በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የጥድፊያ ስሜታችሁ እንዳይጠፋ ተጠንቀቁ

የጥድፊያ ስሜታችሁ እንዳይጠፋ ተጠንቀቁ

የጥድፊያ ስሜታችሁ እንዳይጠፋ ተጠንቀቁ

“ቃሉን ስበክ፣ . . . በጥድፊያ ስሜት አገልግል።”​—2 ጢሞ. 4:2

ልታብራራ ትችላለህ?

በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበሩ ክርስቲያኖች በጥድፊያ ስሜት የሰበኩት ለምንድን ነው?

የጥድፊያ ስሜታችን እንዳይጠፋ መጠንቀቅ የምንችለው እንዴት ነው?

በአሁኑ ጊዜ የመንግሥቱን መልእክት መስበክ ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ አጣዳፊ የሆነው ለምንድን ነው?

1, 2. ‘በጥድፊያ ስሜት እንድናገለግል’ ከተሰጠን ትእዛዝ ጋር በተያያዘ የትኞቹ ጥያቄዎች ይነሳሉ?

ነፍስ አድን በሆነ ሥራ ላይ የተሰማሩ ሰዎች በአብዛኛው ነገሮችን የሚያከናውኑት በጥድፊያ ስሜት ነው። ለምሳሌ፣ የእሳት አደጋ ሠራተኞች የእርዳታ ጥሪ ሲደርሳቸው በፍጥነት አደጋው ወደ ተከሰተበት ቦታ ይሄዳሉ፤ ምክንያቱም የሰው ሕይወት አደጋ ላይ እንደሆነ ያውቃሉ።

2 የይሖዋ ምሥክሮች እንደመሆናችን መጠን ከጥፋት እንዲተርፉ ሰዎችን መርዳት እንፈልጋለን። በመሆኑም የመንግሥቱን ምሥራች የመስበክ ተልእኳችንን በቁም ነገር እንመለከተዋለን። ይሁንና ሥራችንን በጥድፊያ ስሜት እናከናውናለን ሲባል በደመ ነፍስ እንራወጣለን ማለት አይደለም። ታዲያ ሐዋርያው ጳውሎስ “ቃሉን ስበክ፣ . . . በጥድፊያ ስሜት አገልግል” የሚለውን ማሳሰቢያ ሲሰጥ ምን ማለቱ ነበር? (2 ጢሞ. 4:2) በጥድፊያ ስሜት መስበክ የምንችለው እንዴት ነው? ሥራችን በጣም አጣዳፊ የሆነውስ ለምንድን ነው?

የስብከቱ ሥራችን አጣዳፊ የሆነው ለምንድን ነው?

3. ሰዎች የመንግሥቱን መልእክት መቀበል ወይም አለመቀበላቸው በሕይወታቸው ላይ ምን ተጽዕኖ ያሳድራል?

3 ምሥራቹን መስበክ ምን ጥቅም እንደሚያስገኝና አለመስበክ ደግሞ በሰዎች ላይ ምን ጉዳት እንደሚያስከትል ማሰብህ መልእክቱን ለሌሎች የማድረሱ ጉዳይ አንገብጋቢ እንደሆነ ለመገንዘብ እንደሚያስችልህ ምንም ጥርጥር የለውም። (ሮም 10:13, 14) የአምላክ ቃል እንዲህ ይላል፦ “ክፉውን ሰው፣ ‘በእርግጥ ትሞታለህ’ ብለው፣ እርሱም ከኀጢአቱ ተመልሶ ቀና የሆነውንና ትክክለኛውንም ነገር ቢያደርግ፣ . . . በእርግጥ እርሱ በሕይወት ይኖራል፤ አይሞትምም። ከሠራው ኀጢአት አንዱም አይታሰብበትም።” (ሕዝ. 33:14-16) መጽሐፍ ቅዱስ፣ የመንግሥቱን መልእክት የሚያስተምሩ ሰዎች ‘ራሳቸውንም ሆነ የሚሰሟቸውን እንደሚያድኑ’ ይናገራል።​—1 ጢሞ. 4:16፤ ሕዝ. 3:17-21

4. ክህደት፣ በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበሩ ክርስቲያኖችን በጥድፊያ ስሜት እንዲሰብኩ ያደረጋቸው እንዴት ነው?

4 ጳውሎስ፣ ለጢሞቴዎስ በጥድፊያ ስሜት እንዲሰብክ ያሳሰበው ለምን እንደሆነ ለመረዳት የጥናት ርዕሱ ከተመሠረተበት ጥቅስ ቀጥሎ ያሉትን ሐሳቦች እንመልከት። ጥቅሱ እንዲህ ይላል፦ “ቃሉን ስበክ፣ አመቺ በሆነ ወቅትም ሆነ በአስቸጋሪ ወቅት በጥድፊያ ስሜት አገልግል፤ በብዙ ትዕግሥትና በማስተማር ጥበብ ገሥጽ፣ ውቀስ እንዲሁም አጥብቀህ ምከር። ምክንያቱም ጤናማውን ትምህርት የማይታገሡበት ጊዜ ይመጣል፤ ከዚህ ይልቅ ከራሳቸው ፍላጎት ጋር በሚስማማ ሁኔታ ጆሯቸውን እንዲኮረኩሩላቸው ለራሳቸው አስተማሪዎችን ይሰበስባሉ፤ እንዲሁም እውነትን ከመስማት ጆሯቸውን ይመልሳሉ።” (2 ጢሞ. 4:2-4) ኢየሱስ ክህደት የሚስፋፋበት ጊዜ እንደሚመጣ ትንቢት ተናግሮ ነበር። (ማቴ. 13:24, 25, 38) ይህ ጊዜ እየቀረበ በመሆኑ ክርስቲያኖች በሐሰት ትምህርቶች ተማርከው እንዳይታለሉ ጢሞቴዎስ በጉባኤ ውስጥ ጭምር በጥድፊያ ስሜት ‘ቃሉን መስበክ’ ነበረበት። የሰዎች ሕይወት አደጋ ላይ ነበር። ስለ ዘመናችንስ ምን ማለት ይቻላል?

5, 6. በአገልግሎት ላይ ምን ዓይነት አመለካከት ያላቸው ሰዎች ሊያጋጥሙን ይችላሉ?

5 ከእውነተኛው አምልኮ የወጣው ክህደት በአሁኑ ወቅት ሥር ከመስደዱም በላይ በጣም ተስፋፍቷል። (2 ተሰ. 2:3, 8) በዛሬው ጊዜ የሰዎችን ጆሮ የሚኮረኩሩ ትምህርቶች የትኞቹ ናቸው? የዝግመተ ለውጥ ትምህርት በብዙ ቦታዎች ሃይማኖታዊ ድጋፍ አግኝቷል። ለወትሮው ከሳይንስ አንጻር ማብራሪያ ሲሰጥበት የነበረው የዝግመተ ለውጥ ጽንሰ ሐሳብ አሁን አሁን ሃይማኖታዊ መልክ እየያዘ ነው፤ እንዲሁም ሰዎች ለአምላክና ለባልንጀሮቻቸው ባላቸው አመለካከት ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ እያደረገ ነው። በብዙዎች ዘንድ ተቀባይነት ያገኘው ሌላው አመለካከት ደግሞ አምላክ ለሰው ልጆች ምንም ደንታ ስለሌለው እኛም በሕይወታችን ውስጥ ለእሱ ቦታ መስጠት አያስፈልገንም የሚለው ነው። እነዚህ ትምህርቶች በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች በመንፈሳዊ እንዲያንቀላፉ እስኪያደርጉ ድረስ ይህን ያህል ትኩረት የሳቡት ለምንድን ነው? ሁለቱም አመለካከቶች የሚያስተላልፉት መልእክት ተመሳሳይ ነው፤ ይኸውም ‘ስላደረከው ነገር የሚጠይቅህ አካል ስለሌለ የፈለከውን ነገር ማድረግ ትችላለህ’ የሚል ነው። በእርግጥም ይህ መልእክት የብዙዎችን ጆሮ ኮርኩሯል።​—መዝሙር 10:4ን አንብብ።

6 የሰዎችን ጆሮ የሚኮረኩሩ ሌሎች ነገሮችም አሉ። ቤተ ክርስቲያን የሚሄዱ አንዳንድ ሰዎች ‘የፈለግከውን ነገር ብታደርግ አምላክ ይወድሃል’ የሚሉ ትምህርቶችን መስማት ያስደስታቸዋል። ቀሳውስትና ፓስተሮች ክብረ በዓላት፣ ሥርዓተ ቁርባንና ምስሎች የአምላክን በረከት እንደሚያስገኙ በማሳመን የሰዎችን ጆሮ ይኮረኩራሉ። ይሁንና እነዚህ ቤተ ክርስቲያን የሚያዘወትሩ ሰዎች ምን ያህል አደገኛ ሁኔታ ውስጥ እንዳሉ አይገነዘቡም። (መዝ. 115:4-8) እኛ ግን ትክክለኛውን የመጽሐፍ ቅዱስ መልእክት እንዲረዱ በማድረግ ከመንፈሳዊ እንቅልፋቸው የምንቀሰቅሳቸው ከሆነ የአምላክ መንግሥት ከሚያመጣው በረከት ተካፋይ ይሆናሉ።

በጥድፊያ ስሜት መስበክ ሲባል ምን ማለት ነው?

7. የጥድፊያ ስሜት እንዳለን ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው?

7 አንድ ጠንቃቃ የሆነ ዶክተር ለአንድ ሰው ቀዶ ጥገና በሚያደርግበት ጊዜ ሙሉ ትኩረቱን በሥራው ላይ ማድረግ ይኖርበታል፤ ምክንያቱም የግለሰቡ ሕይወት አደጋ ላይ ነው። እኛም በክርስቲያናዊ አገልግሎታችን ላይ ትኩረት በማድረግ ይኸውም ሰዎችን ሊማርኩ የሚችሉ ርዕሰ ጉዳዮች፣ ጥያቄዎችና መረጃዎች የትኞቹ እንደሆኑ በማሰብ የጥድፊያ ስሜት እንዳለን ማሳየት እንችላለን። በተጨማሪም የጥድፊያ ስሜት ካለን ብዙ ሰዎች እኛን ለማናገር ይበልጥ ፈቃደኛ በሚሆኑበት ሰዓት ላይ ቤታቸው ለመሄድ ፕሮግራማችንን እናመቻቻለን።​—ሮም 1:15, 16፤ 1 ጢሞ. 4:16

8. የጥድፊያ ስሜት እንዳለን የምናሳይበት ሌላው መንገድ ምንድን ነው?

8 ለምን ነገር ቅድሚያ መስጠት እንዳለብን መገንዘባችን የጥድፊያ ስሜት እንዳለን የምናሳይበት ሌላው መንገድ ነው። (ዘፍጥረት 19:15ን አንብብ።) ለምሳሌ፣ አንድ ዶክተር የምርመራ ውጤትህን ከተመለከተ በኋላ ወደ ቢሮው በመጥራት እንዲህ ብሎ ጠበቅ አድርጎ ነገረህ እንበል፦ “ይኸውልህ፣ ያለህበት ሁኔታ ጊዜ የሚሰጥ አይደለም። ከአንድ ወር ባነሰ ጊዜ ውስጥ አንድ ነገር ማድረግ አለብህ።” በዚህ ጊዜ የእርዳታ ጥሪ እንደደረሰው የእሳት አደጋ ሠራተኛ ከቢሮው ዘለህ እንደማትወጣ የታወቀ ነው። ከዚህ ይልቅ በእርጋታ የሚሰጥህን ምክር ታዳምጣለህ፤ ከዚያም ወደ ቤትህ ሄደህ ቅድሚያ መስጠት ስላለብህ ነገር በጥሞና ታስባለህ።

9. ጳውሎስ በኤፌሶን በነበረበት ጊዜ ምሥራቹን በጥድፊያ ስሜት ሰብኳል እንድንል የሚያደርገን ምንድን ነው?

9 ጳውሎስ ምሥራቹን በእስያ አውራጃ እንዴት እንደሰበከ ለኤፌሶን ሽማግሌዎች ከነገራቸው ነገር በመነሳት ይህ ሐዋርያ የነበረውን የጥድፊያ ስሜት ማስተዋል እንችላለን። (የሐዋርያት ሥራ 20:18-21ን አንብብ።) እዚያ ከደረሰ ከመጀመሪያው ዕለት አንስቶ ከቤት ወደ ቤት በመሄድ ምሥራቹን በመስበኩ ሥራ ተጠምዶ ነበር። በተጨማሪም ቋሚ ፕሮግራም በማውጣት ለሁለት ዓመት ያህል “በጢራኖስ የትምህርት ቤት አዳራሽ በየዕለቱ ንግግር ይሰጥ ነበር።” (ሥራ 19:1, 8-10) ከዚህ በግልጽ መረዳት እንደምንችለው ጳውሎስ የጥድፊያ ስሜት ያለው መሆኑ በዕለት ተዕለት ልማዱ ላይ ማስተካከያ እንዲያደርግ አነሳስቶታል። ‘አገልግሎታችንን በጥድፊያ ስሜት’ እንድናከናውን የተሰጠን መመሪያ ዓላማው እኛን ከልክ በላይ እንድንወጣጠር ለማድረግ አይደለም። ያም ሆኖ በሕይወታችን ውስጥ ለስብከቱ ሥራ ቅድሚያ መስጠት ይኖርብናል።

10. ከ100 ዓመታት ገደማ በፊት የነበሩ ክርስቲያኖች በጥድፊያ ስሜት በማገልገላቸው ደስ ሊለን የሚገባው ለምንድን ነው?

10 ከ1914 በፊት የነበሩ አነስተኛ ቁጥር ያላቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች ምሥራቹን በመስበክ ረገድ የተዉት ምሳሌ በጥድፊያ ስሜት ማገልገል ሲባል ምን ማለት እንደሆነ እንድንገነዘብ ያደርገናል። እነዚህ የአምላክ አገልጋዮች በጥቂት ሺዎች ብቻ የሚቆጠሩ ቢሆኑም እንኳ የጊዜውን አጣዳፊነት በመገንዘብ የመንግሥቱን ስብከት ሥራ በቅንዓት አከናውነዋል። በመቶዎች በሚቆጠሩ ጋዜጦች ላይ ስብከቶችን ያወጡ የነበረ ከመሆኑም በላይ ባለቀለም ስላይዶችንና ተንቀሳቃሽ ምስሎችን የያዘውን “የፍጥረት ፎቶ ድራማ” የተባለ ፊልም ያሳዩ ነበር። በዚህ መንገድ ምሥራቹን በሚሊዮን ለሚቆጠሩ ሰዎች አዳርሰዋል። እነዚህ ክርስቲያኖች የጥድፊያ ስሜት ባይኖራቸው ኖሮ ከእኛ መካከል ስንቶቻችን እውነትን ማወቅ እንችል ነበር?​—መዝሙር 119:60ን አንብብ።

የጥድፊያ ስሜታችሁ እንዳይጠፋ ተጠንቀቁ

11. አንዳንዶች የጥድፊያ ስሜታቸውን እንዲያጡ ያደረጋቸው ምንድን ነው?

11 አንድ ሰው ትኩረቱ ከተከፋፈለ የስብከት ሥራው ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆነ ላይገነዘብ ይችላል። የሰይጣን ሥርዓት የተዋቀረው የግል ፍላጎቶቻችንን እንድናሳድድና እምብዛም አስፈላጊ ባልሆኑ ነገሮች እንድንጠላለፍ ሊያደርገን በሚችል መንገድ ነው። (1 ጴጥ. 5:8፤ 1 ዮሐ. 2:15-17) በአንድ ወቅት ለይሖዋ አገልግሎት ቅድሚያ ይሰጡ የነበሩ አንዳንድ ሰዎች ከጊዜ በኋላ የጥድፊያ ስሜታቸውን አጥተዋል። ለምሳሌ በመጀመሪያው መቶ ዘመን ይኖር የነበረው ዴማስ የተባለ ክርስቲያን የጳውሎስ ‘የሥራ ባልደረባ’ ነበር፤ ይሁንና ዴማስ ከጊዜ በኋላ ክፉ በሆነው ሥርዓት ትኩረቱ ተከፋፍሏል። ዴማስ በችግር ጊዜ ወንድሙን ማበረታታቱን ከመቀጠል ይልቅ ለሌላ ነገር ቅድሚያ በመስጠት ጳውሎስን ትቶት ሄዷል።​—ፊል. 23, 24፤ 2 ጢሞ. 4:10

12. በአሁኑ ጊዜ የትኛው አጋጣሚ ተከፍቶልናል? ወደፊት ለዘላለም ስንኖርስ ምን አጋጣሚዎች ይኖሩናል?

12 የጥድፊያ ስሜታችንን ጠብቀን ለመቆየት ከፈለግን ለሥጋዊ ፍላጎታችን ቅድሚያ እንድንሰጥ የሚደረግብንን ግፊት መቋቋም አለብን። በሌላ በኩል ደግሞ ‘እውነተኛ የሆነውን ሕይወት አጥብቀን ለመያዝ’ ጥረት ማድረግ ይኖርብናል። (1 ጢሞ. 6:18, 19) በአምላክ መንግሥት ሥር በምድር ላይ የዘላለም ሕይወት አግኝተን በምንኖርበት ጊዜ አስደሳች የሆኑ ሥራዎችን ለማከናወን የሚያስችሉ በርካታ አጋጣሚዎችን እንደምናገኝ ጥርጥር የለውም። ሰዎች ከአርማጌዶን እንዲተርፉ በመርዳቱ ሥራ መካፈል ግን በሌላ ጊዜ የምናገኘው አጋጣሚ አይደለም።

13. ከጨለማ ወጥተን ክርስቲያን ከሆንን በኋላ የጥድፊያ ስሜታችንን እንዳናጣ ምን ማድረግ ይኖርብናል?

13 በዓለም ላይ የሚገኙ አብዛኞቹ ሰዎች በመንፈሳዊ አንቀላፍተው ባሉበት በዚህ ጊዜ የጥድፊያ ስሜታችንን እንዳናጣ ምን ሊረዳን ይችላል? በአንድ ወቅት በጨለማ ውስጥ በእንቅልፍ ላይ እንደነበርን ማስታወስ ይኖርብናል። ይሁንና ጳውሎስ እንደተናገረው ከእንቅልፋችን ነቅተናል፤ እንዲሁም ክርስቶስ በእኛ ላይ አብርቷል። በመሆኑም አሁን ብርሃን አብሪዎች የመሆን መብት አግኝተናል። (ኤፌሶን 5:14ን አንብብ።) ጳውሎስ ይህን ከገለጸ በኋላ እንዲህ ብሏል፦ “ስለዚህ የምትመላለሱት ጥበብ እንደጎደላቸው ሰዎች ሳይሆን እንደ ጥበበኛ ሰዎች መሆኑን ምንጊዜም በጥንቃቄ አስተውሉ፤ ቀኖቹ ክፉዎች ስለሆኑ ለራሳችሁ አመቺ የሆነውን ጊዜ ግዙ።” (ኤፌ. 5:15, 16) እንዲህ ባለ ክፉ ጊዜ ውስጥ የምንገኝ እንደመሆናችን መጠን በመንፈሳዊ ንቁ ለመሆን በሚያስችሉን እንቅስቃሴዎች ለመካፈል ‘አመቺ የሆነውን ጊዜ እንግዛ።’

የምንኖረው ወሳኝ በሆነ ወቅት ነው

14-16. የስብከቱ ሥራ ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ ዛሬ አጣዳፊ የሆነው ለምንድን ነው?

14 ክርስቲያናዊ አገልግሎታችን ምንጊዜም ቢሆን አጣዳፊ ነው፤ አሁን ግን የስብከቱን ሥራ ማከናወን ከምንጊዜውም በበለጠ አንገብጋቢ ሆኗል። ከ1914 ጀምሮ በአምላክ ቃል ላይ የተጻፉት የምልክቱ የተለያዩ ገጽታዎች በግልጽ እየታዩ ነው። (ማቴ. 24:3-51) የሰው ዘር ሕልውና ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ አደጋ ላይ ወድቋል። ልዕለ ኃያላን መንግሥታት በቅርቡ የተለያዩ ስምምነቶችን ቢያደርጉም አሁንም ለመወንጨፍ ዝግጁ የሆኑ ከ2,000 የሚበልጡ ኑክሌር ተሸካሚ ሚሳይሎች አሉ። ኑክሌር ለመሥራት የሚያገለግሉ ንጥረ ነገሮች በተለያዩ ጊዜያት “እንደጠፉ” ባለሥልጣናት ከመቶ ጊዜ በላይ ሪፖርት አድርገዋል። ምናልባት የተወሰኑት በአሸባሪዎች እጅ ገብተው ይሆን? አንዳንዶች፣ አሸባሪዎች በሚቀሰቅሱት ጦርነት ሳቢያ የሰው ዘር ከምድረ ገጽ ሊጠፋ ይችላል የሚል ስጋት አላቸው። ሆኖም የሰውን ዘር ሕልውና አደጋ ላይ የጣለው ጦርነት ብቻ አይደለም።

15 “በ21ኛው መቶ ዘመን በዓለም አቀፍ ደረጃ ለጤና አስጊ ከሆኑት ነገሮች ሁሉ ትልቁን ቦታ የያዘው የአየር ንብረት ለውጥ ነው” በማለት ዘ ላንሴት የተባለ መጽሔትና የለንደን ዩኒቨርሲቲ በ2009 ባወጡት አንድ ሪፖርት ላይ ገልጸዋል። ሪፖርቱ እንዲህ ይላል፦ “የአየር ንብረት ለውጥ በጤና ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖ በሚቀጥሉት አሥርተ ዓመታት አብዛኛውን የሰው ዘር የሚነካ ከመሆኑም በላይ በቢሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎችን ሕይወትና ደኅንነት ከመቼውም ጊዜ በበለጠ አደጋ ላይ ይጥላል።” የአየር ንብረት ለውጥ የባሕር ጠለል ከፍ እንዲል እንዲሁም ድርቅ፣ የውኃ መጥለቅለቅ፣ ወረርሽኝና አደገኛ አውሎ ነፋስ እንዲከሰት ብሎም እየተመናመነ የሄደውን የተፈጥሮ ሀብት ለመቆጣጠር የሚደረገው ሽሚያ ጦርነት እንዲነሳ ስለሚያደርግ ጥፋቱ መጠነ ሰፊ ሊሆን ይችላል። በእርግጥም፣ ጦርነትና የተፈጥሮ አደጋዎች የሰውን ዘር ስጋት ላይ ጥለውታል።

16 አንዳንዶች፣ ኢየሱስ የተናገረው ‘ምልክት’ ፍጻሜውን የሚያገኘው የኑክሌር ጦርነት ሲነሳ ነው ብለው ያስባሉ። ይሁንና አብዛኞቹ ሰዎች የምልክቱን ትክክለኛ ትርጉም አልተረዱም። የክርስቶስ መገኘት እውን እንደሆነና ይህ ሥርዓት የሚጠፋበት ጊዜ በፍጥነት እየቀረበ እንዳለ የሚጠቁመው ምልክት ለአሥርተ ዓመታት ሲታይ ቆይቷል። (ማቴ. 24:3) የምልክቱ የተለያዩ ገጽታዎች የአሁኑን ያህል በብዛት የታዩበት ጊዜ የለም። በመሆኑም ሰዎች ከመንፈሳዊ እንቅልፋቸው የሚነቁበት ጊዜ አሁን ነው። አገልግሎታችን ደግሞ ሰዎችን ለማንቃት ይረዳል።

17, 18. (ሀ) “ዘመኑን” ማወቃችን ምን እንድናደርግ ሊያነሳሳን ይገባል? (ለ) ሰዎች ለመንግሥቱ መልእክት ያላቸውን አመለካከት እንዲቀይሩ የሚያደርጋቸው ምን ሊሆን ይችላል?

17 ለይሖዋ ያለንን ፍቅር ለማሳየትና በዚህ በመጨረሻው ዘመን የተሰጠንን የስብከት ሥራ ለማጠናቀቅ የቀረን ጊዜ አጭር ነው። ጳውሎስ በመጀመሪያው መቶ ዘመን በሮም ለሚገኙ ክርስቲያኖች እንደሚከተለው በማለት ተናግሮ ነበር፦ “ዘመኑን ስለምታውቁም ይህን አድርጉ፤ አማኞች ከሆንበት ጊዜ ይልቅ አሁን መዳናችን ይበልጥ ስለቀረበ ከእንቅልፍ የምትነቁበት ሰዓት አሁን ነው።” ይህ ማሳሰቢያ ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ ዛሬ ለእኛ ትልቅ ትርጉም አለው።​—ሮም 13:11

18 የመጨረሻውን ዘመን አስመልክቶ የተነገሩት ትንቢቶች፣ አንዳንዶች ለመንፈሳዊ ነገሮች ትኩረት እንዲሰጡ ሊያነሳሷቸው ይችላሉ። ሌሎች ደግሞ ከኢኮኖሚ ውድቀት፣ ከኑክሌር ስጋት፣ ከወንጀል መበራከት ወይም ከምድር መበላሸት ጋር በተያያዘ ሰብዓዊ መንግሥታት መፍትሔ ማምጣት አለመቻላቸውን ሲመለከቱ የሰው ዘር ከሌላ አቅጣጫ እርዳታ እንደሚያስፈልገው ይገነዘባሉ። አንዳንዶች ደግሞ በቤታቸው ውስጥ የሚከሰቱ ነገሮች ለምሳሌ የጤና ችግር፣ የትዳር መፍረስ ወይም የሚወዱትን ሰው በሞት ማጣት ለመንፈሳዊ ጉዳዮች ትኩረት እንዲሰጡ ያደርጓቸዋል። በአገልግሎት ስንካፈል እንዲህ ዓይነት ሰዎችን ለመርዳት አጋጣሚ እናገኛለን።

የጥድፊያ ስሜት ለበለጠ ሥራ ያነሳሳል

19, 20. ብዙ ክርስቲያኖች የጥድፊያ ስሜት ያላቸው መሆኑ በአኗኗራቸው ላይ ምን ለውጥ እንዲያደርጉ አነሳስቷቸዋል?

19 ብዙ ክርስቲያኖች የጥድፊያ ስሜት ያላቸው መሆኑ በአገልግሎት የሚያደርጉትን ተሳትፎ እንዲጨምሩ አነሳስቷቸዋል። ለምሳሌ ያህል፣ የኢኳዶር ተወላጅ የሆኑ አንድ ባልና ሚስት “ጤናማ ዓይን ይኑራችሁ” በሚል ጭብጥ በ2006 በተካሄደው የልዩ ስብሰባ ቀን ፕሮግራም ላይ ከተገኙ በኋላ ኑሯቸውን ቀላል ለማድረግ ወሰኑ። ከዚያም የማያስፈልጓቸውን ዕቃዎች በዝርዝር ከጻፉ በኋላ በሦስት ወር ጊዜ ውስጥ ባለ ሦስት መኝታ ክፍል አፓርታማቸውን በመልቀቅ አንድ መኝታ ክፍል ወዳለው ቤት የገቡ ከመሆኑም በላይ አንዳንድ ዕቃዎቻቸውን ሸጡ፤ እንዲሁም ያለባቸውን ዕዳ ከፈሉ። ወዲያው ረዳት አቅኚ ሆኑ፤ ከዚያም የወረዳ የበላይ ተመልካቻቸው ያቀረበላቸውን ሐሳብ በመቀበል እርዳታ ይበልጥ ወደሚያስፈልግበት ጉባኤ ተዘዋውረው ማገልገል ጀመሩ።

20 በሰሜን አሜሪካ የሚኖር አንድ ወንድም እንዲህ በማለት ጽፏል፦ “እኔና ባለቤቴ በ2006 በተደረገ አንድ ትልቅ ስብሰባ ላይ ስንገኝ ከተጠመቅን 30 ዓመታት ሆኖን ነበር። በመኪናችን ወደ ቤት እየተመለስን ሳለ ኑሮን ቀላል ስለማድረግ የተሰጠውን ትምህርት እንዴት በሕይወታችን ተግባራዊ ማድረግ እንደምንችል ተወያየን። (ማቴ. 6:19-22) ሦስት መኖሪያ ቤት ያለን ከመሆኑም በላይ መሬት፣ የቅንጦት መኪናዎች፣ አንድ ጀልባና ተንቀሳቃሽ ቤት ነበረን። እስከ አሁን ጊዜያችንን በከንቱ እንዳባከንን ስለተሰማን ወደ ሙሉ ጊዜ አገልግሎትን ለመግባት ወሰንን። ከዚያም 2008 ላይ ልክ እንደ ልጃችን አቅኚ ሆንን። ከወንድሞች ጋር ይበልጥ ተቀራርበን የመሥራት መብት በማግኘታችን በጣም ተደስተናል! እንዲሁም እርዳታ ይበልጥ ወደሚያስፈልግበት አካባቢ በመሄድ ማገልገል ችለናል። በተጨማሪም ይሖዋን በማገልገል ሰፋ ያለ ጊዜ ማሳለፋችን ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ወደ እሱ እንድንጠጋ አድርጎናል። ሰዎች በአምላክ ቃል ውስጥ የሚገኘውን እውነት ሲሰሙና ሲረዱ ፊታቸው ላይ የሚነበበውን የደስታ ስሜት መመልከት ደግሞ በጣም የሚክስ ነው።”

21. ለበለጠ ሥራ የሚያነሳሳን የትኛውን እውቀት ማግኘታችን ነው?

21 በቅርቡ ይህ ክፉ ሥርዓት ምን እንደሚደርስበት ማለትም ‘ፈሪሃ አምላክ የሌላቸው ሰዎች በሚጠፉበት የፍርድ ቀን’ እንደሚደመሰስ እናውቃለን። (2 ጴጥ. 3:7) ስለ አምላክ ቃል ያገኘነው እውቀት ስለ መጪው ታላቅ መከራና ከዚያ በኋላ ስለሚመጣው አዲስ ዓለም በቅንዓት እንድናውጅ ያነሳሳናል። በመሆኑም ሰዎች እውነተኛ ተስፋ እንዲያገኙ ለመርዳት የጥድፊያ ስሜታችን እንዳይጠፋ እንጠንቀቅ። በዚህ አጣዳፊ ሥራ ሙሉ ተሳትፎ በማድረግ ለአምላክና ለሰዎች እውነተኛ ፍቅር እንዳለን እናሳይ።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]