በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

አምላክን በመታዘዝ በመሐላ ከገባው ቃል ተጠቃሚ ሁኑ

አምላክን በመታዘዝ በመሐላ ከገባው ቃል ተጠቃሚ ሁኑ

“አምላክ . . . ሊምልበት የሚችል ከእሱ የሚበልጥ ሌላ ማንም ስለሌለ በራሱ ማለ።”—ዕብ. 6:13

1. የይሖዋ ቃል ኃጢአተኛ የሆኑት የሰው ልጆች ከሚገቡት ቃል የሚለየው እንዴት ነው?

ይሖዋ “የእውነት አምላክ” ነው። (መዝ 31:5) ኃጢአተኛ የሆኑ የሰው ልጆች ሁልጊዜ እምነት ሊጣልባቸው አይችልም፤ በአንጻሩ ግን ‘አምላክ ሊዋሽ አይችልም።’ (ዕብ. 6:18፤ ዘኍልቍ 23:19ን አንብብ።) ለሰው ልጆች ጥቅም ሲል የሚያወጣቸው ዓላማዎች ምንጊዜም ይፈጸማሉ። ለምሳሌ አምላክ የፍጥረት ሥራዎቹን ባከናወነበት በእያንዳንዱ ወቅት መጀመሪያ ላይ፣ አደርገዋለሁ ብሎ የተናገረው ነገር በሙሉ ‘እንዳለው ሆኗል።’ በመሆኑም በስድስተኛው የፍጥረት ቀን ማብቂያ ላይ አምላክ “ያደረገውን ሁሉ አየ፤ እነሆም፣ እጅግ መልካም ነበረ።”—ዘፍ. 1:6, 7, 30, 31

2. የአምላክ የእረፍት ቀን ምንድን ነው? ቀኑን ‘የቀደሰው’ ለምንድን ነው?

2 ይሖዋ አምላክ የፍጥረት ሥራዎቹን መለስ ብሎ ካየ በኋላ ሰባተኛው ቀን መጀመሩን አስታውቋል፤ ይህ ቀን የ24 ሰዓት ርዝማኔ ያለውን ቀን ሳይሆን አምላክ በምድር ላይ ተጨማሪ የፍጥረት ሥራዎች ማከናወኑን አቁሞ ያረፈበትን ረጅም ዘመን ያመለክታል። (ዘፍ. 2:2) የአምላክ የእረፍት ቀን እስካሁን ድረስ አላበቃም። (ዕብ. 4:9, 10) መጽሐፍ ቅዱስ ይህ ቀን የጀመረበትን ትክክለኛውን ጊዜ አይገልጽም። ይህ ቀን የጀመረው ከ6,000 ዓመት ገደማ በፊት የአዳም ሚስት ሔዋን ከተፈጠረች ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ነበር። ከፊታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የሺህ ዓመት ግዛት ይጠብቀናል፤ በዚያ ወቅት፣ አምላክ ምድርን ሲፈጥር ለዘላለም ገነት ሆና ፍጹም በሆኑ የሰው ልጆች እንድትሞላ የነበረው ዓላማ ዳር ይደርሳል። (ዘፍ. 1:27, 28፤ ራእይ 20:6) ወደፊት ይህን አስደሳች ሕይወት እንደምታገኝ እርግጠኛ መሆን ትችላለህ! ምክንያቱም አምላክ ‘ሰባተኛውን ቀን ባርኮታል፤ እንዲሁም ቀድሶታል።’ ይህም ያልታሰቡ ችግሮች ቢከሰቱ እንኳ የአምላክ ዓላማ በእረፍት ቀኑ ማብቂያ ላይ በእርግጥ እንደሚፈጸም ዋስትና ይሆናል።—ዘፍ. 2:3

3. (ሀ) የአምላክ የእረፍት ቀን ከጀመረ በኋላ ምን ዓመፅ ተከሰተ? (ለ) ይሖዋ ዓመፁን ለማኮላሸት ያለውን ዓላማ የገለጸው እንዴት ነው?

3 የአምላክ የእረፍት ቀን ከጀመረ በኋላ ግን ችግር ተከሰተ። በሰማይ መልአክ የነበረው ሰይጣን፣ ሌሎች እሱን እንዲያመልኩት ስለፈለገ የአምላክን ቦታ ተቀናቀነ። የመጀመሪያውን ውሸት በመናገር ሔዋን በይሖዋ ላይ እንድታምፅ አታለላት። (1 ጢሞ. 2:14) ሔዋን ደግሞ ባሏ በዓመፁ እንዲተባበራት አደረገች። (ዘፍ. 3:1-6) የአምላክ እውነተኝነት ጥያቄ ላይ በወደቀበትና በአጽናፈ ዓለም ታሪክ ውስጥ እጅግ አስከፊ የሆነ ነገር በተፈጸመበት በዚያ ወቅት እንኳ ይሖዋ ዓላማው መፈጸሙ እንደማይቀር በመሐላ ማረጋገጥ አላስፈለገውም። ከዚህ ይልቅ እሱ በወሰነው ጊዜ ግልጽ የሚሆን ትንቢት የተናገረ ሲሆን ዓመፁ እንዴት እንደሚኮላሽ በአጭሩ እንዲህ ሲል ገልጿል፦ “በአንተና [በሰይጣንና] በሴቲቱ፣ በዘርህና በዘሯ መካከል፣ ጠላትነትን አደርጋለሁ፤ እርሱ [ተስፋ የተደረገበት ዘር] ራስህን ይቀጠቅጣል፤ አንተም ተረከዙን ትቀጠቅጣለህ።”—ዘፍ. 3:15፤ ራእይ 12:9

መሐላ—ጠቃሚ የሆነ ሕጋዊ መሣሪያ

4, 5. አብርሃም በተለያዩ ጊዜያት በየትኛው ሕጋዊ መሣሪያ ተጠቅሟል?

4 የሰው ዘር ታሪክ በጀመረበት በዚያ ወቅት የአንድን ነገር እውነተኝነት ለማረጋገጥ መማል አስፈላጊ የነበረ አይመስልም። አምላክን የሚወዱና እሱን ለመምሰል የሚጥሩ ፍጹም ፍጥረታት መሐላ መግባት አያስፈልጋቸውም፤ ምንጊዜም እውነት የሚናገሩ ከመሆኑም ሌላ እርስ በርሳቸው ሙሉ በሙሉ ይተማመናሉ። ይሁን እንጂ የሰው ልጅ ኃጢአት ሲሠራና ፍጽምና ሲጎድለው ሁኔታዎች ተለወጡ። ውሎ አድሮ መዋሸትና ማታለል በሰው ልጆች መካከል የተለመዱ ነገሮች እየሆኑ ሲሄዱ ክብደት ያላቸውን ነገሮች እውነተኝነት በመሐላ ማረጋገጥ አስፈላጊ እየሆነ መጣ።

5 መሐላ መግባት ሕጋዊ መሣሪያ ሆኖ አገልግሏል፤ አብርሃም ቢያንስ በሦስት የተለያዩ ጊዜያት በመሐላ ያጸናቸው ነገሮች ነበሩ። (ዘፍ. 21:22-24፤ 24:2-4, 9) ለምሳሌ ያህል፣ አብርሃም የኤላምን ንጉሥና ተባባሪዎቹን ድል አድርጎ ሲመለስ መሐላ ገብቶ ነበር። የሳሌምና የሰዶም ነገሥታት አብርሃም ሲመለስ ወጥተው ተቀበሉት። የሳሌም ንጉሥ መልከጼዴቅ “የልዑል እግዚአብሔር ካህን” በመሆንም ያገለግል ነበር። በመሆኑም አብርሃምን ባርኮታል፤ ደግሞም አብርሃምን በጠላቶቹ ላይ ድል ስላቀዳጀው አምላክን አወድሷል። (ዘፍ. 14:17-20) ከዚያም የሰዶም ንጉሥ፣ አብርሃም ከወራሪው ሠራዊት ሕዝቡን ስላስጣለለት ለእሱ ወሮታ መክፈል በፈለገ ጊዜ አብርሃም እጁን አንስቶ እንዲህ ሲል ምሏል፦ “ሰማይንና ምድርን ወደ ፈጠረ ወደ እግዚአብሔር፣ ወደ ልዑል አምላክ እጆቼን አንሥቻለሁ፤ ‘አብራምን አበለጸግሁት’ እንዳትል፣ ብጣሽ ክርም ሆነ የጫማ ማሰሪያ እንኳ ከአንተ አንዳች አልፈልግም።”—ዘፍ. 14:21-23

ይሖዋ ለአብርሃም በመሐላ የገባው ቃል

6. (ሀ) አብርሃም ለእኛ ምን ምሳሌ ትቷል? (ለ) አብርሃም ታዛዥ መሆኑ እኛን የሚጠቅመን እንዴት ነው?

6 ይሖዋ አምላክም ኃጢአተኞች ለሆኑት የሰው ልጆች ጥቅም ሲል “በሕያውነቴ እምላለሁ! ይላል ልዑል እግዚአብሔር” እንደሚለው ያሉ አገላለጾችን በመጠቀም መሐላ ገብቷል። (ሕዝ. 17:16) መጽሐፍ ቅዱስ፣ ይሖዋ አምላክ ከ40 በላይ በሚሆኑ የተለያዩ ጊዜያት በመሐላ ቃል እንደገባ ይገልጻል። በዚህ ረገድ በሰፊው የሚታወቀው ምሳሌ አምላክ ከአብርሃም ጋር በነበረው ግንኙነት የገባው መሐላ ሳይሆን አይቀርም። በርካታ ዓመታት ባስቆጠረ ጊዜ ውስጥ ይሖዋ ለአብርሃም የተለያዩ የቃል ኪዳን ተስፋዎች የሰጠው ሲሆን ተስፋዎቹ ጠቅለል ተደርገው ሲታዩ አስቀድሞ የተነገረለት ዘር በልጁ በይስሐቅ በኩል ከአብርሃም እንደሚገኝ ይጠቁማሉ። (ዘፍ. 12:1-3, 7፤ 13:14-17፤ 15:5, 18፤ 21:12) ይሁንና ይሖዋ፣ አብርሃም የሚወደውን ልጁን እንዲሠዋ ባዘዘው ጊዜ በአብርሃም ፊት ከባድ ፈተና ተደቀነ። አብርሃም ምንም ሳያመነታ ታዘዘ፤ የአምላክ መልአክ ባያስቆመው ኖሮ ይስሐቅን መሥዋዕት ለማድረግ ምንም አልቀረውም ነበር። በዚህ ጊዜ አምላክ የሚከተለውን መሐላ ገባለት፦ “በራሴ ማልሁ . . . አንዱን ልጅህን ለእኔ ለመስጠት አልሳሳህምና፣ በእርግጥ እባርክሃለሁ፤ ዘርህን እንደ ሰማይ ከዋክብት፣ እንደ ባሕር ዳር አሸዋም አበዛዋለሁ። ዘሮችህም የጠላቶቻቸውን ደጆች ይወርሳሉ፤ ቃሌን ስለ ሰማህ የምድር ሕዝቦች ሁሉ በዘርህ ይባረካሉ።”—ዘፍ. 22:1-3, 9-12, 15-18

7, 8. (ሀ) አምላክ ለአብርሃም በመሐላ ቃል የገባው ለምንድን ነው? (ለ) የኢየሱስ “ሌሎች በጎች” አምላክ በመሐላ ከገባው ቃል ጥቅም የሚያገኙት እንዴት ነው?

7 አምላክ፣ የገባው ቃል እንደሚፈጸም ለአብርሃም የማለለት ለምንድን ነው? አስቀድሞ የተነገረለት “ዘር” ሁለተኛ ክፍል የሚሆኑትንና ከክርስቶስ ጋር አብረው የሚገዙትን ለማበረታታትና እምነታቸውን ለማጠናከር ሲል ነው። (ዕብራውያን 6:13-18ን አንብብ፤ ገላ. 3:29) ሐዋርያው ጳውሎስ እንደገለጸው ይሖዋ “ተስፋውን በመሐላ አጸናው፤ ይህንም ያደረገው . . . አምላክ ሊዋሽ በማይችልባቸው ፈጽሞ በማይለወጡት በእነዚህ ሁለት ነገሮች [በገባው ቃልና በመሐላው] አማካኝነት በፊታችን ያለውን ተስፋ አጥብቀን እንድንይዝ የሚረዳንን ከፍተኛ ማበረታቻ እንድናገኝ ነው።”

በቅርቡ አብርሃም፣ ይሖዋ የገባቸው ቃሎች ሲፈጸሙ ይመለከታል

8 አምላክ ለአብርሃም በመሐላ ከገባው ቃል ተጠቃሚ የሚሆኑት ቅቡዓን ክርስቲያኖች ብቻ አይደሉም። ይሖዋ በአብርሃም “ዘር” አማካኝነት ‘የምድር ሕዝቦች ሁሉ እንደሚባረኩ’ ምሏል። (ዘፍ. 22:18) ይህን በረከት ከሚቋደሱት መካከል ገነት በምትሆነው ምድር ላይ ለዘላለም የመኖር ተስፋ ያላቸው ታዛዥ የሆኑ የክርስቶስ “ሌሎች በጎች” ይገኙበታል። (ዮሐ. 10:16) ተስፋችሁ ሰማያዊም ሆነ ምድራዊ ምንጊዜም ለአምላክ ታዛዥ ሆናችሁ በመኖር ተስፋችሁን ‘አጥብቃችሁ ያዙ።’—ዕብራውያን 6:11, 12ን አንብብ።

አምላክ የገባቸው ተዛማጅነት ያላቸው መሐላዎች

9. የአብርሃም ዘሮች የግብፃውያን ባሪያዎች በነበሩበት ወቅት አምላክ የገባው መሐላ ምን ነበር?

9 ከበርካታ መቶ ዓመታት በኋላ ይሖዋ በወቅቱ የግብፃውያን ባሪያዎች የነበሩትን የአብርሃምን ዘሮች እንዲያናግር ሙሴን በላከው ጊዜ ቀደም ሲል ከገባቸው ቃሎች ጋር በተያያዘ በድጋሚ መሐላ ገብቷል። (ዘፀ. 6:6-8) አምላክ ያንን ወቅት በተመለከተ እንዲህ ብሏል፦ “እስራኤልን በመረጥሁበት ቀን፣ . . . እጄን አንሥቼ . . . ከግብፅ አውጥቻቸው ከምድር ሁሉ ይልቅ ውብ ወደ ሆነችው፣ ማርና ወተት ወደምታፈስሰው፣ ወዳዘጋጀሁላቸውም ምድር እንደማስገባቸው ማልሁላቸው።”ሕዝ. 20:5, 6

10. አምላክ እስራኤላውያንን ከግብፅ ነፃ ካወጣቸው በኋላ ምን ቃል ገባላቸው?

10 እስራኤላውያን ከግብፅ ነፃ ከወጡ በኋላ ደግሞ ይሖዋ እንዲህ ሲል ሌላ መሐላ ገባላቸው፦ “በፍጹም ብትታዘዙኝና ቃል ኪዳኔን ብትጠብቁ እነሆ ከአሕዛብ ሁሉ እናንተ የተወደደ ርስቴ ትሆናላችሁ፤ ምንም እንኳ ምድር ሁሉ የእኔ ብትሆንም፣ እናንተ ለእኔ የመንግሥት ካህናት የተቀደሰ ሕዝብ ትሆናላችሁ።” (ዘፀ. 19:5, 6) በዚህ መንገድ አምላክ ለእስራኤላውያን በዓይነቱ ልዩ የሆነ መብት ሰጣቸው! የዚህ ብሔር አባል የሆኑ ግለሰቦች ታዛዥ ከሆኑ አምላክ ወደፊት የተቀረውን የሰው ዘር ለመባረክ የሚጠቀምባቸው የመንግሥት ካህናት የመሆን ተስፋ ይጠብቃቸው ነበር። ከጊዜ በኋላ ይሖዋ በዚያን ወቅት ለእስራኤላውያን ያደረገላቸውን ነገር በማመልከት እንዲህ ብሏል፦ “ማልሁልሽ፤ ከአንቺም ጋር ቃል ኪዳን ተጋባሁ።”—ሕዝ. 16:8

11. እስራኤላውያን፣ አምላክ የተመረጡ ሕዝቦቹ ሆነው ከእሱ ጋር በቃል ኪዳን እንዲተሳሰሩ ላቀረበላቸው ግብዣ ምን ምላሽ ሰጡ?

11 በዚያን ጊዜ ይሖዋ፣ እስራኤላውያን እንታዘዛለን ብለው እንዲምሉም ሆነ ይህን ውድ ዝምድና እንዲመሠርቱ አላስገደዳቸውም። ከዚህ ይልቅ በገዛ ፈቃዳቸው “እግዚአብሔር ያለውን ሁሉ እናደርጋለን” ብለዋል። (ዘፀ. 19:8) ይህ ከሆነ ከሦስት ቀን በኋላ ይሖዋ አምላክ ከመረጠው ብሔር ምን እንደሚጠብቅ ለእስራኤላውያን አሳወቀ። በመጀመሪያ አሥሩን ትእዛዛት ሰሙ፤ ከዚያም ሙሴ ተጨማሪ ትእዛዛት ሰጣቸው፤ ይህም ከ⁠ዘፀአት 20:22 እስከ ዘፀአት 23:33 ላይ ተመዝግቦ ይገኛል። እስራኤላውያን ምን ምላሽ ሰጡ? ሕዝቡ ሁሉ “በአንድ ድምፅ ሆነው፣ ‘እግዚአብሔር ያለውን ሁሉ እናደርጋለን’ አሉ።” (ዘፀ 24:3) ከዚያም ሙሴ ሕጎቹን ‘የኪዳኑ መጽሐፍ’ ላይ ጻፈ፤ ደግሞም ሕዝቡ በሙሉ በድጋሚ ሕጎቹን መስማት እንዲችሉ ጮክ ብሎ አነበበላቸው። ከዚህ በኋላ ለሦስተኛ ጊዜ ሕዝቡ “እግዚአብሔር ያለውን ሁሉ እናደርጋለን፤ እንታዘዛለን” በማለት ማሉ።—ዘፀ 24:4, 7, 8

12. ይሖዋና የመረጣቸው ሕዝቡ በመካከላቸው ለተመሠረተው ቃል ኪዳን የሰጡት ምላሽ ምን ነበር?

12 ይሖዋ ወዲያውኑ ለአምልኮ የሚያገለግል ድንኳንና ኃጢአተኛ የሆኑት የሰው ልጆች ወደ እሱ መቅረብ የሚችሉበትን የክህነት ሥርዓት በማዘጋጀት ከሕጉ ቃል ኪዳን ጋር በተያያዘ የበኩሉን ድርሻ መወጣት ጀመረ። በአንጻሩ ግን እስራኤላውያን ለአምላክ የገቡትን ቃል ወዲያው በመርሳት ‘የእስራኤልን ቅዱስ አስቈጡት።’ (መዝ 78:41) ለምሳሌ ያህል፣ ሙሴ በሲና ተራራ ላይ ተጨማሪ መመሪያዎችን በመቀበሉ ሥራ ተጠምዶ እያለ እስራኤላውያን ሙሴ እንደተዋቸው በማሰብ ትዕግሥታቸው የተሟጠጠ ከመሆኑም በላይ በአምላክ ላይ እምነት አጡ። በመሆኑም የወርቅ ጥጃ ሠርተው ለሕዝቡ “እስራኤል ሆይ፤ ከግብፅ ያወጡህ አማልክት እነዚህ ናቸው” አሏቸው። (ዘፀ 32:1, 4) ከዚያም ‘የእግዚአብሔር በዓል’ ብለው የጠሩትን ክብረ በዓል አዘጋጅተው በሰው እጅ ለተሠራው ምስል ሰገዱ፤ እንዲሁም መሥዋዕት አቀረቡ። ይሖዋ ይህን ሲመለከት ሙሴን “ካዘዝኋቸው ፈቀቅ ለማለት ፈጣኖች ሆኑ” አለው። (ዘፀ 32:5, 6, 8) የሚያሳዝነው ከዚያን ጊዜ አንስቶ እስራኤላውያን ለአምላክ የገቧቸውን መሐላዎች በተደጋጋሚ አፍርሰዋል።—ዘኍ 30:2

ሁለት ተጨማሪ መሐላዎች

13. አምላክ ለንጉሥ ዳዊት ምን ብሎ ማለለት? ይህስ አስቀድሞ ከተነገረለት ዘር ጋር ምን ዝምድና አለው?

13 በንጉሥ ዳዊት የግዛት ዘመን ይሖዋ ለሚታዘዙት ሰዎች ሁሉ ጥቅም ሲል ሁለት ተጨማሪ መሐላዎች ገባ። በመጀመሪያ ዙፋኑ ለዘላለም እንደሚጸና ለዳዊት ማለለት። (መዝ 89:35, 36፤ 132:11, 12) በመሆኑም አስቀድሞ የተነገረለት ዘር “የዳዊት ልጅ” ተብሎ ይጠራል ማለት ነው። (ማቴ 1:1፤ 21:9) ዳዊት ትሕትና በሚንጸባረቅበት ሁኔታ፣ ወደፊት በእሱ የትውልድ ሐረግ የሚመጣውን ዘር “ጌታዬ” በማለት ጠርቶታል፤ እንዲህ ሊል የቻለው ክርስቶስ እጅግ የላቀ ቦታ ስለሚኖረው ነው።—ማቴ 22:42-44

14. ይሖዋ አስቀድሞ የተነገረለትን ዘር አስመልክቶ በመሐላ የገባው ቃል ምንድን ነው? እኛስ ከዚህ ጥቅም የምናገኘው እንዴት ነው?

14 በሁለተኛ ደረጃ፣ ዳዊት በዓይነቱ ልዩ የሆነው ይህ ንጉሥ ለሰው ልጆች ሊቀ ካህናትም ሆኖ እንደሚያገለግል ትንቢት እንዲናገር ይሖዋ በመንፈሱ መርቶታል። በእስራኤል ንግሥናና ክህነት ምንም የማይገናኙ ነገሮች ነበሩ። ካህናቱ የሌዊ ነገድ ዝርያዎች ሲሆኑ ነገሥታቱ ደግሞ ከይሁዳ ነገድ ነበሩ። ይሁንና ዳዊት ወደፊት ታላቅ ክብር የሚጎናጸፈውን የዙፋኑን ወራሽ በተመለከተ እንዲህ ሲል ትንቢት ተናግሯል፦ “እግዚአብሔር ጌታዬን፣ ‘ጠላቶችህን ለእግርህ መርገጫ፣ እስከማደርግልህ ድረስ፣ በቀኜ ተቀመጥ’ አለው። ‘እንደ መልከ ጼዴቅ ሥርዐት፤ አንተ ለዘላለም ካህን ነህ’ ብሎ፣ እግዚአብሔር ምሎአል፤ እርሱ ሐሳቡን አይለውጥም።” (መዝ 110:1, 4) በዚህ ትንቢት ፍጻሜ መሠረት አስቀድሞ የተነገረለት ዘር የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ በአሁኑ ጊዜ በሰማይ ሆኖ እየገዛ ነው። በተጨማሪም ንስሐ የገቡ ሰዎች ከአምላክ ጋር ጥሩ ዝምድና እንዲመሠርቱ በመርዳት የሰው ልጆች ሊቀ ካህናት ሆኖ እያገለገለ ነው።—ዕብራውያን 7:21, 25, 26ን አንብብ።

አዲሱ የአምላክ እስራኤል

15, 16. (ሀ) መጽሐፍ ቅዱስ ስለ የትኞቹ ሁለት የእስራኤል ብሔሮች ይናገራል? በዛሬው ጊዜ የአምላክን በረከት ያገኘው የትኛው ብሔር ነው? (ለ) ኢየሱስ መሐላን አስመልክቶ ለተከታዮቹ ምን ትእዛዝ ሰጥቷል?

15 የእስራኤል ብሔር ኢየሱስ ክርስቶስን ሳይቀበል በመቅረቱ በመጨረሻ በአምላክ ፊት የነበረውን ልዩ ቦታና “የመንግሥት ካህናት” የመሆን ተስፋ አጣ። ኢየሱስ ለአይሁድ መሪዎች “የአምላክ መንግሥት ከእናንተ ተወስዶ ፍሬውን ለሚያፈራ ሕዝብ ይሰጣል” ሲል ተናግሯል። (ማቴ. 21:43) አዲሱ ብሔር የተወለደው በ33 ዓ.ም. በጴንጤቆስጤ ዕለት በኢየሩሳሌም ተሰብስበው በነበሩት 120 የሚያህሉ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ላይ የአምላክ መንፈስ በፈሰሰ ጊዜ ነበር። እነዚህ የኢየሱስ ተከታዮች ‘የአምላክ እስራኤል’ ተብለው የተጠሩ ሲሆን ብዙም ሳይቆይ፣ በዚያን ጊዜ በነበረው ዓለም ውስጥ ከነበሩት ብሔራት ሁሉ የተውጣጡ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ አባላትን ያቀፉ ለመሆን በቅተዋል።—ገላ. 6:16

16 ከሥጋዊ እስራኤላውያን በተለየ ሁኔታ አዲሱ የአምላክ መንፈሳዊ ብሔር ዘወትር ለአምላክ በመታዘዝ መልካም ፍሬ ማፍራቱን ቀጥሏል። የዚህ ብሔር አባላት ከሚጠብቋቸው ትእዛዛት መካከል አንዱ ከቃለ መሐላ ጋር የተያያዘ ነው። ኢየሱስ ምድር ላይ በነበረበት ወቅት ሰዎች በውሸት በመማል ወይም ለማይረባ ነገር መሐላ በመፈጸም መሐላን አላግባብ ይጠቀሙበት ነበር። (ማቴ. 23:16-22) ኢየሱስ ተከታዮቹን እንዲህ ሲል አስተምሯል፦ “ፈጽሞ አትማሉ። . . . ቃላችሁ ‘አዎ’ ከሆነ አዎ ይሁን፣ ‘አይደለም’ ከሆነ አይደለም ይሁን፤ ከዚህ ውጭ የሆነ ግን ከክፉው ነው።”—ማቴ. 5:34, 37

ይሖዋ የገባው ቃል ሁሉ ይፈጸማል

17. በሚቀጥለው የጥናት ርዕስ ላይ የትኞቹ ጥያቄዎች ይብራራሉ?

17 እንዲህ ሲባል ታዲያ መማል ሁልጊዜ ስህተት ነው ማለት ነው? ደግሞስ “አዎ” ያልነው ነገር አዎ እንዲሆን ምን ማድረግ ይኖርብናል? እነዚህ ጥያቄዎች በሚቀጥለው የጥናት ርዕስ ላይ ይብራራሉ። በአምላክ ቃል ላይ አዘውትረን ማሰላሰላችን ይሖዋን ምንጊዜም ለመታዘዝ የሚያነሳሳን ይሁን! እኛ እንዲህ ካደረግን ይሖዋ በመሃላ ከገባው ቃል ጋር በሚስማማ መንገድ ለዘላለም ይባርከናል።