በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

አሳዛኝ ሁኔታ ቢደርስብህም ደስተኛ መሆን ትችላለህ

አሳዛኝ ሁኔታ ቢደርስብህም ደስተኛ መሆን ትችላለህ

አሳዛኝ ሁኔታ ቢደርስብህም ደስተኛ መሆን ትችላለህ

አሳዛኝ ሁኔታ ደርሶበት የማያውቅ ማን ይኖራል? በሰማይ የሚኖረው አባታችን፣ ይሖዋ አምላክ እንኳ ያዘነባቸው ጊዜያት ነበሩ። ለምሳሌ ያህል፣ እስራኤላውያንን ከግብጽ ባርነት ነፃ በማውጣት የተትረፈረፈ በረከት ሰጥቷቸው የነበረ ቢሆንም መጽሐፍ ቅዱስ “ደግመው ደጋግመው እግዚአብሔርን ተፈታተኑት፤ የእስራኤልንም ቅዱስ አስቈጡት [“አሳዘኑት፣” የ1954 ትርጉም]” ይላል። (መዝሙር 78:41) ያም ሆኖ ይሖዋ ምንጊዜም “ደስተኛ አምላክ” ነው።—1 ጢሞቴዎስ 1:11 NW

እርግጥ ነው፣ እንድናዝን የሚያደርጉን በርካታ ነገሮች አሉ። ታዲያ እነዚህ ነገሮች ደስታችንን እንዳይሰርቁብን ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው? ይሖዋ አሳዛኝ ሁኔታዎች ሲገጥሙት ከወሰደው እርምጃ ምን ትምህርት እናገኛለን?

ለሐዘን የሚዳርጉ ነገሮች

የአምላክ ቃል ባልታሰበ “ጊዜና አጋጣሚ” በሁላችንም ላይ መጥፎ ነገር ሊደርስብን እንደሚችል ይናገራል። (መክብብ 9:11 NW) በድንገት በደረሰብን ሁኔታ ለምሳሌ ያህል፣ በወንጀል፣ በአደጋ አሊያም በበሽታ ምክንያት ለችግር ልንዳረግና ልናዝን እንችላለን። ከዚህም በተጨማሪ መጽሐፍ ቅዱስ “ለነገ የሚባል ተስፋ ልብን ያሳምማል [‘ያሳዝናል፣’ የ1954 ትርጉም]” ይላል። (ምሳሌ 13:12) አንድን ጥሩ ነገር በጉጉት መጠባበቅ የሚያስደስት ቢሆንም የጠበቅነው ነገር ቶሎ አለመፈጸሙ ግን ሊያሳዝነን ይችላል። ለምሳሌ ያህል፣ ዳንከን * ሚስዮናዊ ለመሆንና ሕይወቱን በሙሉ በዚህ የአገልግሎት ዘርፍ ለማሳለፍ ከፍተኛ ፍላጎት የነበረው ቢሆንም ለረጅም ጊዜ ሲያገለግሉ ከቆዩ በኋላ እሱና ባለቤቱ በሚስዮናዊነት ማገልገላቸውን ለማቆም ተገደዱ። ዳንከን እንዲህ ብሏል:- “በሕይወቴ ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ የባዶነት ስሜት ተሰማኝ። ምንም ግብ አልነበረኝም። ሁሉም ነገር ከንቱ እንደሆነ አሰብኩ።” የሚሰማን የሐዘን ስሜት ለረጅም ጊዜ ሊዘልቅ ይችላል። ተመሳሳይ ሁኔታ የገጠማት ክሌር እንዲህ ብላለች:- “የሰባት ወር ነፍሰ ጡር እያለሁ አስወረደኝ። ይህ የሆነው ከረጅም ጊዜ በፊት ቢሆንም አሁንም ድረስ አንድ ልጅ መድረክ ላይ ቆሞ ንግግር ሲያቀርብ ስመለከት ‘ልጄ በሕይወት ቢኖር ኖሮ ይህን ያክል ነበር’ እያልኩ አስባለሁ።”

በተጨማሪም ለጋብቻ ካሰብነው ሰው ጋር የምናደርገው መጠናናት ሳይሳካ ሲቀር፣ ትዳራችን ሲፈርስ፣ ልጃችን ሲያምጽ ወይም የምንወደው ጓደኛችን ታማኝና አመስጋኝ ሳይሆን ሲቀር ልናዝን እንችላለን። የምንኖረው ፍጽምና በጎደላቸው ሰዎች መካከልና በአስጨናቂ ጊዜ ውስጥ በመሆኑ ለሐዘን የሚዳርጉን በርካታ ነገሮች አሉ።

ከዚህም ባሻገር የራሳችን ድክመት እንድናዝን ሊያደርገን ይችላል። ለምሳሌ ያህል ፈተና ስንወድቅ፣ ሥራ ሳናገኝ ስንቀር፣ ያፈቀርነው ሰው ለእኛ ፍቅር እንደሌለው ስናውቅ የከንቱነት ስሜት ሊሰማን ይችላል። በተጨማሪም አንድ የምንወደው ሰው መንፈሳዊ እድገት ማድረጉን ሲያቆም እናዝናለን። ሜሪ እንዲህ ብላለች:- “ሴት ልጄ ጥሩ መንፈሳዊ እድገት በማድረግ ላይ ያለች ትመስል ነበር። እኔም ጥሩ ምሳሌ እንደሆንኳት ሆኖ ይሰማኝ ነበር። ይሁንና ይሖዋ አምላክን ስትተውና ቤተሰባችን የሚመራባቸውን መሥፈርቶች ለመታዘዝ ፈቃደኛ ሳትሆን ስትቀር ልፋቴ ከንቱ እንደሆነ ተሰማኝ። ከዚያ ቀደም በሕይወቴ ውስጥ ያገኘኋቸው ሌሎች ስኬቶች ሊያጽናኑኝ አልቻሉም። ከፍተኛ የተስፋ መቁረጥ ስሜት ተሰማኝ።”

እነዚህን የመሰሉ አሳዛኝ ሁኔታዎችን መቋቋም የምንችለው እንዴት ነው? ይሖዋ የደረሱበትን አሳዛኝ ሁኔታዎች የያዘበትን መንገድ መመርመራችን የዚህን ጥያቄ መልስ ለማግኘት ይረዳናል።

በመፍትሔው ላይ አተኩር

ይሖዋ አምላክ፣ ለመጀመሪያዎቹ ባልና ሚስት በፍቅር ተነሳስቶ የሚያስፈልጋቸውን ነገር ሁሉ ሰጥቷቸው ነበር። እነሱ ግን አመስጋኞች ሳይሆኑ ከመቅረታቸውም ሌላ ዓመጹበት። (ዘፍጥረት ምዕራፍ 2 እና 3) ከዚያም ልጃቸው ቃየን መጥፎ ዝንባሌ ማሳየት ጀመረ። ቃየን የይሖዋን ማስጠንቀቂያ ችላ በማለት የገዛ ወንድሙን ገደለው። (ዘፍጥረት 4:1-8) ይህ ሁኔታ ይሖዋን ምን ያህል ሊያሳዝነው እንደሚችል ገምት!

ይህ አሳዛኝ ሁኔታ መከሰቱ የይሖዋን ደስታ አላጠፋውም። ምክንያቱም አምላክ ምድርን ፍጹም በሆኑ ሰዎች የመሙላት ዓላማ የነበረው ሲሆን ይህንንም ከግብ ለማድረስ እየሠራ ነበር። (ዮሐንስ 5:17) ለዚህም ሲል ቤዛዊ መሥዋዕት ከማዘጋጀቱም ሌላ መንግሥቱን አቋቁሟል። (ማቴዎስ 6:9, 10፤ ሮሜ 5:18, 19) ይሖዋ አምላክ ትኩረት ያደረገው በችግሩ ላይ ሳይሆን በመፍትሔው ላይ ነው።

የአምላክ ቃል፣ ያለፈውን ነገር እያሰብን ከመቆጨት ይልቅ አሁን ልናደርጋቸው በምንችላቸው ነገሮች ላይ እንድናተኩር ያበረታታናል። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል:- “እውነት የሆነውን ሁሉ፣ ክቡር የሆነውን ሁሉ፣ ትክክል የሆነውን ሁሉ፣ ንጹሕ የሆነውን ሁሉ፣ ተወዳጅ የሆነውን ሁሉ፣ መልካም የሆነውን ሁሉ፣ በጎነት ቢሆን ወይም ምስጋና፣ እንደ እነዚህ ስላሉት ነገሮች አስቡ።”—ፊልጵስዩስ 4:8

ለደረሰብን አሳዛኝ ሁኔታ ተገቢ አመለካከት መያዝ

በሕይወታችን ውስጥ ከፍተኛ ለውጥ የሚያስከትሉ ነገሮች ሊገጥሙን ይችላሉ። ለምሳሌ ያህል፣ በድንገት ከሥራ ልንባረር እንዲሁም የትዳር ጓደኛችንን አሊያም በጉባኤ ውስጥ ያለንን የአገልግሎት መብት ልናጣ እንችላለን። ምናልባትም ጤንነታችን ሊታወክ፣ ቤታችንን ወይም ጓደኞቻችንን ልናጣ እንችላለን። እንዲህ ያሉ ሁኔታዎችን መቋቋም የምንችለው እንዴት ነው?

አንዳንዶች በሕይወታቸው ውስጥ ቅድሚያ ሊሰጣቸው ለሚገቡ ነገሮች ተገቢውን ቦታ መስጠታቸው ጠቃሚ ሆኖ አግኝተውታል። ቀደም ሲል የተጠቀሰው ዳንከን እንዲህ ብሏል:- “እኔና ባለቤቴ ዳግም ሚስዮናዊ ሆነን ማገልገል እንደማንችል ስናውቅ እጅግ አዝነን ነበር። ውሎ አድሮ ግን ለሁለት ነገሮች ቅድሚያ ለመስጠት፣ ማለትም እማማን ለመንከባከብና በተቻለን መጠን በሙሉ ጊዜ አገልግሎት ለመቀጠል ወሰንን። አንድ ውሳኔ ከማድረጋችን በፊት ቅድሚያ የምንሰጣቸውን እነዚህን ነገሮች እንዴት ሊነካብን እንደሚችል እናስባለን። እንዲህ ማድረጋችን ብዙም ሳንጨነቅ ትክክለኛ ውሳኔ እንድናደርግ ይረዳናል።”

አብዛኞቻችን ያጋጠመንን ችግር አጋነን መመልከት ይቀናናል። ለምሳሌ ያህል ልጆቻችንን ለማሳደግ፣ ሥራ ለማግኘት ወይም በሌላ አገር የምሥራቹን ለመስበክ ያደረግነው ጥረት ያሰብነውን ያህል ውጤት እንዳላስገኘ ይሰማን ይሆናል። በመሆኑም ‘የማልረባ ሰው ነኝ’ ብለን ልናስብ እንችላለን። ሆኖም በሰው ልጅ ታሪክ መጀመሪያ ላይ የተከሰተው አሳዛኝ ሁኔታ አምላክ ብቃት እንደጎደለው የሚያሳይ ማስረጃ እንዳልነበረ ሁሉ ያደረግነው ጥረት ወዲያውኑ ጥሩ ውጤት ስላላስገኘ ብቻ ‘የማንረባ ሰዎች ነን’ ማለትም አይደለም።—ዘዳግም 32:4, 5

ሰዎች ሲበድሉን በቀላሉ ቅር እንሰኝ ይሆናል። ይሖዋ ግን እንዲህ አያደርግም። ንጉሥ ዳዊት ከቤርሳቤህ ጋር ዝሙት መፈጸሙና ባሏን ማስገደሉ ይሖዋን አሳዝኖት ነበር። ያም ሆኖ ይሖዋ፣ ዳዊት ከልቡ ንስሐ መግባቱን በማየት እሱን ማገልገሉን እንዲቀጥል ፈቅዶለታል። በተመሳሳይም ታማኝ የነበረው ንጉሥ ኢዮሳፍጥ ከአምላክ ጠላቶች ጋር ሕብረት በመፍጠር ስህተት ፈጽሟል። ሆኖም የይሖዋ ነቢይ “የእግዚአብሔር ቍጣ ባንተ ላይ ነው፤ ይሁን እንጂ . . . መልካም ነገር ተገኝቶብሃል” ብሎታል። (2 ዜና መዋዕል 19:2, 3) ይሖዋ ኢዮሳፍጥ አንድ ስህተት መሥራቱ ብቻ እሱን ክዷል ሊያሰኘው እንደማይችል ተገንዝቧል። በተመሳሳይም ወዳጆቻችን ሲሳሳቱ ከልክ በላይ ባለመቆጣት ወዳጅነታችንን ጠብቀን መኖር እንችላለን። ወዳጆቻችን ቅር ቢያሰኙንም ጥሩ ባሕርያት አሏቸው።—ቈላስይስ 3:13

ስኬት ላይ ለመድረስ ጥረት ስናደርግ አሳዛኝ ሁኔታዎች መከሰታቸው የማይቀር መሆኑን መገንዘብ ይኖርብናል። ኃጢአት ስንሠራ በራሳችን እናዝን ይሆናል። ያም ሆኖ ትክክለኛና ቁርጥ ያለ እርምጃ ከወሰድን ካለንበት ሁኔታ ልናገግም ብሎም እድገት ልናደርግ እንችላለን። ንጉሥ ዳዊት በራሱ ሁኔታ እጅግ ባዘነበት ወቅት “ቀኑን ሙሉ ከመቃተቴ የተነሣ፣ . . . ዐጥንቶቼ ተበላሹ፤ . . . ኀጢአቴን ለአንተ [ለይሖዋ] አስታወቅሁ . . . አንተም የኀጢአቴን በደል፣ ይቅር አልህ” በማለት ጽፏል። (መዝሙር 32:3-5) ይሖዋ ከእኛ የሚጠብቀውን ነገር እንዳላደረግን ከተገነዘብን ይቅር እንዲለን መለመን፣ አካሄዳችንን ማስተካከልና ማሳሰቢያዎቹን በጥብቅ ለመከተል ቁርጥ ውሳኔ ማድረግ ይገባናል።—1 ዮሐንስ 2:1, 2

አሳዛኝ ሁኔታዎችን ለመቋቋም መዘጋጀት

ወደፊትም ቢሆን ሁላችንም አንድ የሚያሳዝን ነገር ሊያጋጥመን ይችላል። ታዲያ እነዚህን ሁኔታዎች ለመቋቋም መዘጋጀት የምንችለው እንዴት ነው? በሕይወታቸው ላይ ከፍተኛ ለውጥ ያስከተለ አሳዛኝ ሁኔታ የገጠማቸው ብሩኖ የተባሉ አንድ አረጋዊ ክርስቲያን የተናገሩት የሚከተለው ሐሳብ ትኩረት የሚስብ ነው:- “የደረሰብኝን አሳዛኝ ሁኔታ ለመቋቋም የረዳኝ ዋናው ነገር ከዚህ ቀደም አደርግ እንደነበረው ሁሉ መንፈሳዊነቴን ለማጠናከር ጥረት ማድረጌ ነው። አምላክ ይህ ክፉ ሥርዓት እንዲቀጥል የፈቀደበትን ምክንያት አውቃለሁ። ከይሖዋ ጋር የቅርብ ዝምድና ለመመሥረት ለረጅም ዓመታት ጥረት አድርጌያለሁ። እንዲህ በማድረጌ ደስተኛ ነኝ። ይሖዋ ከጎኔ እንደሆነ ማወቄ ያደረብኝን የመንፈስ ጭንቀት እንድቋቋም ረድቶኛል።”

ስለ ወደፊቱ ጊዜ ስናስብ፣ ራሳችን በምንፈጽመው ድርጊት አሊያም ሌሎች ሰዎች በሚያደርጉት ነገር ልናዝን ብንችልም አምላክ ግን ፈጽሞ እንደማያሳዝነን እርግጠኞች መሆን እንችላለን። እንዲያውም አምላክ፣ ይሖዋ የሚለው ስሙ “መሆን የሚያስፈልገኝን ሁሉ እሆናለሁ” የሚል ትርጉም እንዳለው ተናግሯል። (ዘፀአት 3:14 NW) ይህን ማወቃችን፣ ይሖዋ የገባውን ቃል ለመፈጸም ሲል መሆን የሚያስፈልገውን ሁሉ እንደሚሆን ማረጋገጫ ይሰጠናል። ይሖዋ በመንግሥቱ አማካኝነት ‘ፈቃዱ በሰማይ እንደሆነ ሁሉ በምድርም’ ላይ እንዲሆን እንደሚያደርግ ቃል ገብቷል። በመሆኑም ሐዋርያው ጳውሎስ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “ይህን ተረድቻለሁ፤ ሞትም ይሁን ሕይወት፣ መላእክትም ይሁኑ አጋንንት፣ . . . ወይም የትኛውም ፍጥረት፣ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ካለው ከእግዚአብሔር ፍቅር ሊለየን አይችልም።”—ማቴዎስ 6:10፤ ሮሜ 8:38, 39

አምላክ በነቢዩ ኢሳይያስ በኩል የተናገረው የሚከተለው ሐሳብ ሙሉ በሙሉ እንደሚፈጸም እርግጠኞች መሆን እንችላለን:- “እነሆ፤ እኔ፣ አዲስ ሰማያትንና አዲስ ምድርን እፈጥራለሁ፤ ያለፉት ነገሮች አይታሰቡም፤ አይታወሱም።” (ኢሳይያስ 65:17) ያጋጠሙንን አሳዛኝ ሁኔታዎች ሙሉ በሙሉ የምንረሳበት ጊዜ እንደሚመጣ ማወቅ እንዴት አስደሳች ነው!

[የግርጌ ማስታወሻዎች]

^ አን.5 አንዳንዶቹ ስሞች ተቀይረዋል።

[በገጽ 13 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

ያደረግነው ጥረት ወዲያውኑ ጥሩ ውጤት ስላላስገኘ ብቻ ‘የማንረባ ሰዎች ነን’ ማለት አይደለም

[በገጽ 14 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

የአምላክ ቃል፣ ያለፈውን ነገር እያሰብን ከመቆጨት ይልቅ አሁን ልናደርጋቸው በምንችላቸው ነገሮች ላይ እንድናተኩር ያበረታታናል

[በገጽ 15 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ሰዎች በኃጢአት ቢወድቁም አምላክ ዓላማው ከግቡ መድረሱ እንደማይቀር እርግጠኛ ስለነበር ደስታውን አላጣም

[በገጽ 16 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ለመንፈሳዊ ነገሮች ቅድሚያ መስጠት አሳዛኝ ሁኔታዎችን ለመቋቋም ይረዳናል