ምክር ለመቀበል ፈቃደኛ ባይሆንስ? ግለሰቡ ከጉባኤው አባልነት መሰረዙ እኛን ሊበክል የሚችለው ነገር “እንዲወገድ” እንዲሁም የጉባኤው መንፈስ እንዲጠበቅ ያደርጋል። (1 ቆሮንቶስ 5:5ን አንብብ።) በእርግጥም የጉባኤው መንፈስ እንዲጠበቅ የምንፈልግ ከሆነ ሁላችንም ተገቢ የሆነ እርምጃ መውሰድ፣ ከሽማግሌዎች አካል ጋር መተባበር እንዲሁም ለእምነት ባልንጀሮቻችን ደኅንነት ከልብ ማሰብ ይኖርብናል።

“የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ” ጥረት ማድረግ

17, 18. “የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ” ምን ሊረዳን ይችላል?

17 የጥንቶቹ የኢየሱስ ተከታዮች ‘የሐዋርያቱን ትምህርት በትኩረት መከታተላቸው’ በጉባኤው ውስጥ የአንድነት መንፈስ እንዲኖር አድርጓል። (ሥራ 2:42) በተጨማሪም ሐዋርያት የሚሰጧቸውን ቅዱስ ጽሑፋዊ ምክርና መመሪያ ከፍ አድርገው ይመለከቱ ነበር። በዛሬው ጊዜም ቢሆን ሽማግሌዎች ከታማኝና ልባም ባሪያ ጋር መተባበራቸው የጉባኤው አንድነት ተጠብቆ እንዲቆይ አስተዋጽኦ አድርጓል። (1 ቆሮ. 1:10) የይሖዋ ድርጅት የሚሰጠንን ቅዱስ ጽሑፋዊ መመሪያ ተግባራዊ የምናደርግ እንዲሁም ሽማግሌዎች የሚሰጡንን አመራር የምንከተል ከሆነ “አንድ ላይ በሚያስተሳስረው የሰላም ማሰሪያ የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ልባዊ ጥረት” እንደምናደርግ እናሳያለን።​—ኤፌ. 4:3

18 እንግዲያው በተቻለን መጠን በጉባኤ ውስጥ ጤናማና ጥሩ መንፈስ እንዲሰፍን ጥረት እናድርግ። እንዲህ የምናደርግ ከሆነ ‘የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ ከምናሳየው መንፈስ ጋር ይሆናል።’​—ፊልጵ. 4:23

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 19 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

የሚያንጹ ሐሳቦችን ለመስጠት ዝግጅት በማድረግ በጉባኤ ውስጥ ጥሩ መንፈስ እንዲሰፍን አስተዋጽኦ ታደርጋላችሁ?

[በገጽ 20 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

መዝሙሮቻችንን በደንብ በመለማመድ በጉባኤ ውስጥ ጥሩ መንፈስ እንዲኖር አስተዋጽኦ አድርጉ