በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ታስታውሳለህ?

ታስታውሳለህ?

በቅርቡ የወጡትን የመጠበቂያ ግንብ እትሞች በደንብ አንብበሃቸዋል? እስቲ የሚከተሉትን ጥያቄዎች ለመመለስ ሞክር፦

ክርስቲያኖች መጸለይ ያለባቸው ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው?

አይደለም። ኢየሱስ ራሱ ወደ ይሖዋ እንድንጸልይ ያስተማረን ሲሆን ለአባቱ በመጸለይ ረገድም ምሳሌ ትቶልናል። (ማቴ. 6:6-9፤ ዮሐ. 11:41፤ 16:23) በመሆኑም የጥንቶቹ ተከታዮቹ ይጸልዩ የነበረው ወደ ኢየሱስ ሳይሆን ወደ አምላክ ነበር። (ሥራ 4:24, 30፤ ቆላ. 1:3)—1/1 ገጽ 14

ለዓመታዊው የኢየሱስ ሞት መታሰቢያ በዓል መዘጋጀት የምንችለው እንዴት ነው?

አንደኛ ከዚህ በዓል ጋር ተያይዞ የሚወጣውን የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ ማንበብ እንችላለን። በተጨማሪም በዚህ ወቅት የአገልግሎት እንቅስቃሴያችንን ለማሳደግ ጥረት ማድረግ እንችላለን። ከዚህም ሌላ አምላክ የሰጠንን ተስፋ በጸሎት ልናስብበት ይገባል።—1/15 ከገጽ 14-16

ግራ የሚያጋባ ሕልማቸውን ለዮሴፍ የነገሩት ሁለት ግብፃውያን እስረኞች መጨረሻቸው ምን ሆነ?

ዮሴፍ ለፈርዖን መጠጥ አሳላፊ ወደ ቀድሞ ሥልጣኑ እንደሚመለስ ነገረው። ዳቦ ጋጋሪው ያየው ሕልም ደግሞ ፈርዖን እንደሚያስገድለውና በእንጨት ላይ እንደሚሰቅለው ያመለክታል። ዮሴፍ ለሁለቱም ሰዎች የነገራቸው የሕልም ፍቺ ተፈጽሟል። (ዘፍ. 40:1-22)—2/1 ከገጽ 12-14

በጃፓን ያሉ ወንድሞች ምን ያልተጠበቀ ስጦታ አገኙ?

ከአዲስ ዓለም ትርጉም የተወሰደ የማቴዎስ ወንጌልን የያዘ ጽሑፍ አግኝተዋል። ወንድሞች ጽሑፉን በአገልግሎት ላይ እያበረከቱት ሲሆን ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር ትውውቅ የሌላቸው ብዙ ሰዎች ይህን ጽሑፍ ወስደዋል።—2/15 ገጽ 3

በመጀመሪያው መቶ ዘመን ምሥራቹ እንዲስፋፋ እገዛ ያደረጉት ሁኔታዎች ምንድን ናቸው?

ፓክስ ሮማና በሚባለው የተረጋጋ ወቅት ብዙ ግጭቶች አልነበሩም። የጥንቶቹ ደቀ መዛሙርት በወቅቱ የነበሩትን ጥሩ መንገዶች ለጉዞ ይጠቀሙ ነበር። በርካታ ሰዎች ግሪክኛ መቻላቸው ምሥራቹ እንዲስፋፋ አስተዋጽኦ አድርጓል፤ እንዲሁም በመላው የሮም ግዛት ውስጥ ለሚኖሩ አይሁዳውያን ጭምር ለመስበክ አስችሏል። በተጨማሪም ደቀ መዛሙርቱ ለምሥራቹ ለመሟገት የሮምን ሕግ መጠቀም ይችሉ ነበር።—2/15 ከገጽ 20-23

እውነተኛ ክርስቲያኖች በዓለ ትንሣኤን የማያከብሩት ለምንድን ነው?

ኢየሱስ ተከታዮቹ እንዲያከብሩ ያዘዘው ትንሣኤውን ሳይሆን ሞቱን ነው። (ሉቃስ 22:19, 20)—3/1 ገጽ 8

ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በጽሑፎቻችን ላይ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስለሚገኙ ጥላ የሚሆኑ ነገሮችና ስለ እውነተኛዎቹ ነገሮች ማብራሪያ መስጠት የቀረው ለምንድን ነው?

መጽሐፍ ቅዱስ አንዳንድ ግለሰቦች ለላቀ ነገር ጥላ እንደሆኑ ይናገራል። በገላትያ 4:21-31 ላይ የሚገኘው ዘገባ ለዚህ ምሳሌ ይሆነናል። ከዚህ ውጪ ግን አንድ ግለሰብ ወይም ዘገባ ለሌላ ነገር ጥላ እንደሆነ ከመግለጽ መቆጠብ ይኖርብናል። ሆኖም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከሚገኙት ግለሰቦችና ክንውኖች ትምህርት ማግኘት እንችላለን። (ሮም 15:4)—3/15 ከገጽ 17-18

በግብፅ ባለ ጥንታዊ የቆሻሻ ክምር መሃል የተገኘ የፓፒረስ ቁራጭ ትኩረታችንን የሚስበው ለምንድን ነው?

ባለፈው መቶ ዓመት ከተገኙት ጥንታዊ ቁርጥራጮች መካከል ከዮሐንስ ወንጌል የተወሰነውን ክፍል የያዘው ይገኝበታል። ይህ ጽሑፍ የተዘጋጀው ዮሐንስ ወንጌሉን ከጻፈ ከጥቂት አሥርተ ዓመታት በኋላ ሊሆን ይችላል፤ ይዘቱ የዮሐንስ ወንጌል በትክክል እንደተላለፈልንና መጽሐፍ ቅዱስ እምነት የሚጣልበት እንደሆነ ያረጋግጣል።—4/1 ከገጽ 10-11

ንስሐ የማይገባ ኃጢአተኛ መወገዱ ፍቅራዊ ዝግጅት ነው ሊባል የሚችለው ለምንድን ነው?

መጽሐፍ ቅዱስ ንስሐ የማይገባ ኃጢአተኛ ከባድ እርምጃ እንደሚወሰድበት ይኸውም እንደሚወገድ ይገልጻል፤ ይህ እርምጃ የሚያስገኛቸው ጥቅሞች አሉት። (1 ቆሮ. 5:11-13) የአምላክን ስም ያስከብራል፣ የጉባኤው ንጽሕና እንዲጠበቅ ያደርጋል እንዲሁም ኃጢአት የሠራው ሰው ወደ ልቡ እንዲመለስ ሊረዳው ይችላል።—4/15 ከገጽ 29-30