በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

በእርግጥ “ሕቡዕ ስም” ነው?

በእርግጥ “ሕቡዕ ስም” ነው?

በእርግጥ “ሕቡዕ ስም” ነው?

በሴይንት ሉዊስ፣ ሚዙሪ በወንዝ ዳርቻ ላይ የሚገኘው የጌትዌይ ቅስት በዩናይትድ ስቴትስ ውስጥ ካሉት ሐውልቶች ሁሉ በጣም ረጅሙ ሲሆን ቁመቱም 192 ሜትር ነው። በአንደኛው የቅስቱ ጎን አቅራቢያ በተለምዶ ኦልድ ካቴድራል ተብሎ የሚጠራ ቤተ ክርስቲያን ይገኛል።

ቤተ ክርስቲያኗ ያሳተመችው ዘ ስቶሪ ኦቭ ዚ ኦልድ ካቴድራል የተሰኘው ቡክሌት፣ በካቴድራሉ መግቢያ ላይ የሚገኘውን የሕንፃ ጥበብ አስመልክቶ ሲናገር እንዲህ ብሏል:- “ውብ በሆነው የካቴድራሉ በረንዳ አናት ላይ የአምላክ ሕቡዕ ስም በትላልቅ የዕብራይስጥ ፊደላት ተቀርጾ የሚገኝ ሲሆን ፊደላቱም በወርቅ ተለብጠዋል።” በፎቶው ላይ መመልከት እንደሚቻለው መለኮታዊውን ስም የሚወክሉት ቴትራግራማተን ተብለው የሚጠሩት አራት የዕብራይስጥ ፊደላት יהוה (የሐወሐ) በጉልህ ይታያሉ።

ካቴድራሉ በ1834 በተገነባበት ወቅት በሴይንት ሉዊስ የነበሩት የካቶሊክ ሃይማኖት መሪዎች፣ በአራቱ የዕብራይስጥ ፊደላት የተጻፈው የአምላክ ስም ትልቅ ቦታ ሊሰጠው እንደሚገባ ሳይሰማቸው አልቀረም። ታዲያ፣ ይህ መለኮታዊ ስም “ሕቡዕ” እንደሆነ ወይም “መጠራት እንደሌለበት” ተደርጎ የሚታሰበው ለምንድን ነው?

አይሁዳውያን በስድስተኛው መቶ ዘመን ከክርስቶስ ልደት በፊት ከባቢሎን ግዞት ከተመለሱ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ስለነበረው ሁኔታ ኒው ካቶሊክ ኢንሳይክሎፒዲያ ሲገልጽ እንዲህ ብሏል:- “ያህዌህ [በአራቱ የዕብራይስጥ ፊደላት ላይ አናባቢ ተጨምሮበታል] የሚለው ስም እጅግ ቅዱስ እንደሆነ ተደርጎ መታየት ጀመረ፤ በመሆኑም ይህ ስም አዶናይ [ጌታ] ወይም ኤሎሂም [አምላክ] በሚሉት ስሞች ይተካ ጀመር። . . . ስለሆነም ጊዜ እያለፈ ሲሄድ ሰዎች ያህዌህ የሚለውን ስም ትክክለኛ አጠራር ረሱት።” በዚህም ምክንያት ሰዎች በአምላክ ስም መጠቀማቸውን አቆሙ። ውሎ አድሮ በጥንት ዘመን ሰዎች ይጠቀሙበት የነበረው የአምላክ ስም ትክክለኛ አጠራር የተረሳ ሲሆን መለኮታዊው ስምም ሊጠራ እንደማይገባ ተደርጎ መታየት ጀመረ።

የአምላክን ስም ትክክለኛ አጠራር በእርግጠኝነት ማወቅ ባንችልም በስሙ መጠቀማችን ይበልጥ ወደ እሱ እንድንቀርብ ይረዳናል። ወዳጆችህ በስምህ ባይጠሩህ ምን ይሰማሃል? እነዚህ ሰዎች ሌላ ቋንቋ የሚናገሩ ቢሆኑና ስምህን አስተካክለው መጥራት ባይችሉ እንኳ በስምህ እንዲጠሩህ እንደምትፈልግ ምንም ጥርጥር የለውም። አምላክን በተመለከተም ሁኔታው ተመሳሳይ ነው። አምላክ፣ ይሖዋ በሚለው የግል ስሙ እንድንጠራው ይፈልጋል። ታዲያ አምላክን የሚወዱ ሁሉ በግል ስሙ በመጠቀም ከእሱ ጋር ይበልጥ መቀራረብ እንዳለባቸው አይሰማህም? መጽሐፍ ቅዱስ ‘ወደ አምላክ ቅረቡ፤ እሱም ወደ እናንተ ይቀርባል’ ይላል።—ያዕቆብ 4:8