በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ወደር የማይገኝለት አባት

ወደር የማይገኝለት አባት

ወደ አምላክ ቅረብ

ወደር የማይገኝለት አባት

ማቴዎስ 3:16, 17

“አባት።” አንዳንድ ቃላት በሰው ልብ ውስጥ ልዩ ስሜት ይፈጥራሉ። ለልጆቹ ልባዊ ፍቅር ያለው አባት ልጆቹ በጥሩ ሁኔታ እንዲያድጉ ይረዳቸዋል። መጽሐፍ ቅዱስ ይሖዋ አምላክን “አባት” በማለት መጥራቱ የተገባ ነው። (ማቴዎስ 6:9) ይሖዋ ምን ዓይነት አባት ነው? ለዚህ ጥያቄ መልስ ለማግኘት እንድንችል ኢየሱስ በተጠመቀበት ጊዜ ይሖዋ ለኢየሱስ የተናገራቸውን ቃላት እንመርምር። አንድ አባት ልጆቹን የሚያነጋግርበት መንገድ ምን ዓይነት ወላጅ መሆኑን በሚገባ እንደሚገልጽ እሙን ነው።

በ29 ከክርስቶስ ልደት በኋላ በጥቅምት ወር አካባቢ ኢየሱስ ለመጠመቅ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ ሄደ። መጽሐፍ ቅዱስ ሁኔታውን አስመልክቶ እንዲህ በማለት ይገልጻል:- “ኢየሱስም እንደ ተጠመቀ ከውሃው ወጣ፤ ወዲያውኑም ሰማይ ተከፍቶ የእግዚአብሔር መንፈስ እንደ ርግብ ሲወርድበት አየ። እነሆ፣ ‘በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው’ የሚል ድምፅ ከሰማይ ተሰማ።” * (ማቴዎስ 3:16, 17) ይሖዋ ራሱ የተናገራቸው እነዚህ አሳቢነት የተንጸባረቀባቸው ቃላት እሱ ምን ዓይነት አባት እንደሆነ ብዙ የሚነግሩን ነገር አለ። ይሖዋ ለልጁ የተናገራቸውን ሦስት ነገሮች ልብ በል።

በመጀመሪያ ደረጃ፣ ይሖዋ “ልጄ ይህ ነው” ሲል ‘የአንተ አባት በመሆኔ ኩራት ይሰማኛል’ በማለት የተናገረ ያህል ነበር። ልጆች በራሳቸው ማንነት መታወቅ እንዲሁም የሌሎችን ትኩረት ማግኘት ይፈልጋሉ፤ አሳቢ የሆነ አባት ደግሞ ይህን ፍላጎታቸውን ያሟላላቸዋል። ልጆች ትልቅ ግምት የሚሰጣቸው የቤተሰቡ አባላት ተደርገው እንደሚቆጠሩ ማረጋገጫ ሊሰጣቸው ያስፈልጋል። ኢየሱስ ጎልማሳ ሆኖም እንኳ ከአባቱ ይህን የመሰለ እውቅና በማግኘቱ ምን ሊሰማው እንደሚችል ገምት!

በሁለተኛ ደረጃ፣ ይሖዋ “የምወደው” ብሎ ስለ ልጁ በመናገር ለኢየሱስ ያለውን ፍቅር በይፋ ገልጿል። ይሖዋ ይህንን ሲል ‘እወድሃለሁ’ ማለቱ ነበር። ጥሩ የሆነ አባት ልጆቹን በጣም እንደሚወዳቸው ይነግራቸዋል። እንደዚህ ያሉ ቃላት የፍቅር መግለጫ በሆኑ ድርጊቶች ሲደገፉ ልጆች በጥሩ ሁኔታ እንዲያድጉ ይረዷቸዋል። ኢየሱስ፣ አባቱ እንደሚወደው ሲናገር ሲሰማ ምን ያህል ልቡ ተነክቶ ይሆን?

በሦስተኛ ደረጃ፣ ይሖዋ “በእርሱ ደስ የሚለኝ” በማለት ለልጁ ያለውን አድናቆት ገልጿል። ይሖዋ ይህንን ሲል ‘ልጄ፣ ባደረግከው ነገር ተደስቻለሁ’ በማለት የተናገረ ያህል ነበር። አፍቃሪ የሆነ አባት ልጆቹ በሚናገሩት ወይም በሚያደርጉት መልካም ነገር መደሰቱን እንዲያውቁ ለማድረግ አጋጣሚዎችን ይፈልጋል። ልጆች፣ ወላጆቻቸው እንደሚያደንቋቸው መስማታቸው ብርታት የሚጨምርላቸው ከመሆኑም በላይ ደፋሮች እንዲሆኑ ያደርጋቸዋል። ኢየሱስ አባቱ ለእሱ ያለውን አድናቆት መስማቱ አበረታቶት እንደሚሆን ምንም ጥርጥር የለውም!

በእርግጥም፣ ይሖዋ ወደር የማይገኝለት አባት ነው። ይሖዋ የአንተም አባት እንዲሆን ትመኛለህ? ከሆነ አንተም ከይሖዋ ጋር እንዲህ ያለውን ዝምድና መመሥረት እንደምትችል ማወቅህ ሊያጽናናህ ይችላል። በይሖዋ ላይ እምነት በማሳደር ስለ እሱ የምትማርና ፈቃዱን ለመፈጸም ከልብህ የምትጥር ከሆነ ምላሽ ይሰጥሃል። መጽሐፍ ቅዱስ “ወደ እግዚአብሔር ቅረቡ፤ እርሱም ወደ እናንተ ይቀርባል” ይላል። (ያዕቆብ 4:8) ወደር የማይገኝለት አባት ከሆነው ከይሖዋ አምላክ ጋር የተቀራረበ ዝምድና ከመመሥረት የበለጠ ደኅንነት እንዲሰማህ የሚያደርግ ምን ነገር ሊኖር ይችላል?

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.5 “የምወድህ ልጄ አንተ ነህ፤ በአንተ ደስ ይለኛል” በሚለው በሉቃስ ወንጌል ውስጥ ሰፍሮ በሚገኘው ተመሳሳይ ዘገባ ውስጥ ይሖዋ “አንተ” የሚለውን ተውላጠ ስም ተጠቅሟል።​—ሉቃስ 3:22